Friday, October 18, 2013

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ ለእምነታቸው ዘብ ቆሙ

                                             ከሐራ ዘተዋሕዶ መካነ ድር

ከጥቅምት ፬ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም. ጀምሮ እየተካሄደ የሚገኘውና ሦስተኛ ቀኑን ያስቆጠረው ፴፪ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባ በዛሬው ዕለት ከቀትር በኋላ በነበረው ውሎ የተለየ ክሥተት አስተናግዷል፡፡ ‹‹የሃይማኖት መቻቻል›› በሚል ርእስ በአጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤው ዓመታዊ ስብሰባ ላይ በተካሄደው ውይይት፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ ከፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ባለሥልጣናት ጋራ በተለይም በመቻቻልና በኢትዮጵያ የክርስትና ታሪክ ዙሪያ ሲከራከሩና በአንዳንድ ኹኔታዎችም ኤክስፐርቶቹን ሲገሥጹ ውለዋል፡፡
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ÷ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ፣ ብፁዕ አቡነ ኄኖክ፣ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ፣ ብፁዕ አቡነ ያሬድ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ እና ብፁዕ አቡነ እንድርያስ÷ ከየአህጉረ ስብከታቸው ተጨባጭ ኹኔታና ከቀረበው ጽሑፍ እየተነሡ በመረጃ፣ በጥያቄና በትችት ስለ መቻቻል ጽሑፍ ያቀረቡ የሚኒስቴሩን ባለሥልጣናት ፈተና ላይ ጥለዋቸው አምሽተዋል፡፡ የሊቃነ ጳጳሳቱ ምስክርነት‹‹የባዕድ እምነት አራማጆች በቤተ ክርስቲያንና በካህናት ላይ ልዩ ልዩ ተጽዕኖ እንደሚያደርጉና ሕገ መንግሥቱን የጣሰ ታላቅ ድፍረት እንደሚፈጽሙ›› ቀደም ሲል ለአጠቃላይ ጉባኤው የቀረቡ ሪፖርቶችን በገሃድ የሚያጠናክሩና የሚያጸኑ ናቸው፡፡
የሚኒስቴሩ አማካሪዎችና ባለሞያዎች በበኩላቸው፣ ቅሬታዎቹ በተጨባጭ ማስረጃዎች ተደግፈው በሃይማኖት ተቋማት ጉባኤበኩል ቢቀርቡላቸው መፍትሔ እንደሚሰጧቸው፣ በሊቃነ ጳጳሳቱ ከተገለጹት በላይ ያልተነገሩ ቅሬታዎች ስለመኖራቸው በየወረዳው ተዘዋውረው መረጃዎችን አሰባስበው ማረጋገጣቸውን አስታውቀዋል፡፡ በ‹‹ሕግ የተያዙት ጉዳዮች በሕግ እንደተያዙ ተጠብቀው እንዲቀጥሉ›› ለዚህም የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ ጥንካሬ አስፈላጊ መኾኑን አሳስበዋል፡፡
የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱን ጥያቄ፣ አስተያየትና ትችት በከፍተኛ ጥሞና የተከታተለው የአጠቃላይ ጉባኤው ተሳታፊ የሞቀ ድጋፉን ሰጥቷቸዋል፡፡ በዚህ የውይይት አጀንዳ አጋጣሚውን እንደ ምቹ ኹኔታ ለመጠቀም ያሰቡ የሚመስሉትና ልዩ ፍላጎት ያላቸው የሚመስሉት አቡነ ሳዊሮስ ውይይቱን ሳይጨርሱ አቋርጠው ሲወጡ ታይተዋል፡፡

* * *

‹‹አክራሪነት/ጽንፈኝነት የሚለው ቋንቋ እናንተ ናችኹ ያሰማችኁን፤ ከዚህ በፊት አይታወቅም፤ ዕድሜ ሰጥታችኁም ያበለጸጋችኋቸው እናንተው ናችኹ፡፡ አባቶቻችን የእረኛ ሰነፍ ከሩቅ ይመልሳል ይላሉ፤ በሩቅ መቅጨት ሲገባ ታሪካቸው እየተተረከ ብዙ አተራመሱት፤ [የአክራሪነት]መረባቸውን ከላይ ዘርግተዋል፤ መሬት አልነኩም ተባለ፤ መረባቸውን መሬት ዘርግተው፣ ሕዝብ እያተራመሱ ሙስሊሙ ራሱ እኛ አናውቃቸውም እያለ እየጮኸ እንዴት መሬት አልነኩም ይባላል? በእናንተ አነጋገር መሬት ሲነኩ እንዴት ሊያደርጉን ኖሯል? . . . ተቻቻሉ? እስከ ምን ድረስ ነው መቻቻል? ምንድን ነው መቻቻል? አሁን በወለጋ ያለው ኹኔታ መንግሥት በአገሩ ያለ ያስመስላል? ሰው እግሩን እሳት እየበላው ቻል ይባላል? እንድንቻቻል አድርጉን፤ እንችላለን!!›› /ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ፣ የሰሜን ወሎና ዋግ ኽምራ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ/

‹‹በምዕራብ ወለጋ ሀ/ስብከት በሦስት ወረዳዎች – ነጆ፣ ባቦ ገምቤል፣ ቤጊ – በፖሊቲካና የመናፍቃን አባላት የኾኑ ባለሥልጣናት በሥነ ልቡና ጦርነት ምእመኖቻችንን እየነጠቁን በደል አድርሰውብናል፡፡ አገሩ ለፕሮቴስታንት የተፈቀደና ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አታስፈልግም የተባለ ነው የሚመስለው፡፡›› /ብፁዕ አቡነ ኄኖክ፣ የምዕራብ ወለጋና አሶሳ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ/
‹‹ከዚህ በፊት በዚህ መድረክ ክቡር ዶ/ር ሽፈራው ተክለ ማርያም መጥተው ብዙ ነገር አስጨብጫቸው ነበር፤ ምላሽ አላገኘኹም፤ በኢትዮጵያ ምድር ላይ ታይቶ የማይታወቅ ነገር በጋሞጎፋ ሀ/ስብከት ተፈጥሯል፡፡ የደመራ በዓል በሚከበርበት ቦታ ላይ ምትክ ሳይሰጥ ተወስዶ ሱቅ በመከፈቱ ዘንድሮ በመቶ ወረዳዎች የደመራ በዓል ሳይከበር ሕዝቡ እያዘነ፣ እያለቀሰ ቤቱ ውሏል፡፡ በሴቻ ከተማ ባልተፈቀደ ቦታ ለስምንት ቀን ጉባኤ አዘጋጅተው የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያናችንን፣ ጽላት፣ ቅዱሳን መላእክት እያነሡ ሲቃወሙ ነበር፡፡ ይህ ነዳጅ የተረከፈከፈበት ክብሪት ማለት ነው፡፡ ሕዝብ ሰልፍ እንውጣ ሲለን ሰላማችንን፣ ልማታችንን እንወደዋለን፤ መብታችንን በሕግ ነው የምንጠይቀው ብለን ከልክለናል፡፡ ጉባኤ ማካሄዳቸውን አንቃወምም፤ ግን ስማችንን ማንሣት ምን ማለት ነው? ይሄ ነው መቻቻል? እኛ ሌላውን አንነካም፤ ስንነካ ግን መብታችንን እንጠይቃለን፤ ቤተ ክርስቲያኗ መሬት መያዟን የወረዳው ባለሥልጣናት መሬቷን ቆርሳችኹ ጉባኤ አድርጉ ይላሉ፤ ይህን እንደ በቀል ነው የሚያዩት›› /ብፁዕ አቡነ ኤልያስ፤ የጋሞጎፋና ደቡብ ኦሞ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ/

‹‹በሶማሌ ክልል እስከ ቀበሌ ድረስ ባሉ የመንግሥት መሥ/ቤቶች ብዙ ሠራተኞች ምእመናን አሉ፡፡ ያሉን አብያተ ክርስቲያናት ግን አምስት ብቻ ናቸው፡፡ በየወረዳው ቤተ ክርስቲያን እንዲሠራ ምእመናን ይጠይቃሉ፡፡ እስከ ክልሉ መስተዳድር ድረስ ለምእመናን የምንጮኸበት፣ መብታችንን የምናስከበርበት ኹኔታ ግን የለም፡፡. . .ምእመናን እምነታቸውን በካሴትና በዘመናዊ መሣርያ ካልኾነ እኛ ተንቀሳቅሰን ለማገልገል የምንችልበት ኹኔታ የለም፡፡ በክልሉ ሁሉም ወረዳዎች የምእመናኑን ብዛት ዐውቀንና አጥንተን ያዘጋጀነው ስላለ የሚመለከተው ክፍል መፍትሔ እንዲሰጠን እንጠይቃለን፡፡›› /ብፁዕ አቡነ ያሬድ፣ የሶማሌ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ/

‹‹ታሪክ ክፉ ይኹን ደግ እንደ ታሪኩ ነው የሚተረክ፤ ወንድማችን [ከዕለቱ የሚኒስቴሩ ሦስት ተናጋሪዎች አንዱ የነበሩት አቶ ገዛኽኝ ጥላሁን] ይህን ታሪክ ስታቀርብ ምን ያህል ላይሰንስ አለኽ? ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ፤. . .ክርስትና በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ነው የሚለው ሌላ ጊዜ እንዳይደገም፣ ዛሬ ግራጁዌት አድርጉት፤ ክርስትና ወደ ኢትዮጵያ ሲገባ ክርስቶስ ካረገ ዓመት አልሞላውም፤ ገና ከኢየሩሳሌም አልተወጣም፤ ከሰው አይደለም ደግሞ ከእግዚአብሔር ነው የተቀበለችው፡፡ (የሐዋ.8÷26) ባለሥልጣን ሁሉ አገር የሚጠላ ምንድን ነው? በዓለም በትልቁ መጽሐፍ በመጽሐፍ ቅዱስ ተጽፏል፤ በእግዚአብሔር ማመንንም የተቀበልን ከአይሁድ በፊት ነው፡፡ ታሪኩን አታዛቡ፤ ከዚህም ስትመጡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ የሠለጠነ፣ ቢቻል ኦርቶዶክስ ሃይማኖት ተከታይ የኾነ፣ በጳጳሳቱ ፊት ለመናገር የሚገባው መኾን አለበት፤ አታስቆጡን! . . .ቤተ ክርስቲያን እንግዳ ሲመጣ ሃይማኖትኸ ምንድን ነው አትልም፡፡ እግር አጥባ፣ አብልታ ነው፤ ግን ልታስተምሩን ስትመጡ ሳብጀክቱን ግራጁዌት አድርጋችኹ ኑ!›› /ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፣ የምሥራቅ ጎጃም ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ/


‹‹. . .ችግሮቹ መፍትሔ አጥተው ቀርተዋል፡፡ ስድስት አድባራት ተቃጥለዋል፤ ሦስቱ በአንድ አካባቢ፣ ሦስቱ በተራራቀ ኹኔታ፡፡ ቢጮኽ የክልሉ መንግሥት አይሰማም፤ መልስም አይሰጠም፤ እንዲያውም ያስተባብላል፤ የተበደለ ሲናገር ፖሊቲካ ነው እያሉ ያተራምሱናል፤ ሐቅ ሲነገር ድብቅ የለውም፤ ሌትም ቀንም ቤተ ክርስቲያን እየተቃጠለ፣ የሚጮኽበት እየታጣ ነው፡፡. . .የመንግሥት ሥልጣን የተረከቡ ወንድሞች የእኛን አንደበት ብቻ ነው እንዴ የሚጠብቁት? ለሌላው ብቻ ነው የቆሙት? ይህ የሰላም መደፍረስ አይደለም? መቻቻል የሚባለው አማርኛ ምንድን ነው? አማርኛ ነው እንዴ የምታመርቱት? በየቢሯቸው ሄጃለኹ፣ አንዱ እንደውም ተቆጣኝ፤ ይኸው ዘመን ተቆጥሯል፤ ዐርባ ዓመት ኾኗል፤ ለሕዝቡም ለመንግሥትም የምንኖረው እኛ ብቻ ነን፡፡ ለምንድን ነው በሽፋንነት የምትጠቀሙብን? ሁሉም ሲያጭበረብረን፣ ሲያታኩሰን፣ ሲያቃጥለን የሚኖረው መንግሥትን ሽፋን አድርጎ ነው፡፡ ይቅርታ አድርጉልን፡፡›› /ብፁዕ አቡነ እንድርያስ፣ የደቡብ ጎንደር ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ/

Thursday, October 10, 2013

ማኅበረ ቅዱሳን – የሃይማኖት አጥባቂነት ወይስ የአክራሪነት




(ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፤ 19ኛ ዓመት ቁጥር 255፤ ነሐሴ 16 – ጳጉሜ 5 2004 ዓ.ም)

በዲ/ን ታደሰ ወርቁ*

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአንዳንድ መንግሥታዊ አካላት በወጡ ሰነዶችና በሚሰሙ ንግግሮች ማኅበረ ቅዱሳንን ‹‹የኦርቶዶክስ ክርስትና ሃይማኖት አክራሪዎች›› ማንጸርያ አድርጎ የመውሰድ አዝማሚያዎች እየታዩ ነው፡፡ ይህን የተሳሳተ አቻ ፈጠራበመጠቀም አፅራረ ቤተ ክርስቲያንም የራሳቸውን ፍላጎት ሲያራግቡበት ይታያል፡፡ ተከታዩ ጽሑፍ መንግሥት አቋሞቹን የገለጸባቸውን ሰነዶችና የማኅበረ ቅዱሳንን የኅትመት ውጤቶች በመፈተሽ ማኅበረ ቅዱሳን የሃይማኖት አጥባቂነት እንጂ የሃይማኖት አክራሪነት ትእምርት እንዳልኾነና ሊኾንም እንደማይችል ያስረዳል፡፡
* * *


ዲ/ን ታደሰ ወርቁ

አክራሪነት አሉታዊ ትርጉም ሲኖረው የራስን እምነትና አመለካከት በሌሎች ላይለመጫን መሞከር ነው፡፡ ሃይማኖት መንግሥታዊ ቅርጽ ይዞ እንዲወጣ ለማድረግ መሞከር ራሱ አክራሪነት እንደኾነ የዘርፉ ዐዋቆች ይሞግታሉ፡፡ አክራሪነት በአሉታዊ መልኩ የፖሊቲካ ገጽታ ያለው ነው፡፡ ኾኖም ግን ሃይማኖትን ማጥበቅ አክራሪነት አይደለም፡፡ሃይማኖት ፍጹም እውነታን በፍጹም እምነት ስለሚቀበል ከሌሎች ግላዊ አስተሳሰቦች የተለየ ነው፡፡ የሃይማኖት መገለጫዎችን መጠቀም የዚያን ሃይማኖት ጥልቀት የሚያሳይ እንጂ እንደ ችግርም የሚወሰድ ወይም አክራሪነት ሊኾን አይችልም፡፡ «መጾም፣ መጸለይ፣ ሥርዓተአምልኮን መፈጸም ለሃይማኖቱ ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ እንጂ አክራሪነት ሊባልአይችልም፤» ይላሉ የዘርፉ ምሁራን፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥትም የሃይማኖት አክራሪነትን ለመቃወም ባዘጋጃቸው ሰነዶች የአክራሪነትና የአጥባቂነት ፅንሰ ሐሶቦች በጥሩ ኹኔታ ተለይተው ተገልጸዋል፡፡ ሰነዶቹ አክራሪነትንና አጥባቂነትን በአግባቡ ለይተውና ተንትነው ያስቀምጣሉ፡፡ በዚሁ መሠረትአጥባቂነትን ‹‹የግል ሃይማኖትን ሃይማኖቱ በሚያዘው መሠረት ሳይንጠባጠብ ሁሉንም ትእዛዛት መፈጸም ነው፤» በማለት ሲፈታው አክራሪነትን ደግሞ፣ «ከራስ እምነት ወጥቶ ሌላውን መተንኮስና የሌሎችን ሃይማኖት መኖር አለማመንና አለመፍቀድወይም ሌሎቹን አስገድዶ የራስ እምነት ተከታዮች ለማድረግ መጣር ነው፤» ይላል፡፡

ከዚህ ብያኔ ስንነሣ ሙስሊምም ኾነ ክርስቲያን ከርሱ ውጭ የኾኑትን የሌሎቹን መኖር የማይቀበልና ከግለሰቦቹ ፈቃድ ውጭ አስገዳጅ እስከኾነ ድረስ እርሱን አክራሪ ማለት ይቻላል፡፡ በዚህ መልኩ አክራሪው ይህንኑ ድርጊት ሊፈጽም የተነሣውን ቡድን ብቻ እንጂ «አክራሪው ቡድን» የወጣበትን/የተገኘበትን ቤተ እምነት ሊወክል አይችልም፡፡ ስለዚህ የአክራሪ እስልምና ቡድን መኖር የእስልምና ተከታዮችን በሙሉ «አክራሪ» አስብሎ ሊያስፈርጃቸው አይችልም፤ ለሌላው ቤተ እምነትም እንዲሁ፡፡

የሃይማኖት አክራሪነትንና አጥባቂነትን በዚህ መልኩ ከተረዳን ማኅበረ ቅዱሳን የሃይማኖት አክራሪነት ወይስ አጥባቂነት ትእምርት የሚለውን ወቅታዊ ጥያቄ መመለስ ግድ ይለናል፡፡ ይኸውም መንግሥት የተለያዩ መግለጫዎችን ከማውጣት አንሥቶ ውይይቶችን እያካሔደና ሌሎች ርምጃዎችንም እየወሰደ ይገኛል፡፡ ይህን እንደ መልካም አጋጣሚ ተጠቅመው ማኅበረ ቅዱሳንን በአክራሪነት ለማስፈረጅና ከመንግሥት ጋራ ለማጋጨት ቆርጠው የተነሡ አካላት እንዳሉ ከአንዳንድ የውይይት መድረኮች፣ ሰነዶች፣ [የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ] ብሎጎችና የደብዳቤ መጻጻፎች ለመረዳት ተችሏል፡፡

በተለይ ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሚያዝያ 9 ቀን 2004 ዓ.ም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የስድስት ወር ሪፖርት በሚያቀርቡበት ወቅት የሃይማኖት አክራሪነትንና የመንግሥታቸውን የፀረ አክራሪነት እንቅስቃሴ በተመለከተ ለምክር ቤቱ አባላት ሰፊ ማብራሪያ ሲሰጡ፣ «. . . አንዳንድ የሰለፊ እምነት ተከታዮች . . . በተለያየ መንገድ አንዳንድ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት የሚያራምዱትንግልባጭ ሲያራምዱ ታይቷል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ አብዛኛው ሙስሊም ነው፡፡ የስታቲስቲክስ መሥሪያ ቤት ያቀረበው መረጃ ውሸትነው፡፡ አብዛኛው ሕዝብ ሙስሊም ስለኾነ የእስላም መንግሥት ነው መቋቋም ያለበት የሚል ቅስቀሳ በሰፊው ነው የሚካሔደው፡፡በእነዚህ አክራሪዎች፡፡. . .» ብለው መጥቀሳቸውን ተከትሎ የስም ማጥፋት ዘመቻው ከወትሮው ተባብሷል፡፡

ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን አክራሪነትን ከመቃወም አንጻር ምን እንደ ሠራ ከዚህም ጋራ በማኅበሩ ላይ ያሉ ብዥታዎችን በማጥራት የማኅበሩን አጠቃላይ ኹኔታ ለመግለጽ ጊዜው የሚጠይቀው ጉዳይ ኾኗል፡፡ ይህ ጽሑፍም ማኅበሩ በሃይማኖት አክራሪነት ጉዳይ ያለውን አቋም፣ የማኅበሩን እውነተኛ ማንነትና ትክክለኛ ገጽታ ከድርጊቱና ከወሰዳቸው አቋሞች አንጻር ለማስረዳት የተዘጋጀ ነው፡፡ ሦስት መሠረታዊ መነሻዎችን እናቅርብ፡፡

የፍረጃው አዝማሚያና የቅርብ መነሻ የሕዝብና ቤት ቆጠራ ውጤት መኾኑ፤

በምክር ቤቱ ማብራሪያ ውስጥ አቶ መለስ ማኅበረ ቅዱሳንን የሰለፊ ማንጸርያ አድርገው ያቀረቡት ከሕዝብና ቤት ቆጠራ ውጤት አንጻር ብቻ ነው፡፡ ይህም ቢኾን በራሱ ማኅበረ ቅዱሳንን እንደ ተቋም አክራሪ አያሰኘውም፤ ስለ ሁለት ነገር፤ የመጀመሪያው፣ አቶ መለስ «አንዳንድ የማኅበረ ቅዱስን አባላት» አሉ እንጂ ማኅበረ ቅዱሳን አላሉም፡፡ ይህም ግለሰባዊ ሓላፊነትን እንጂ ተቋማዊ ሓላፊነትን አይገልጽም፡፡ ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን እንደ ማኅበር የሃይማኖት አክራሪነት ትእምርት ተደርጎ ሊወሰድ አይችልም፡፡

ሁለተኛው፣ የሕዝብና ቤት ቆጠራውን ውጤት ከአለመቀበል ጋራ ማኅበረ ቅዱሳን እንደ ተቋም «አክራሪ» ተብሏል በሚለው ብንሔድ እንኳን የመረጃና የማስረጃ ዳጥን ከማሳበቅ ውጭ ማኅበረ ቅዱሳንን የሃይማኖት አክራሪ አያሰኘውም፡፡ ምክንያቱም የሕዝብና ቤት ቆጠራው ውጤት ላይ «ጥርጣሬ አለኝ» ያለችው /ይህም ቢኾን አክራሪ አያስብልም/ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንጂ ማኅበረ ቅዱሳን ወይም አንዳንድ የማኅበረ ቅዱሳንአባላት አይደሉም፡፡

በወቅቱ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወክለው መግለጫ የሰጡት የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ መጋቤ ሥርዐት ዳንኤል ወልደ ገሪማ ቤተ ክርስቲያኒቱ በውጤቱ ላይ ያላትን ጥርጣሬ ሲገልጹ፣ «መንግሥት የሕዝብና ቤት ቆጠራ በሚያካሒድበት ወቅት ከቦታ ርቀት የተነሣበገዳም የሚገኙ መነኮሳትና መነኮሳዪያትን፣ የቆሎ ተማሪዎች ቁጥር ካለማካተቱም ባሻገር በተለያዩ ምክንያቶች ያልተቆጠሩምእመናን ተካተዋል ለማለት ስለሚያጠራጥር ቤተ ክርስ ቲያኗ መንግሥት ይፋ ያደረገውን ውጤት ሙሉ ለሙሉ ለመቀበልይቸግራታል፤» በማለት ነው፡፡ የማኅበሩ ልሳን የኾነችው ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ በወቅቱ «የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንበሕዝብ ቆጠራ ውጤት ጥርጣሬ እንዳላት አስታወቀች» በሚል ርእስ ዘግባለች፡፡ /16ኛ ዓመት ቁጥር 71፣ ቅጽ 16 ቁጥር 168፤ከታኅሣሥ 16 – 30 ቀን 2001 ዓ.ም/፡፡

በመጀመሪያ ደረጃ መግለጫው የተሰጠው በቤተ ክርስቲያኒቱ ነው፡፡ ይህም መግለጫ በራሱ አክራሪ አያሰኝም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም ይህን ከመግለጽ/ከማስታወቅ አልፎ የሰጠው መግለጫ የለም፡፡ በምንም መስፈርት የማኅበረ ቅዱሳንን ተቋማዊ ሰውነት ወይም የማኅበሩን አባላት የሃይማኖት አክራሪነት ትእምርት አድርጎ አያስወስድም፡፡

የመንግሥት የሃይማኖት አክራሪነት ብያኔ ማኅበረ ቅዱሳንን አይገልጽም

የኢትዮጵያ መንግሥት ራሱ በየሰነዶቹ እንደገለጸው፣ የሃይማኖት አክራሪነትን የሚመለከተው ከሃይማኖት ሳይኾን ከልማት፣ ዴሞክራሲና ሰላም አንጻር ብቻ ነው፡፡ ምንም እንኳን እንዲህ ዓይነቱ ኀልዮት አከራካሪ ቢኾንም መንግሥት፣ «እኔ አንድን ተቋም ወይም ግለሰብ የሃይማኖት አክራሪ ነው የምልበት የራሴ የብያኔ መስፈርት አለኝ» ካለ መብቱ ነው፡፡ የትኛውም ሀገር ከራሱ ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊና ምጣኔ ሀብታዊ ኹኔታዎች አንጻር መበየን ስለሚችል፡፡ መስፈርቱንም «የሃይማኖት አክራሪነትና የፀረ አክራሪነት ትግላችን» በሚል ርእስ ለመንግሥት አመራሮች ሥልጠና በቀረበው ሰነድ እና «ልማት፣ ዴሞክራሲና የሃይማኖት አክራሪነት» በሚል ርእስ በፌዴራል ጉዳዮች የሃይማኖት ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀው ጽሑፍ እንዲሁም በአዲስ ራእይ የንድፈ መጽሔትም ሲያትተው እንደሚከተለው ይላል፡-
  • በዜጎች የእምነት ነጻነት አለማመን፤ በማስገደድ የራስን እምነት ለማስያዝ መንቀሳቀስ፤ እምነት ለመያዝ ያለውን ነጻነትበኀይል በማስገደድ መገደብ ወይም መከላከል፤
  • በሃይማኖት እኩልነት አለማመን፤ የእኔ ይበልጣል የሌላኛው ያንሳል በሚል መንቀሳቀስ፤ ሁሉም እኩል መኾኑ የእኔንሃይማኖት ክብርና ሞገስ ይቀንሳል በሚል ተግባራዊ እንቅስቃሴ ማካሔድ፤
  • መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው የሚለውን መንግሥታዊ መርሕ በመጣስ መንግሥታዊ ሃይማኖት ካልሆንኩ ወይምሃይማኖታዊ መንግሥት ከሌላ በሚል ይህንኑ ለማሳካት በተግባር መንቀሳቀስ፤

በእነዚህ የመንግሥት የሃይማኖት አክራሪነት መስፈርትነት ማኅበረ ቅዱሳን ሲመዘን ማኅበሩ አንዱንም አሟልቶ አይገኝም፤ ወይም ሦስቱም የብያኔ መስፈርቶች ማኅበረ ቅዱሳንን አይመለከቱም፡፡ እስኪ አንድ በአንድ እንመልከታቸው፡፡

በዜጎች የእምነት ነጻነት አለማመን፤ ከዚህ አንጻር ማኅበረ ቅዱሳን ሲታይ እምነቱን ከመግለጽ አልፎ ለዜጎች እምነት ነጻነት መከበር የድርሻውን ተወጥቷል፡፡ ይኸውም ሌሎችን በማስገደድ የራሱን እምነት ለማስያዝ መንቀሳቀስ ወይም የሌሎችን የእምነት ነጻነት በኀይል መገደብ ፀረ ሕገ መንግሥታዊ ብቻ ሳይኾኑ ኢ-ሃይማኖታዊ ድርጊት መኾኑን በይፋ የገለጸ ማኅበር ነው፡፡ ያለአንዳች ማጋነን በፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የሃይማኖት ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ተቋቁሞ የሕገ መንግሥት ትምህርት ከመጀመሩ በፊት፣ ማኅበረ ቅዱሳን የእምነት ነጻነት በሕገ መንግሥቱ ብቻ ሳይኾን በሌሎቹም የሀገሪቱ ሕጎች ያለውን ቦታ ከ1996 ዓ.ም ጀምሮ በመጽሔቱና በጋዜጣው አስተምሯል፡፡ ይህን ያደረገው ደግሞ በመንግሥት ወይም በሌላ ኀይል ትእዛዝ አይደለም፡፡ የዜጎችን የእምነት ነጻነት በመሠረቱ ከማመን ነው፡፡

ማኅበሩ ይህን እምነቱን «ሐመረ ጽድቅ» በሚል ርእስ በ1996 ዓ.ም ባሳተመው የሐመር መጽሔትና የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ልዩ የጋራ ዕትም፣«የእምነት ነጻነት በኢትዮጵያ ሕግ» በሚል በተዘጋጀው መጣጥፍ ላይ፣ «የእምነት ነጻነት ሰፋ ባለ መልኩ ሲታይ የኅሊና ነጻነትማለትም ማንም ሰው ያለፍላጎቱ ማንኛውንም ዐይነት ሃይማኖት ወይም እምነት እንዲቀበል አይገደድም ማለት ነው፡፡ ማንም ሰውበማንኛውም መንገድ አንድን ሃይማኖት ከሌላው በመምረጡ ወይም ምንም ዐይነት ሃይማኖት እንዳይኖረው በመፈለጉ ምክንያትበምንም መንገድ አይቀጣም፡፡ የአንድ ሰው የሃይማኖት እምነት የግል ጉዳይ እንጂ በመንግሥት ባለሥልጣናት ወይም በሌሎችሰዎች አስገዳጅነት የሚመረጥ ወይም የሚተውና የሚለውጥ ጉዳይ አይደለም፤» ሲል ገልጿል፡፡

ከዚህም በተጨማሪ ማኅበሩ በዚሁ መጣጥፍ ላይ የእምነት ነጻነት በሀገራችን ያለውን ሕጋዊ ይዞታና ጥበቃ ሲያትት እንዲህ ብሏል፡-

የእምነት ነጻነት በሕገ መንግሥቱ ልዩ ቦታ ከተሰጣቸው መሠረታዊ የሰው ልጆች መብቶችና ነጻነቶች አንዱ ነው፤. . . በሀገራችን ማንም ሰው የመረጠውን እምነት የመከተል፣ የማስተማርና የማስፋፋት መብት አለው፡፡ መንግሥትን ጨምሮ ማንኛውም ሰውጣልቃ በመግባት በሌላው ሰው የእምነት ነጻነት ላይ ተጽዕኖ እንዳይደረግበት የሕግ ጥበቃ አለ፡፡ ስለዚህ በሕጉ መሠረትየሌሎችን ሰዎች ነጻነትና መብት ለመጠበቅ ከተቀመጠው ገደብ ውጭ ማንም ሰው በማንኛውም ቦታና ጊዜ ሥርዐተ አምልኮቱንእንዳይፈጽም ሊከለከል ወይም ማንኛውም ተጽዕኖ ሊደረግበት አይገባም፡፡ /ሐመረ ጸድቅ፣ 1996፣55/፡፡

ከዚህ ሁሉ መረዳት የሚቻለው ማኅበረ ቅዱሳን በሃይማኖት አክራሪነት ስሜት የሌሎችን የእምነት ነጻነት መብት አለመቀበል ወይም መገደብ ይቅርና የራስን እምነት አጽንቶ ከመያዝ ጋራ ኦርቶዶክሳውያን በሙሉ የሌሎችን የእምነት ነጻነት እንዲያከብሩ ብርቱ ጥረት ማድረጉን ነው፡፡ እንዲያውም አንዳንድ መንግሥታዊ ያልኾኑ አካላት እንዲህ ዐይነቱን ሕገ መንግሥታዊ መብት መጣሳቸውንም በዚህ ጽሑፍ እንዲህ ሲል አጋልጧል፡፡

አንዳንድ መንግሥታዊ ያልኾኑ ገባሬ ሠናይ ድርጅቶች በሚሰጡአቸው ማኅበራዊ አገልግሎቶች ዜጎችን በድርጅቶቹ የሚደገፈውንእምነት ካልተቀበሉ አድልዎ ይፈጽሙባቸዋል፡፡ በተለይ ትምህርት፣ በማናቸውም ረገድ ከሃይማኖት፣ ከፖለቲካ አመለካከትናከባህላዊ ተጽዕኖ ነጻ በኾነ መንገድ መካሔድ እንዳለበት በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 90/2/ በግልጽ ተደንግጎ እያለ በአሁኑ ሰዓትበአንዳንድ መንግሥታዊ ባልኾኑ በጎ አድራጊ ድርጅቶችና የእምነት ተቋማት በተቋቋሙ ት/ቤቶች የሚማሩ ሕፃናትና ወጣቶችከወላጆቻቸው የወረሱትን ሃይማኖት እንዲለውጡ ይገደዳሉ፡፡ ፈቃደኛ ካልኾኑ ደግሞ ሌሎች ምክንያቶች እየተፈለጉ ከትምህርትገበታቸው እንዲወገዱ የሚደረግበት አጋጣሚ እየታየ ነው፡፡ በአንዳንድ የመንግሥት የትምህርት ተቋማትም ሓላፊዎችበተማሪዎቻቸው የእምነት ነጻነት ላይ የሀገሪቱ ሕግ ከሚፈቅደው ውጭ ገደብ የሚጥሉበት ኹኔታ አለ፡፡

እነዚህ ድርጊቶች የሀገሪቱ የበላይ ሕግ የኾነው የሕገ መንግሥቱን ድንጋጌ የሚጥሱ በመኾናቸው የድርጊቱን ፈጻሚዎች ተጠያቂነትየሚያስከትል ነው፡፡ እዚህ ላይ መብቱን የማስከብር ሓላፊነትና ግዴታ የተጣለባቸው በየደረጃው ያሉ የመንግሥት ባለሥልጣናትተጠያቂነት ስላለባቸው ተገቢውን የእርምት ርምጃ መውሰድ ይኖርባቸዋል፡፡


ማኅበረ ቅዱሳን የራሱን እምነት በሌሎች ላይ ለመጫን እንዲያመቸው የሌሎችን የእምነት ነጻነት በኀይል ወይም በጉልበት ሊገድብ ይቅርና በአመለካከት እንኳን እንዲህ ዐይነቱ ኢ-ሃይማኖታዊ ድርጊት የሚታይበት ማኅበር አለመኾኑን በግልጽ መረዳት ይቻላል፡፡ ከዚህ አኳያ ማኅበረ ቅዱሳን የሃይማኖት መከባበር ትእምርት እንጂ የሃይማኖት አክራሪነት ትእምርት ተደርጎ ሊወሰድ የሚችል ማኅበር አለመኾኑን ብያኔው ይገልጣል፡፡

ሌላው የመንግሥት የሃይማኖት አክራሪነት ብያኔ በሃይማኖት እኩልነት አለማመን ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ጥንቱንም ቢኾን በዚህ ረገድ የአመለካከትም ኾነ የተግባር ችግር የለበትም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን በሃይማኖት ልዩነት መከባበር ላይ ያለውን እምነት በተለያዩ ጊዜ ገልጿል፡፡ በሃይማኖት ልዩነት መከባበርን የሚተነትኑ ጽሑፎችን በልሳኖቹ አስተናግዷል፡፡ በሐመር መጽሔት መስከረም/ጥቅምት፣ 1999 ዓ.ም. ዕትሙ «ሽብር ሃይማኖት የለውም» በሚል ርእስ ስለ ሽብርተኝነትና የሽብር መሣሪያ ስለኾኑት አክራሪነትና ጽንፈኝነት የሚተነትነውን ጽሑፍ ማስታወስ ብቻ በቂ ነው፡፡ በዚህ ጽሑፍ ስለ ሃይማኖት እኩልነት የሰፈረውን ሐሳብ እንመልከት፡፡

. . .ስለዚህ ማንኛውምና የየትኛውም እምነት ተከታይ የእምነቱን አስተምህሮ በመከተል በራሱ የተስተካከለ ሕይወት ሊኖርናየተቻለውን ሊያደርግ ይገባል፡፡ የራሱን ሃይማኖት አጥብቆ ሊከተልና የሌሎችንም ሃይማኖት ሊያከብር ይገባል፡፡ ከመወያየት ይልቅከአንተ የኔ ይሻላል ወይም ይበልጣል እያሉ ሳይፎካከሩና ሳይወራረዱ እርስ በርስ ተከባብረው ሊኖሩ ይገባል፡፡ ሃይማኖትን ሽፋንአድርገው የሚነሡ ጽንፈኛ ቡድኖችና ግለሰቦች ለመከላከል ዋናው መንገድ ሰላምን፣ ፍቅርን፣ በልዩነት መቻቻልንና አንድነትንመስበክ፣ ማስተማርና በተለያዩ እምነት መሪዎች መካከል መከባበርንና መዋደድን ማስፈን ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን እንዲህ ዓይነቱን የሃይማኖት እኩልነት መርሕን ያከበረና የሚተነትን ጽሑፍ ብቻ አይደለም ያስተናገደው፡፡ ከሀገሪቱ ሕግ አንጻር የሃይማኖት እኩልነት ሲባል ምን ማለት እንደኾነ ለሁሉም በሚኾን መልኩ ያስተማረ ማኅበር ነው፡፡ ይህንንም በ2001 ዓ.ም በታተመው «ሐመረ ተዋሕዶ የሐመር መጽሔት ልዩ ዕትም» ላይ «ሃይማኖት በመድበለ ሃይማኖት ማኅብረሰብ» በሚል ርእስ የተዘጋጀውን መጣጥፍ መመልከት ከበቂ በላይ ማረጋገጫ ነው፡፡ ጽሑፉም የሚያጠነጥነው ሀገራችን ኢትዮጵያ የመድበለ ሃይማኖት ማኅበረሰብ ሀገር እንደ መኾኗ መጠን ሁሉም ቤተ እምነት ከእነርሱ ውጪ ካሉ ቤተ እምነቶች ጋራ እንዴትና በምን ኹኔታ ተከባብረው መኖር እንዳለባቸውና በመድበለ ሃይማኖት ማኅበረሰብ ውስጥ የሕግ የበላይነትን ከማረጋገጥ አኳያ የሃይማኖት እኩልነትና ነጻነት ከሕግ አንጻር በምን አግባብ መፈታት እንዳለበት የሚያመለክት ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በመርሑ ከማመን በላይ በተግባር ብዙ ርቀት መጓዙን ከዚህ መረዳት ይቻላል፡፡ ጽሑፎቹ «የእኔ ይበልጣል፣ የሌላውያንሣል» በሚል ትምክህት ሌላውን ለመድፈቅ አለመነሣቱንም በሚገባ የሚገልጹ ሐቆች ናቸው፡፡ «ሁሉም እኩል መኾኑ የእኔን ሃይማኖትክብርና ሞገስ ይቀንሳል» በሚል ተግባራዊ እንቅስቃሴ አለማካሔዱን ብቻ ሳይኾን የሃይማኖት እኩልነት መርሕን በአግባቡ ተንትኖ እየተገበረው ያለ ማኅበር መኾኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ከዚሁ መርሕ በመነሣት «ክርስትናና እስልምናን ጨምሮ ማንኛውም ሃይማኖት በመሠረቱ የሚሰብከው በሰላም አብሮ ተቻችሎ መኖር ነው፤» በማለት የሌሎችንም ቤተ እምነታት ሰላም ወዳድነት ዕውቅና የሰጠ የአብሮነትና የመከባበር ትእምርት ነው ማኅበረ ቅዱሳን፡፡ /ሐመር፣ መስከረም/ጥቅምት 1999 ዓ.ም.፣ 22/።

የመጨረሻው የመንግሥት የሃይማኖት አክራሪነት ብያኔ፣ «መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው የሚለውን ሕገ መንግሥታዊ መርሕ በመጣስ መንግሥታዊ ሃይማኖት ካልኾነ ማለት ወይም ሃይማኖታዊ መንግሥት ከሌለ በሚል ይህንኑ ለማሳካት በተግባር መንቀሳቀስ» የሚል ነው፡፡ ከዚህ የሃይማኖት አክራሪነት ብያኔያዊ መስፈርት አንጻር ማኅበረ ቅዱሳን ሲፈተሽ ፍርጃው ተገቢ አይደለም፡፡

የፍርጃውን አስገራሚ ገጽታ ጉልሕ የሚያደርገው ደግሞ «የሃይማኖት አክራሪነትና የፀረ አክራሪነት ትግላችን» በሚል ርእስ ለአመራር ሥልጠና በተዘጋጀው ሰነድ ላይ የሰፈረው አቋም ነው፡፡ የሥልጠና ሰነዱም ማኅበረ ቅዱሳንን ሲገልጸው፣ «ማኅበረ ቅዱሳን የእምነትነጻነትን፣ የሃይማኖት እኩልነትንና መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው የሚለውን ሕገ መንግሥታዊ መርሕ ይቃወማል»በማለት ነው፡፡

ዳሩ ግን ማኅበረ ቅዱሳን በሰነዱ ላይ እንደተቀመጠው የእምነት ነጻነትን፣ የሃይማኖት እኩልነትንና መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው የሚለውን ሕገ መንግሥታዊ መርሕ ሊቃወም ይቅርና እንዲያውም ሐመር መጽሔትና ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ አለኝታነቱን አረጋግጠው በርእሰ አንቀጾቻቸው በተደጋጋሚ አስፍረዋል፡፡ ለዚህም የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣን 14ኛ ዓመት ቁጥር 21፣ ቅጽ 14 ቁጥር 121 ኅዳር 1999 ዓ.ም ዕትም ብቻ መመልከት በቂ ነው፡፡ አይደለም ማኅበረ ቅዱሳን ለመኾኑ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን «ክርስቲያናዊ መንግሥት» ብቻ የሚል አስተሳሰብ ያለው የት ነው? በሀገሪቱ ሕግም ኾነ በሃይማኖታቸው መሪ ተቋም ውስጥ ከማይተዳደሩትና በሌላ መንገድ ከሚንቀሳቀሱ ዓለም ዓቀፍ የእስልምና አክራሪ ቡድኖች ጋራ ማኅበረ ቅዱሳን ተደምሮ የሚፈረጅበት መስፈርትም ግልጽ አይደለም፡፡

ማኅበረ ቅዱሳንና አባላቱ የተገነቡበት ሥነ ልቡና ለአክራሪነት የተመቸ አይደለም

በርግጥ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም ከመስከረም 1 – 15 ቀን 2002 ዓ. ም. ለኅትመት በዋለችው ስምዐ ጽድቅጋዜጣ ላይ እንዳመለከቱት፣ «አክራሪ» ማለት የሃይማኖቱን ሕግ አክብሮ የሚኖር፣ ተግቶ የሚጾም፣ የሚጸልይ፣ በሃይማኖቱ ላይ ለሚነሡ ጥያቄዎች መልስ የሚሰጥና ታሪኩንና ቤተ ክርስቲያኑን የሚወድ፣ ለሃይማኖቱ የሚቀና፣ የማይዋሽ ወይም ወደ ከፍተኛ ሥነ ምግባራዊ ሕይወት ራሱንም የሃይማኖት ወገኑን ሁሉ ለማድረስ የሚተጋ ከኾነ የማኅበራችንን አባላት ሊገልጽ ይችላል፡፡ ሰዎች ምናልባት በልማድ በዚህ ብያኔ ለመጥራት ፈልገው ከኾነ ችግር ላይኖረው ይችላል፤ ነገር ግን በዚህ ኹኔታ የሚመላለሱት ክርስቲያኖች «አክራሪ» እያሉ ከማጥላላት ይልቅ አጥባቂ፣ ዐቃቤ ሃይማኖት፣ ቀናዒ ቢባሉ የተሻለ እንደኾነ እሙን ነው፡፡

በሌላ በኩል ግን «አክራሪ» የሚለው ቃል በሰነዱ ላይ እንደተቀመጠው፣ «አብያተ ክርስቲያናትንና ገዳማትን ለፖሊቲካ ዓላማ ጥቅም ላይ ማዋል፣ ከተቃዋሚ የፖሊቲካ ድርጅቶች ጋር በመተሳሰር ፀረ መንግሥት ቅስቀሳና አድማ ማስተባበር፣ በሃይማኖቶች መካከል የከረረ ጥላቻን በመዝራትና በማስተጋባት በሕዝብ ውስጥ የመተማመን፣ የመከባበርና የመቻቻል ዕሴት እንዲሸረሸር ሌት ተቀን መረባረብ» ከኾነ ግን ከማኅበራችን አቋምና ከአባሎቻችን ሥነ ልቡና እጅግ የራቀ አሉባልታ ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ፀረ መንግሥት ቅስቀሳና አድማ ሊያደርግ ይቅርና በጅማና ኢሉ አባቦራ አክራሪዎች በክርስቲያኖች ላይ ግድያ በፈጸሙበት ወቅት በስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 14ኛ ዓመት ቁጥር 21፣ ቅጽ 14 ቁጥር 121 ኅዳር ዕትም ላይ የወቅቱ መልእክት ያለው ዜናና ርእሰ አንቀጽ ጽፏል፡፡ ርእሰ አንቀጹ የመንግሥትንም ጥረት የሚያሳይና ለወደፊቱ መንግሥት፣ ቤተ ክርስቲያንና ምእመናን ማድረግ ያለባቸውን የሚጠቁም ነበር፡፡

በዜናውም የመንግሥትን ጥረት «የሕዝቡን ሰላም በሚያደፈርሱ ኀይሎች ላይ መንግሥትና ኅብረተሰቡ የተጠናከረ ርምጃ እየወሰዱነው፡፡ . . . በጅማና ኢሉ አባቦራ አህጉረ ስብከት አንዳንድ ወረዳዎች በተከሰተው ግጭት ለችግሩ መንሥኤ ናቸው የተባሉትምሕግ ፊት እየቀረቡ ነው» በማለት ነበር የገለጸው፡፡ እንዲህ የዘገበው ማኅበር ነው እንግዲህ ፀረ – ሕገ መንግሥት የተባለው፡፡ እንዲህ አድርጎ ከፈረጀ ማኅበረ ቅዱሳን በኀይል እስላሞችን ወይም ፕሮቴስታንቶችን ኦርቶዶክስ አድርጓል? መስጊድ አቃጥሎ እስላሞችን ወይም የማምለኪያ ቦታዎችን አቃጥሉ ፕሮቴስታንቶችን ገድሏል? ለሚሉ ጥያቄዎችም መልስ መስጠት ይገባ ነበር፡፡ አለበለዚያ የመንግሥት አካሂደዋለኹ የሚለው የፀረ አክራሪነት እንቅስቃሴ በመንግሥት መርሐ ግብር ተጠቅመው ስውር ዓላማቸውንና ፍላጎታቸውን ለማስፈጸም የተዛባ ፍረጃና የተሳሳተ አቻ ፈጠራ ላይ ለተሰማሩ አካላት መሣርያነት አለመጋለጡን በምን ማረጋገጥ ይቻላል?

ይኹንና ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያኒቱ የበላይ አካል በቅዱስ ሲኖዶስ የጸደቀ ሕግና መተዳደሪያ ደንብ ያለው የቤተ ክርስቲያኒቱ አካል እንጂ ሌላ የእምነት ጽንፍ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ የምታውቃቸው ጋዜጣ፣ መጽሔትና መካናተ ድሮች አሉት፤ ምን እንደሠራም በግልጽ ማየት ይቻላል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን እንደተፈረጀው ሳይኾን መቻቻልን በተመለከተ ከማኅበሩ ሚዲያዎች ቀድሞ የዘገበ ነበር ለማለትም የሚቻል አይመስለንም፡፡

በስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ጥቅምት ወር 1999 ዓ.ም ዕትም በጅማና በኢሉ አባቦራ የደረሰውን ጥቃት በዜናው ዘግቦ ነበር፡፡ ማኅበሩ ይህን ያደረገው ጥቃቱ በቤተ ክርስቲያን ላይ የተፈጸመ በደል ስለኾነ ብቻ አይደለም፡፡ አንድን ነገር እየሰሙ እንዳልሰሙና እንደሌለ ከመቁጠር ይልቅ ችግሩን በትክክል አሳውቆ ለመፍትሔው መሥራት ይገባል ብሎ ስለሚያምን ብቻ ነው፡፡

በተጠቀሰው የጋዜጣው ዕትም ባወጣው ርእሰ አንቀጽም የቆየው የመቻቻል ባህል ዳብሮ እንዲቀጥል የሚጠይቅ፣ የሀገር ሽማግሌዎችና የአካባቢው የመንግሥት አካላት ሊፈጽሙት ይገባል የሚላቸውን ተግባራት በማመልከት የማኅበሩን አቋም አንጸባርቋል፡፡ በቀጣዩ ወር ኅዳር 1999 ዓ.ም ዕትም ግን በመቻቻል እንዴት መኖር እንደሚገባ የሚያሳይ ሰፊ ሽፋን ያለው ሥራ ተሠርቷል፡፡ የመቻቻልን ምንነት፣ በኢትዮጵያ የነበረውን ታሪካዊ ቦታና አስፈላጊነት በመተንተን የሁሉም ቤተ እምነት ተከታዮች በዚሁ ሀገራዊና መንፈሳዊ ባህላችን ጸንተው እንዲኖሩ የሚያግባባ ነበር፡፡ ርእሰ አንቀጹ ደግሞ ከላይ የተገለጹትን አሳቦች በማጽናት ተግባብቶና ተከባብሮ መኖር የሚያስገኘውን ጥቅም ካካተተ በኊላ ለዚህ ባለድርሻ የኾኑ አካላት ሁሉ ድርሻቸውን እንዲወጡ የሚጋብዝ ነበር፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን «በሃይማኖቶች መካከል የከረረ ጥላቻን ሊዘራና ሊያስተጋባ» ይቅርና ሁሉም የእስልምና ተከታዮች አንድ ዓይነትና አክራሪዎች አለመኾናቸውን የሚያሳዩ ሥራዎችን የሠራ ማኅበረ ነው፡፡ ለምሳሌ፣ በስምዐ ጸድቅ ጋዜጣ ጥር 15 – 30 ቀን 2000 ዓ.ም በአርሲ የእስልምና ተከታዮች ለቤተ ክርስቲያን ግንባታ ያደረጉትን አስተዋፅኦ ከዘገበ በኋላ በርእሰ አንቀጹ ደግሞ የሁለቱን የእምነት ተከታዮች መረዳዳት አብነት በማድረግ ድርጊቱን አወድሷል፡፡

ከየካቲት 15 – 30 ቀን 2000 ዓ.ም ዕትም ደግሞ በወልቂጤ አካባቢ በቤተ ክርስቲያን ምረቃ ላይ ድንጋይ የወረወሩ አክራሪዎች ልጆቻቸውን ለሕግ አካላት አሳልፈው በመስጠት ለመቻቻሉ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያደረጉትን ሙስሊም ሽማግሌዎችን ድርጊት በአዎንታዊ ዘግቧል፤ ሥራቸውም ተወድሷል፡፡ ይህም መቻቻልን በተግባር ያሳየ ዘገባ ብቻ ሳይኾን የማኅበረ ቅዱሳን ትእምርተ መከባበር መኾኑንም ያሳየ ነበር፡፡

የአፅራረ ቤተ ክርስቲያን ቅዠት?

በርግጥ ማኅበሩ ወጣቱን በሃይማኖት አክራሪነት ይቀርጻልን የሚለውን ለመረዳት ሌላውን የማኅበሩን ሥራዎች ማየት የሚገባ ይመስለናል፡፡ ለአብነትም ማኅበረ ቅዱሳን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን የሚያስተምርባቸው ኻያ ያህል የመማርያ መጻሕፍት ታትመው አገልግሎት ላይ ከዋሉ ቆይተዋል፡፡ ትምህርቱ የሚሰጠው በይፋ በቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ሰው የኾነ ፍጡር ሁሉ ሊከታተለው የሚችለው ነው፡፡ እነዚህ ሁሉ ይፋዊ በኾነ መንገድ በሚሰጡበትና መጻሕፍቱን ሁሉ መመርመር በሚቻልበት ኹኔታ ያለምንም ማስረጃ «ወጣቶችን በሃይማኖት አክራሪነት ይቀርጻል» ማለት ስሕተት ነው፡፡

ይህን አገላለጽ የሚያይና የማኅበሩን ሥራ በርግጥ የሚያውቅ የዚህ አሳብ አፍላቂዎች በመንግሥት የፀረ አክራሪነት አጀንዳ አስታከው ማኅበረ ቅዱሳንና ቤተ ክርስቲያንን ለማሳጣት ወይም ለማጋጨት የተነሡና ሃይማኖታዊ መግፍኤ ያላቸው ኀይሎች ሊኾኑ አይችለምን? በርግጥ የማይኾኑበትስ ምክንያት ሊኖር ይችል ይኾን?

ቀደም ብለን እንደገለጽነው ማኅበረ ቅዱሳን ቤተ ክርስቲያን ትውልዱን በትምህርቷ ትዋጅ ዘንድ ሥርዐተ ትምህርት ቀርጾ ንጹሕ ቃለ እግዚአብሔር ብቻ የሚያስተምር ማኅበር ነው፡፡ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖትን ይጠብቃል ተብሎ ይታማ ካልኾነ በቀር በአክራሪነት ሊወነጀል አይችልም፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን መዋቅራዊ ቁመና ለአክራሪነት ብቻ ሳይኾን ለፖሊቲካም የሚመች አይደለም፡፡ በስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ መስከረም 1 – 15 ቀን 2002 ዓ.ም ዕትም ላይ የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም እንዳመለከቱት፣ ማኅበሩ ሃይማኖታዊ አገልግሎት ለመስጠት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር የተቋቋመ የአገልግሎት ማኅበር ነው፡፡ ማኅበሩም እንደ ተቋም የሚሰጠው አገልግሎት ሃይማኖታዊ ነው፡፡ መቼም ቢኾን ለየትኛውም ዐይነት የፖለቲካ አደረጃጀት ለማገዝ/ለመሥራት ተቋማዊ ፍላጎት የለውም፡፡

በዚህ አጋጣሚ ማኅበሩ በመተዳደሪያ ደንቡ ላይ የገለጸውን አቋሙንም አስታውሶ ማለፍ የሚገባ ይመስላል፡፡ በአንቀጽ 5 ላይ «ማኅበሩበማንኛውም የፖለቲካ እንቅስቃሴ ምንም ዓይነት ጣልቃ ገብነት አይኖረውም» በማለት ማኅበሩ ፖለቲካ ላይ ጣልቃ የማይገባ መኾኑን ይገልጻል፡፡ የዚህን አንቀጽ ይዘት ተግባራዊ ለማድረግ እንዲቻል በማኅበሩ ያሉ የተወሰኑ አባላት በሓላፊነት ላይ እያሉ የማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ አባል እንዳይሆኑ በ1998 ዓ.ም የሥራ አመራር ጉባኤው ወስኗል፡፡

በውሳኔውም መሠረት፡- የሥራ አመራር ጉባኤ አባላት፣ የሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ አባላት፣ የኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ክፍልአባላት፣ የኤዲቶሪያል ቦርድ አባላት፣ መደበኛ መምህራን፣ የማኅበሩ ጋዜጠኞች፣ የማእከላት ሰብሳቢዎች በሓላፊነት እያሉየማንኛውም የፖለቲካ ፓ­ርቲ አባል መኾን አይችሉም፡፡ ስለኾነም ማኅበሩ እንደ ተቋም የትኛውንም የፖለቲካ አስተሳሰብ በመደገፍ ወይም በመቃወም ከ­ርቲዎች ጋር ግንኙነት ስለማይኖረው ለማንም ስጋት ወይም ዕድል ሊሆን የሚችል ተቋማዊ ምቹነት የለውም፡፡

ይህ ባይኾን ኖሮ ከመላዋ ኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና የተለያዩ ማኅበራዊ ዳራዎች የተሰበሰቡ አባላቱ በየትኛው የፖለቲካ አቋም ሊስማሙና ቤተ ክርስቲያንን ሊያገለግሉ ይችላሉ? የማኅበሩ አቋም ፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነት እንዳይኖረው የተወሰነው ግን ለዚህ ሲባል ብቻ አይደለም፡፡ በአንድ የፖለቲካ ፓ­ርቲ ውስጥ በርእዮተ ዓለም የተሰባሰቡ የተለያዩ ሃይማኖት ተከታዮች ይኖራሉ/ፓ­ርቲው አክራሪ ሃይማኖታዊ ፓ­ርቲ እስካልኾነ ድረስ/፤ እንደዚሁ ሁሉ የተለያየ የፖሊቲካ አመለካከት ያላቸው ሰዎች የአንድ ቤተ እምነት ተከታዮች ይኾናሉ፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም ሃይማኖታዊ ዕሴታቸውንና ለቤተ ክርስቲያናችን ማበርከት አለብን የሚሏቸው ዓላማዎች የሚያገናኟቸው ሰዎች የተሰበሰቡበት ማኅበር ነው፡፡ ስለዚህ ዓላማው አንድና አንድ ነው – ቤተ ክርስቲያንን ማገልገል ብቻ፡፡ ስለኾነም እንደ ማኅበር በየትኛውም የፖሊቲካ ርእዮተ ዓለም ላይ ጣልቃ ገብነት የለውም፤ ወደፊትም አይኖረውም፡፡

የብዥታው ምንጭና ምንነት

እውነታው ከላይ የተመለከትነው ከኾነ ማኅበረ ቅዱሳን «አክራሪ» ያሰኘው የብዥታው ምንጭና ምንነት ምን ይመስላል? የሚለው ሌላው ወሳኝ ጥያቄ ነው፡፡
የመጀመሪያው፦ የአፅራረ ቤተ ክርስቲያን የተሳሳተ መረጃ ነው፡፡ አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ንጽሕት ርትዕት የኾነችውን እምነትና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶን ህልውና ለማጥፋት በመፈታተን ለዘመናት ሌት ተቀን ሳያቋርጡ እንደሚጥሩት ሁሉ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጅ የኾነው የማኅበረ ቅዱሳንን ቅን መንፈሳዊ አገልግሎትም እንዲኖር አይፈልጉም፡፡ በተለይም በክርስትና ስም እንቀሳቀሳለን የሚሉ የተለያዩ የእምነት ድርጅቶችና የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ አራማጆች ሁሉ፣ ከውጭም ኾነ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጉያ ውስጥ ኾነው የሚያደርሱትን ጥቃትና ቡርቦራ በመከላከል፣ ለቤተ ክርስቲያን አባቶችና ለምእምናን በማሳወቅ የሚያደርገውን ቀና ጥረት በሚገባ ያውቁታል፡፡

በጌታችንና በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሠረት ላይ ጸንታ በእርሱ ጥበቃ የምትኖረውን ቤተ ክርስቲያን በመፈታተን እኩይ ዓላማቸውን በፈለጉት መጠን እንደልባቸው ለማሳካት አለመቻላቸውን ተረድተውታል፡፡ ለእኵይ ተግባራቸው እንቅፋት የኾነውን ማኅበር ንጹሕ መንፈሳዊ አገልግሎት ለማስቆም ባገኙት አጋጣሚና መድረክ ሁሉ የተሳሳቱና የተፈበረኩ መረጃዎችን ይሰጣሉ፡፡ የፍረጃው ምንጭ ይኸው የተሳሳተና የተፈበረከ መረጃ ነው፡፡
የማኅበረ ቅዱሳንን አገልግሎት ለማስተጓጎል የሚጣደፉት እነዚህ የኑፋቄና የጥፋት ኀይሎች በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ መዋቅሮች ውስጥ ሓላፊነት ይዘው ቤተ ክርስቲያንን ለሚያጠፉ አካላት የማይታይ ስውር እጅ ኾነው ለመሥራት እየሞከሩ ያሉግለሰቦችና ቡድኖች ማኅበረ ቅዱሳን የተለየ አጀንዳ ያለው ይመስል ስጋት ኾኖ እንዲታይ ያልፈነቀሉት ድንጋይ፣ ያልወጡት ዳገትናያልወረዱት ቁልቁለት የለም፡፡

የራሳቸው ጥቅምና ክብር እንጂ የቤተ ክርስቲያን ንጹሕ ዓላማ የማይታያቸው እነዚህ በእሳት የሚጫወቱ ግለሰቦችና ቡድኖች ሲፈልጉ በጥርጣሬ፣ በመመሪያና ደንብ፣ ሲያሻቸው ደግሞ ስም በማጥፋትና በአባላቱ መካከል መለያየት ለመፍጠር በመሞከር. . . ወዘተ ማኅበረ ቅዱሳንን መቅበር፣ በመቃብሩም ላይ መቆም፤ ከዚያም የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አንድነትና ህልውና አደጋ ላይ ለመጣል ያደረጉት እንቅስቃሴ ሁሉ በእነርሱው ቋንቋ «በማኅበሯ» ሲከሽፍባቸው መንግሥት ታላቅ ሓላፊነት ያለበት አካል እንደ መኾኑ መጠን የሚመች ቦታ ይዘው የራሳቸውን ውስጣዊ ፍላጎት በመንግሥት መርሐ ግብር አሳዝለው ማኅበሩን ያስመታልናል የሚሉትን የሐሰት መረጃ መፈብረክ ተያይዘውታል፡፡

በጥቅሉ የመናፍቃኑንና ቤተ ክርስቲያንን እናድሳለን ብለው የተነሡት የመናፍቃኑ ተላላኪ ቡድኖች ሤራና የአክራሪ እስልምናን እንቅስቃሴ በመረጃ አስደግፎ በማጋለጡ፣ ከክፉ ትምህርታቸው መመለስ ያልፈለጉ የተሐድሶ ኑፋቄ ቡድን አባላት ከቤተ ክርስቲያን ተወግዘው እንዲወጡ ስለተወሰነባቸውና ሌሎችንም የቤተ ክርስቲያን ችግሮች እየተከታተለ ለዕድገቷና ብልጽግናዋ በመሥራቱ በሚልዮኖች የሚቆጠሩ ወዳጆች ማፍራት መቻሉ የእግር እሳት የኾነባቸው አካላት የፍረጃ ውጤት ነው የማኅበሩ «አክራሪ» መባል፡፡

ሁለተኛው፦ የተሳሳተ አቻ ፈጠራ የወለደው ብዥታ ነው፡፡ አንዳንድ የመንግሥት ተቋማትና ሓላፊዎች አንድን ችግር ለመፍታት ሲሉ ሚዛን የጠበቁና የማያደሉ የሚባሉ እየመሰላቸው ማኅበረ ቅዱሳንን ለወሃቢያ የተሳሳተ አቻ ፈጠራ አክራሪ ማለታቸው ሌላው የብዥታው ምንጭ ነው፤ ነገር ግን ይህ ፈጽሞ አግባብ አይደለም፡፡ ከዚህም ውጭ የተሰጣቸውን መንግሥታዊ ሓላፊነት ዘንግተው በራሳቸው የሃይማኖት አመለካከት ምክንያት የማኅበሩን መኖር የማይፈልጉ አካላት የሰጡት መረጃ ሊኾን እንደሚችል መጠርጠር፣ የመረጃውን ፍሰት/አካሔድ/ መመርመርና ተገቢውን እርምት መውሰድ አለመቻልም ለብዥታው መነሻ ነው፡፡

ሦስተኛውና የመጨረሻው፦ የብዥታው ምንጭ፣ ማኅበረ ቅዱሳን «እውነት ነጻ ያወጣችኊል» በሚለው የወንጌል ቃል መሠረት አሉባልታውን ሁሉ እየተከተለ በወቅቱ ምላሽና አጸፋ አለመስጠቱ ነው፡፡ በጊዜ ሒደት ግን የመረጃውን ስሕተት ከማኅበሩ እውነተኛ ማንነት ጋራ አለመግለጻችን ራሳችንን ለከሳሾቻችን የፈጠራና የተሳሳተ መረጃ ረዳት አድርጎ ሊያስቆጥረን ይችል ይኾናል፡፡ የኾነው ኾኖ ማኅበሩ እንደ እምነት የአገልግሎት ተቋምነቱ ላልሠራው ሥራ አይጨነቅም፤ ጊዜ ይወስዳል እንጂ እውነቱን ደግሞ ማንም አይደብቀውም፡፡

ጌታ በወንጌል እንደተናገረው «የማይገለጥ የተከደነ፣ የማይታወቅ የተሰወረ ምንም የለምና» /ማቴ. 10፥26/ የሁሉንም ስውር ተንኮል እግዚአብሔር በጊዜው ጊዜ ይገልጠዋል፡፡ ያን ጊዜ ማኅበሩ ማን እንደኾነም በእውነት ይታያል፡፡ በዚያን ጊዜ ሁሉም የዘራውን ያጭዳል፡፡ ጠብ እየዘራ ያለ አካል ቢኖር እርሱ የጠብ ውጤት የኾነውን መከራ ከዘራው ዘር ማጨዱ አይቀርም፡፡

ከዚህ በኋላስ...

መንግሥት በየትኛውም የእምነት ተቋማት አሉ የሚላቸውን ችግሮች ማንሣቱ ወይም ተቋማቱ ራሳቸው እንዲፈቱ እገዛ መስጠቱ የሚያስመሰግነው ተግባር ነው፤ ነገር ግን የሚያሰራጫቸው መረጃዎች ይህን ተግባሩን ጥያቄ ውስጥ እንዳይከቱት መጠንቀቅ ብቻ ሳይኾን ማስተካከያ ሊሰጥበትም ያስፈልጋል፡፡ አለበለዚያ መፍትሔው መፍትሔ መኾኑ ቀርቶ ለችግር ፈጣሪዎቹ ከለላ ሰጭ እንዳይኾን ያሰጋል፡፡

ሃይማኖታዊ ጉዳይ በተፈጥሮው ውስብስብና በእጅጉ ጥንቃቄ የሚፈልግ ነው፡፡ በኻያኛው ክፍለ ዘመን ሁለተኛው አጋማሽ ላይ በሕንድና ቀደም ብሎም በግሪክ የመንግሥትን ኃይል ተጠቅመው በእውነኞቹ አማኞች ላይ ታላቅ ጥፋት ካደረሱት ውስጥ የአንዳንዶቹን አካላት ታሪክ ማየትም ለእኛ ምሳሌ ሊኾነን ይችላል፡፡ የተሰጣቸውን ሓላፊነት በመጠቀምና የተሳሳተ መረጃ በማቀበል የመንግሥትን አግባብነት ያለው የፀረ አክራሪነት እንቅስቃሴ ከትክክለኛው አቅጣጫ ሊያስቱ የሚችሉ አካላት መሣሪያ እንዳያደርጉት ስጋታችን ታላቅ ነው፡፡ ሐሰት ተደጋግሞ በመነገሩ እውነት ቢመስልም በፍጹምና መቼም እውነት ሊኾን አይችልም፡፡

በሌላ በኩል፣ ሚዛን ለመጠበቅ በሚል ስሜት ሁሉንም አንድ ዓይነት ጥፋት እንዳጠፉ አድርጎ መመልከትና መግለጽም መቆምይኖርበታል፡፡ በዚህ ረገድ መንግሥት ለተለያየ ዓላማ ከሚያወጣቸው ይፋዊ ሰነዶች ጥናትን መሠረት ያደረጉ መረጃዎች ብቻ ይጠበቃሉ፡፡ ለምሳሌ፣ በሃይማኖታዊ ጉዳይ ላይ የተጻፉ ጸሑፎችን በሙሉ ሰብስቦ አጥንቶና ገምግሞ ማውጣት ቢቻል ሕዝቡንም በአግባቡለማስረዳት ይጠቅማል፡፡ ማን መጀመሪያ ምን ብሎ በሌላው እምነት ላይ ጻፈ? የትኞቹ ምላሾች ናቸው? የትኞቹስ የትንኮሳ ጽሑፎች ናቸው? ሌላው ቀርቶ ሃይማኖትን ለማሳመን፣ ሌላውን ለማስረዳት አልያም ለማጣጣል ብቻ የተደረጉት ላይ ቢጠና እንደ ዘይትና ውኃ ተለይተው ከሩቅ የሚታዩ ናቸው፡፡ ነገር ግን ሁሉንም በአንድነት በመፈረጅና በሕግ የተቋቋመውን ካልተቋቋመው እየደባለቁ በመናገር የተፈጸመን ድርጊት ሁሉ በአንድ ላይ በመጫንና በመለጠፍ ውጤት ማምጣት እንደማይቻል ይታወቃል፡፡

ስለዚህ በቂ ማስተካከያዎችና እውነተኛ ገጽታን የሚገልጹ ሥራዎች ለዛሬ ባይደርሱ ለነገ ይጠበቃሉ፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን እንደ ትላንቱ ሁሉ ዛሬም የሃይማኖት አክራሪነትን መቃወም ብቻ ሳይኾን በጽኑ ያወግዛል፤ ማኅበረ ቅዱሳን የሃይማኖት አክራሪነት ሳይኾን የሃይማኖት አጥባቂነት ትእምርት ነውና!!

ተያያዥ መጣጥፎች
ክርስትና "አክራሪነት"ን የሚያበቅል ነገረ ሃይማኖታዊ መሠረት የለውም

ማኅበረ ቅዱሳን አክራሪ ሁኖ የገደለው ሰው የለም

ቀጣዩ የኢሕአዴግ ዒላማ ማኅበረ ቅዱሳን ይኾን?




                                             ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Saturday, October 5, 2013

ዘመነ ጽጌ

ከገነት የተሰደደውን አዳምን ወደ ቀደመ ክብሩና መንበሩ ከዚያም ወደ ሚበልጥ ክብር ለመመለስ የተወለደው ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ገና ከህፃንንቱ ጀምሮ ስደትን እና መከራን ተቀብሏል፡፡
ጌታ ሲወለድ ሰብአ ሰገል «የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት አለ? በምሥራቅ ኮከቡን አይተን ልንስግድለት መጥተናል» እያሉ በኮከብ እየተመሩ በመጡ ጊዜ በይሁዳ፣ በገሊላና በሰማርያ የሮማውያን ተወካይ የነበረው ንጉሥ ሄሮድስ የጌታችን ንግሥና ምድራዊ ንግሥና መስሎት መንግስቴን ሊቀማኝ ነው ብሎ ደነገጠ፡፡ ፊሪሳውያን «መሲህ ተወልዶ ከሮማውያን አገዛዝ ነጻ ያወጣናል፡፡» ብለው ያምኑ እንደነበር ስለሚያውቅም ይህ የተፈጸመ መስሎት ጭንቀቱ በረታ፡፡ የተወለደውን ሕፃንም ለመግደል ተነሳ፡፡
ስለዚህም ሰብአ ሰገልን አስጠርቶ «ሂዱ ሕፃኑን ፈልጉ ፤ ባገኛችሁትም ጊዜ እኔም እንድሰግድለት ወደ እኔ ተመልሳችሁ ያለበትን ንገሩኝ» በማለት በሽንገላ ተናገራቸው፡፡
ጠቢባኑም ከሄሮድስ ከተለዩ በኋላ በኮከቡ እየተመሩ ጉዞአቸውን ቀጥለው ጌታችንን ከእናቱ ጋር አገኙት ፤ ተንበርክከው ሰገዱለት፤ ወርቅ ፣ ዕጣን፣ ከርቤ እጅ መንሻ አቀረቡለት፡፡

የእግዚአብሔር መልአክ ወደ ሄሮድስ እንዳይመለሱ፤ ነገር ግን መንገድ ቀይረው ወደ ሀገራቸው እንዲሄዱ በነገራቸው መሠረት በሌላ መንገድ ወደ መጡበት ተደብቀው ተመለሱ፡፡

«እነርሱም ከሄዱ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በሕልም ለዮሴፍ ታይቶ «ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነስ፤ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ግብጽ ሽሸ፤ እስክነግርህም በዚያ ተቀመጥ አለው፡፡ » /ማቴ. 2 13 14/

ዮሴፍም ተነሣ፤ በዕድሜዋ በጣም ልጅ የነበረችው እመቤታችን ገና የተወለደውን ሕፃን አቅፋ የምትቀመጥበት አህያም ተዘጋጀ፡፡ ጉዞአቸውን ጀመሩ፡፡ ከእስራኤል ወደ ግብጽ በእግር ለመሔድ የሲናን በረሃ ማለፍ የግድ ነው፡፡ በዚያን ዘመን ከእስራኤል ወደ ግብጽ የሚወስዱ ሦስት የተለያዩ መንገዶች ነበሩ፡፡ በሽፍቶች ላለመጠቃት መንገደኞች በቡድን በቡድን ሆነው በእነዚህ መንገዶች ይሔዱ ነበር፡፡

እነርሱ ግን ንጉሥ ሔሮድስ ተከታትሎ ሊይዛቸው ስለሚችል በእነዚህ መንገዶች መሔድ እንደሌለባቸው ግልጽ ነው፡፡ ስለዚህም በእግዚአብሔር መልአክ እየተመሩ ባልታወቁ መንገዶች መሔድ ነበረባቸው፡፡ ለበርካታ ቀናትና ሳምንታት ሸለቆዎችን በመውረድና ኮረብታዎችን እየወጡ ጉዛአቸውን ቀጠሉ፡፡ ሽማግሌው አናጢ ዮሴፍ ከፊት ሁኖ አህያዋን ባልተስተካከለውና ማለቂያ የሌለው በሚመስለው የበረሃ መንገድ ላይ ይመራ ነበር። ሰሎሜም ስንቃቸውን ይዛ ከኋላ ትከተል ነበር፡፡ በጣም አስቸጋሪ እና አስጨናቂ ጉዞ ነበር፡፡ ቀን ቀን የሚያቃጥለውን የፀሐይ ሐሩር ሌሊት ሌሊት ደግሞ የበረሀውን ውርጭ /ብርድ/ መታገል ነበረባቸው ምግባቸውንም በተአምራት ያገኙ ነበር፡፡

በመጨረሻም በመጽሐፈ ስንክሳር እንደተመዘገበው ግንቦት 24 ቀን ግብጽ ደረሱ፡፡ በግብጽም ባሉ የተለያዩ ከተሞች ተዘዋወሩ፣ ጌታም በተለያዩ ቦታዎች በርካታ ተአምራትን አደረገ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ተቀብለው ሲያስተናግዷቸው ሌሎች ደግሞ አሳደዋቸዋል፤ መከራንም አጽንተውባቸዋል፡፡ በዚሁ ስድታቸው ወቅት ጌታ እና እመቤታችን ወደ ኢትዮጵያም መጥው ሀገራችንን ባርከዋል።

ለሦስት ዓመት ተኩል ያህል በስደት ከቆዩ በኋላ ሄሮድስ ሞተ። ሄሮድስም ከሞተ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በግብጽ ለዮሴፍ በሕልም ታይቶ «የሕፃኑን ነፍስ የፈለጉት ሞተዋልና ተነሣ፤ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ አለው፡፡ እርሱም ተነስቶ ሕጻኑንና እናቱን ይዞ ወደ እስራኤል ሀገር ገባ» ማቴ 2-19-21/

ቅዱስ ዮሴፍ ይህንን «.. ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ..» የሚለውን የመልአኩን ቃል የሰማው ቁስቋም በምትባል በግብጽ ባለች ቦታ ነው፡፡

በኋላ በዚህች ቦታ ላይ የእመቤታችን ቤተክርስቲያን ተሰርቶ ቅዳሴ ቤቱ ኅዳር 6 ቀን ከብሯል። ሃያ ሦስተኛው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ቴዎፈሎስ /384-412 ዓ.ም/ ደግሞ በጌታ እና በእመቤታችን ስደት ወቅት የሆነውን ነገር እንዲገለጥለት ለብዙ ጊዜ ጸሎት ካደረገ በኋላ ህዳር 6 ቀን እመቤታችን ተገልጣለት በጉዞው ወቅት የሆነውን ነገር ሁሉ ነግራዋለች፡፡ ስለዚህ ኅዳር 6 ቀን በሁሉም ምሥራቃውያን አብያተ ክርስቲያናት የእመቤታችን ከስደት የመመለሷ ነገር የሚታሰብበት ሁኗል፡፡

በሀገራችን መስከረም 25 ቀን ዘመነ ክረምት አልፎ መስከረም 26 ቀን ዘመነ ጽጌ ይጀምራል፡፡ ጽጌ ማለት አበባ ማለት ሲሆን ዘመነ ጽጌ ማለት የአበባ ዘመን ማለት ነው፡፡ ዘመኑ አበቦች የሚያብቡበትና ሜዳዎችንና ተራሮችን የሚያስጌጡበት ዘመን ነው፡፡ ፍሬ የተባለ ጌታን ያስገኘች እመቤታችን በአበባ ትመሰላለችና ዘመኑ የጌታንና የእመቤታችንን ነገር በአበባና በፍሬ ለመመሰል የተመቸ ነው፡፡

ስለዚህም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከመስከረም 26 ቀን ጀምሮ እስከ ኅዳር 6 ቀን ድረስ የጌታን እና የእመቤታችን ስደት ታስባለች፡፡

በዚህ ዘመን ቅዱስ ያሬድ እና አባ ጽጌ ድንግል ባዘጋጇቸው ድርሰቶች የጌታችን እና የእመቤታችን ስደት በማኅሌት ይታሰባል፤ ምስጋና እና ልመና ይቀርባል። እነዚህን ለየሳምንቱ በሚዘጋጁት ትምህርቶች እናቀርባቸዋለን፡፡

ከዚህም በተጨማሪ ስደቱን ለማሰብና በረከት ለማገኘት በርካታ ክርስቲያኖች ዘመኑን በጾም ያሳልፉታል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በማቴዎስ ወንጌል ትርጓሜው /Homilies on the Gospel of Saint Mathew/ ይህንን ስደት አስመልክቶ ያስተማረውን ትምህርት ከዚህ ቀጥለን አቅርበናል፡፡

ሰብአ ሰገልም ከሄዱ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በህልም ለዮሴፍ ተገልጾ፡- ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሳና ሕፃኑን ከእናቱ ይዘህ ወደ ግብፅ ሽሽ እስክነግርህም ድረስ በዚህ ተቀመጥ አለው እርሱም ተነስቶ ሕፃኑና እናቱን ያዘና ከጌታ ዘንድ በነቢይ ልጄን ከግብፅ ጠራሁት የተባለው ይፈጸም ዘንድ ወደ ግብፅ ሄደ። ሄሮድስም እስኪሞት ድረስ በዚያ ኖረ።

ከዚህ በኋላ ሄሮድስ ሰብአ ሰገል እንደተሳለቁበት ባወቀ ጊዜ እጅግ ተቆጥቶ /ጌታን ለማስገደል በማሰብ / ጌታ በተወለደባት ከተማ በቤተልሔምና በአውራጃዋ የነበሩትን ሕጻናትን አስገደለ፡፡ /ማቴ. 1.13-18/

እዚህ ላይ ሕፃኑን በተመለከተና ሰብአ ሰገልን በተመለከተ ልንጠይቃቸው የሚገቡ ነገሮች አሉ፡፡ ለምን ሰብአ ሰገልም፣ ሕፃኑም /ጌታም/ በዚያው አልቆዩም? ለምን እነርሱ እንደ ተሳዳጅ /fugitive/ በድብቅ ወደ ፋርስ፣ እርሱም ከእናቱ ጋር ወደ ግብፅ ሄዱ?

ከዚህ ሌላ ምን መደረግ ነበረበት? ጌታ በሄሮድስ እጅ መውደቅና ከዚያ አለመገደል ነበረበት? እንዲህ ቢያደርግም ኖሮ ሥጋን መዋሃዱ ግልጽ አይሆንም ነበር፡፡ የክርስቶስ የማዳን ሥራም አይታመንም ነበር፡፡

ሥጋን መዋሃዱን የሚያሳዩ ይህን የመሳሰሉ በርካታ ነገሮች ተደርገው፣ ሥጋን ለበሰ /ተዋሃደ/ መባሉ ተረት /ውሸት/ ነው የሚሉ ካሉ ሁሉን ነገር እንደ አምላክነቱ ብቻ ቢያደርገውማ ከእነዚህ የሚበልጡ ብዙዎች በተሳሳቱ ነበር፡፡

ሰብአ ሰገልንም በፍጥነት የላካቸው አንደኛ ለፋርስ ሰዎች መምሀራን እንዲሆኑ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ጌታን ለማስገደል ላሰበው ሄሮድስ እየሞከረ ያለው የማይቻል ነገርን መሆኑን አስረድቶ የሄሮድስን እብደት ለማቆምና ንዴቱን አስታግሶ ከከንቱ ድካሙ እንዲያርፍ ለማድረግ ነበር፡፡

ምክንያቱም አምላካችን ጠላቶቹን በግልጽ እና በኃይል ማስገዛት ብቻ ሳይሆን በቀላል እና ትንሽ በሚመስሉ ነገሮች ማሳመንም፣ ያውቅበታል፡፡

ለምሳሌ ግብጻውያንን በግልጽ /በኃይል/ ንብረታቸውን ለእስራኤል እንዲያስረክቡ ማድረግ ሲችል እርሱ ግን በጥበብ ያለ ጦርነት ይህንን እንዲያደርጉ አድርጎአቸል፡፡ ይህም አድራጎቱ ከሌሎቹ ተአምራት ባልተናነሰ ሁኔታ በጠላቶቹ ዘንድ የሚፈራ አድርጎታል፡፡

ለምሳሌ ፍልስጤማውያን ታቦተ ጽዮንን ማርከው በመውሰዳቸው በተቀጠቀጡ ጊዜ የሀገራቸውን ጠቢባን ከእግዚአብሔር ጋር ለመዋጋት እንዳይሞክሩ በነገሯቸው ጊዜ ከሌሎች ተአምራት ጋር ይህንን እግዚአብሔር በሥውር የሠራውንም ሥራ አንስተውታል፡፡ በግልጽ ከተደረጉት የተለየ አድርገው አላዩትም፡፡ 1ኛ ሳሙ. 6-6

በዚህ ጊዜም የተደረገው ከዚህ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ደም የጠማውን ነፍሰ ገዳይ ሊያስደንቅ የሚችል ነገር ነበር፡፡ ሄሮድስ ሊያስብ የሚገባው እንዲህ ነበር፡፡ ሰብአ ሰገል እንደካዱት፣ እንደተናቀና መሳቂያ መሳለቂያ እንደሆነ ባወቀ ጊዜ መደንገጥ ትንፋሹ መቆም ነበረበት፡፡ እነዚህ ሁሉ ነገሮች ካላሻሉት /ካላስተካከሉት/ ግን እርሱን ከጥፋቱ ለመመለስ እነዚህን ሁሉ ነገሮች ያደረገ እግዚአብሔር በእርሱ ጥፋት ሊጠየቅ አይችልም፡፡ ሄሮድስ ከዚህ በኋላ የሆኑትን ነገሮች ሁሉ ያደረገው የእብደቱ ብዛት እነዚህ ሁሉ እውነተኛ ግልጽ ነገሮች እንዲያሳምኑት ስላላደረገ ነው፡፡ ስለዚህ ከጥፋቱ መመለስ አልቻለም፡፡ በክፋቱ ስለ ቀጠለበትም ስለ ሞኝነቱ የከፋ ቅጣት ተቀብሏል፡፡

ሕፃኑ ለምን ወደ ግብጽ ሄደ? የመጀመሪያውን ምክንያት ወንጌላዊው ራሱ በግልጽ ይነግረናል፤ «ልጄን ከግብጽ ጠራሁት የተባለው እንዲፈጸም ወደ ግብጽ ሄደ» /ማቴ. 1-15/

ከዚህም በተጨማሪ በዚህ ድርጊት ለዓለም መልካም ተስፋ ተሰብኳል፡፡ በዚያን ጊዜ በዓለም ካለው ቦታ ሁሉ በከፋ ሁኔታ ባቢሎን /ፋርስ/ እና ግብጽ በእምነተ ቢስነት /በአምላክ አልባነት/ ነበልባል ተቃጥለው ነበር፡፡ እርሱም ከመጀመሪያው ሁለቱንም እንደሚያስተካክል ምልክት ሰጥቶ ሰዎችን ማዳኑ /ስጦታዎቹ/ ለዓለሙ በሙሉ እንደሆኑ አውቀው በተስፋ እንዲጠብቁ አደረጋቸው፡፡ ለዚህም ወደ አንዱ /ባቢሎን፣ ፋርስ/ ሰብአ ሰገልን ላከ፣ ሌላውን /ግብጽን/ ራሱ ከእናቱ ጋር ጎበኘ፡፡

ከዚህም ሌላ በዚህ የምንማረው ሌላ ትምህርት አለ፤ ከፍ ያለ ጽናት ሊኖረን እንደሚገባ፡፡ ይህ ምን ዓይነት ነው? ክፉ ሃሳብ /ተንኮል/ እና ክፉ ድርጊት ገና በመጠቅለያ ካለበት ጊዜ ጀምሮ በእርሱ ላይ እንደሆነ ተመልከቱ፡፡ በልደቱ ጊዜ መጀመሪያ ክፉ ነፍሰ ገዳይ፣ ተነሳበት ከዚያም ስደት እና ሀገርን ትቶ መሄድ ተከተለ፡፡ ያለ ምንም ጥፋትና በደል ከቤቷ እንኳን ርቃ ተጉዛ የማታውቀው እናቱ ወደ አረመኔዎች /barbarians/ ሃገር ተሰደደች፡፡ አስጨናቂና አስቸጋሪ የሆነ ረጅም ጉዞ እንድታደርግ ታዘዘች፡፡ ይህንን የሰማ ሰው መንፈሳዊ አገልግሎት ሲፈጽም አስጨናቂ ችግሮችና ህመሞች ቢደርሱበትና ህመሞች ቢያጋጥሙት መሸበር የለበትም፡፡

«የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ ስለፈጸምኩ መሸለም መከበርና ታዋቂ መሆን ሲገባኝ ለምን ይህ ሆነ?» ማለትም የለበትም፤ ነገር ግን ሁላችንም ይህንን እንደ ምሳሌ ወስደን ሁሉን ነገር በደስታ መቀበል አለብን፡፡ መንፈሳዊ ነገሮች ባሉበት ሁሉ ተቃዋሚ እንደማይጠፋ እና የመንፈሳዊ ነገሮች ሂደትም ይህ መሆኑንም መረዳት አለብን፡፡

ቢያንስ ይህ ነገር የሆነው በሕፃኑና በእናቱ ብቻ ላይ ሳይሆን በሰብአ ሰገልም ላይ መሆኑን እናስተውል፡፡ እነርሱም እንደ ተሳዳጅ /fugitive/ ሆነው በምስጢር እንዲሸሹ ሆነዋል፡፡

ሌላም አስደናቂ ነገር ተመልከቱ፡፡ የእግዚአብሔር ሐገር፣ የተስፋ ምድር የተባለችው ፍልስጤም በጌታ ላይ የተንኮል መረብ /ሤራ/ ስትዘረጋ የኀጢአትና የጣኦት አምልኮ ሀገር የሆነችው ግብጽ ደግሞ ተቀብላ አዳነችው፡፡

ጌታችን በእግረ ሥጋ በተመላለሰባቸው ዘመናት ያደረጋቸው አብዛኞቹ ነገሮች ወደፊት ሊመጡ ላላቸው ነገሮች ትንቢት ናቸው፡፡

ዮሴፍ ጌታንና እናቱን ይዞ ወደ ግብጽ እንዲሄድ በመልአክ ታዘዘ፡፡ ግብጽ በሥፋት ጣኦት የሚመለክባት ሀገር ነበረች፡፡ ይህም በኋላ ክርስትና በአምልኮት ባዕድ ወደ ነበሩ ህዝቦች /አሕዛብ/ ዘንድ ለመውሰዷ ትንቢት /ምልክት/ነው፡፡ እመቤታችን ጌታን ይዛ ወደማታውቀው ሀገር ስትሰደድ ቤተልሄም /ይሁዳ/ ሄሮድስ ባስገደላቸው ሕፃናት በሰማዕታት ደም ተጥለቅልቃለች፤ የሄሮድስ ጭፍጨፋና ሕፃናቱን መግደሉ ወደፊት ክርስቲያኖች በአይሁድ እጅ ለሚቀበሉት ሰማዕትነት ምሳሌ ነው፡፡

መልአኩ ተገልጦ የተነጋገረው ከእመቤታችን ጋር ሳይሆን ከዮሴፍ ጋር ነበር፡፡ ምን አለው? «ተነሳ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ..» የእመቤታችን በግብረ መንፈስ ቅዱስ መጽነስ ሲነግረው ያለው «እጮኛህን ማርያምን ለመውሰድ አትፍራ» ነበር፡፡ አሁን ግን እጮኛህን አላለውም «የሕፃኑን እናት» አለው እንጂ፡፡ ምክንያቱም እመቤታችን ጌታችንን ከወለደች እና በጌታ ልደት ጊዜ የሆኑትን ነገሮች /ኮከቡን፣ ሰብአ ሰገልን/ ካየ በኋላ ሁሉን ነገር ተረድቶ ተረጋግጦ ነበር፡፡ በቂ ነገር ዓይቶ፣ ባየው ነገር ተረጋግቶ ነበር፡፡ ስለዚህ መልአኩ አሁን በግልጽ ይናገራል «ልጅህን» ወይም «እጮኛህን» አላለም፡፡ «ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ግብጽ ሂድ አለው» እንጂ፡፡ የስደቱንም ምክንያት አብሮ ይነግረዋል፤ «ሄርድስ የሕፃኑን ነፍስ ይፈልጋልና፡፡»

ዮሴፍ ይህንን ሲሰማ ቅር አልተሰኘም፤ «ይህን ነገር ለመረዳት ይከብዳል፤ ሕዝቦቹን ያድናቸዋል አላለከኝም ነበር? አሁን ደግሞ ራሱን እንኳን ማዳን አይችልምን? እኛም ከቤታችን ወጥተን ርቀን ለብዙ ጊዜ መሰደድ አለብን አሁን ያለት ነገሮች ከተሰጠው ተስፋ /ቃል/ ጋር ተቃራኒ ናቸው፡፡» አላለም ጻድቅ እና እውነተኛ አማኝ ነበርና፡፡

ምንም እንኳን መልአኩ መመለሻውን ግልጽ ሳያደርግ እስከምነግርህ ድረስ በዚያው ተቀመጥ ቢለውም ስለሚመለሱበት ጊዜ አልተጨነቀም፤ አልጠየቀምም፡፡ ዮሴፍ ፍርሃትም እንኳን አላሳየም፡፡ ሁሉንም ነገር በደሰታ ተቀበለ እንጂ፡፡

ሰውን ወዳጅ የሆነው እግዚአብሔር መከራንና ደስታን በሰዎች ሕይወት ላይ ያመጣል፡፡ በችግር ወይም በደስታ ብቻ አያኖርም፡፡ ነገር ግን ሁለቱንም ችግርን /ሀዘንን/ እና ደስታን /ሃሴትን/ እያፈራረቀ ያመጣል፡፡ አሁንም ያደረገው ይህንኑ ነገር ነው፡፡ ዮሴፍ ድንግልን ጸንሳ ባያት ጊዜ ተጨነቀ፤ ተረበሸ፤ ታወከ፡፡ በዚህ መሃል ግን መልአኩ ተገልጦ ፍርሃቱን አስወገደለት፡፡ ሕፃኑን ተወልዶ ባየ ጊዜም ከፍ ያለ ደስታ ተደሰተ፡፡ ደስታው ብዙም ሳይቆይ አደጋ መጣ፤ በሰብአ ሰገል መምጣት ከተማው ተረበሸ ንጉሡም ከእብደቱና ከክፋቱ የተነሳ የተወለደውን ሕፃን ሊገድል ተነሳ፡፡ ይህ ጭንቀት ደግሞ በደስታ ተተካ ኮከቡና የሰብአ ሰገል ለጌታ መስገድ እጅግ አስደሳች ነበሩ፡፡ ከዚህ ደስታ በኋላም ጭንቀትና ፍርሃት መጣ፡፡ መልአኩ «ንጉሥ ሄሮድስ የሕፃኑን ነፍስ ይፈልጋል፡፡» ብሎ ነገረው፡፡

በዚህ ጊዜ ጌታችን በሕዝብ ፊት ተዓምራት ለማድረግ ጊዜው ገና ነውና መሰደድ አስፈለገው፡፡ ምክንያቱም ገና በልጅነቱ ተአምራትን በአደባባይ /በሕዝብ ፊት/ ቢያደረግ፣ ሥጋን እንደተወሃደ አይታመንም ነበር፡፡

በአንድ ጊዜ ሁሉን ማድረግ ሲችል ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅጸን ያደረው፣ እንደ ሕፃናት ጡትን እየጠባ፣ በጥቂት በጥቂቱ ያደገው፣ ሥራውን እስኪጀምርም ሠላውን ዘመን በዝምታ /በስውር ተዓምራት/ ያሳለፈው፡- የተዋህዶን ነገር እንረዳ ዘንድ ነው፡፡

አይሁድ ትንቢቱን በተመለከተ ጥያቄ ቢያነሱ እና ልጄን ከግብጽ ጠራሁት የተባለው ስለ እኛ ነው ቢሉን ይህ የትንቢት አካሄድ /መንገድ/ ነው እንላቸዋለን፡፡ ብዙ ጊዜ ስለተወሰኑ ሰዎች የተናገረው የሚፈጸመው በሌሎች ነው፡፡ ያዕቆብ ሊሞት ሲል ልጆችን ሰብስቦ በኋለኛው ዘመን ምን እንደሚደርስባቸው ሲነገራቸው እንዲህ ብሎ ነበር፡-

ስምኦንና ሌዊ ወንድማማች ናቸው፤

ሰይፎቻቸው የአመጽ መሣሪያ ናቸው፡፡

ከምክራቸው ነፍሴ አትግባ፡፡

ከጉባኤያቸውም ጋር ክብሬ አትተባበር

በቁጣቸው ሰውን ገድለዋልና

በገዛ ፈቃዳቸው በሬን አስነክሰዋልና፡፡

በያዕቆብ እከፍላቸዋለሁ፡፡ በእስራኤልም እበትናቸዋለሁ፡፡ ዘፍ. 49-7

ይህ ግን በእነርሱ አልተደረገም በልጆቻቸው እንጂ፡፡ በዘፍ. 9-25 ላይ ተጽፎ እንደሚገኘውም ኖህ እንዲህ ብሎ ነበር፡- «ከነአን ርጉም ይሁን ለወንድሞቹም የባሪያዎች ባሪያ ይሁን» ይህ የተፈጸመው በከንአን ሳይሆን በእርሱ ዘሮች ነው፡፡

ይህ መቼ እና እንዴት እንደሆነ በመጽሐፈ ኢያሱ እና በመጽሐፈ ዜና መዋዕል፤ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ እንዲህም ሆነ በዮርዳኖስ ማዶ በተራራማው በቆላውም በታላቁ ባሕር ዳርና ሊባኖስ ፊት ለፊት የነበሩ ነገሥታት ሁሉ ኬጢያዊ፣ አሞራዊም፣ ከነአናዊም፣ ኢያቡሳዊም፣ ይህን በሰሙ ጊዜ ኢያሱንና እስራኤልን ሊወጉ ወጡ፡፡

በዚያም ቀን ኢያሱ ለማኅበሩ በመረጠው ሥፍራ እስከ ዛሬ ድረስ፣ ለእግዚአብሔር መሠዊያ እንጨት ቆራጮች ውኃም ቀጂዎች አደረጋቸው፡፡ /ኢያ. 9-1-27/

1ኛ ዜና.8-7 ሰሎሞንም ኬጤያውያንንም፣ አምራውያንንም፣ ፌርዜያውያንንም ኢያቡሳውያንንም የቀሩትን ከእስራኤል ወገን ያልሆኑትን ሕዝብ ሁሉ... ገባሮች አድርጎ መለመላቸው፡፡

ይስሐቅ «ለወንድሞችህ ጌታ ሁን፡፡ የእናትህም ልጆች ይስገዱልህ»፡፡ ብሎ ያዕቆብን የመረቀው ምርቃት የተፈፀመው በእርሱ ሳይሆን በልጆቹ ነው፡፡ ዘፍ. 27-19

ስለዚህ እርሱ ባይወለድ ኖሮ፣ ትንቢቱ ፍጻሜውን አያገኝም ነበር፡፡ ወንጌላዊውም ያለውን አስተውሉ፡- «ይፈፀም ዘንድ፡፡» ይህም እርሱ ባይመጣ አይፈፀምም ነበር ማለት ነው፡፡

በዚህኛውም ጊዜ የተደረገው /የሆነው/ ከዚህ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ነገር ነው፡፡ መጀመሪያ ለእስራኤል የተነገረው ነገር በኋላ በጌታ ተፈጽሟል፡፡ ደግሞስ የእግዚአብሔር እውነተኛ ልጅ ሊባል የሚችለው የትኛው ነው? ጥጃን ያመለከና ለቤልሆር ልጆቹን የሰዋ? ወይስ በባሕሪው ልጅ የሆነና የወለደው አባቱ «የምወደው ልጄ» ብሎ የሚያመሰግነው?

ከዚህም ሌላ /ግብጽ መሄዳቸው/ እመቤታችን ከፍ ያለ ክብር ያላት እንደሆነች እንዲታወቅ ተደርጓል፡፡ ህዝቡ የሚመኩበትን ከእግዚአብሔር ያገኙትን ስጦታ እርሷም ለራሷ አግኝታለችና፡፡ ማለትም፣ እነርሱ ከግብጽ በመውጣታቸው /ከስደት በመመለሳቸው/ ይመኩና ይኮሩ ነበር፡፡ ይህንኑ የሚመኩበትን ነገር ለእመቤታችንም ስጣት፡፡

ያዕቆብና ህዝበ እስራኤል ወደ ግብጽ በመሄዳቸውና ከዚያም በመመለሳቸው የእርሱን ግብጽ ሄዶ መመለስ ምሳሌ እየፈጸሙ ነበር፡፡ እነርሱ ግብጽ የሄዱት በረሃብ /በድርቅ/ የመጣ መሞትን ለማምለጥ ነበር፡፡ እርሱ ደግሞ በተንኮል መሞትን ለማምለጥ ነው፡፡

እነሱ /ህዝበ እስራኤል/ ግብጽ መሄዳቸው ከረሃቡ /ከድርቁ/ ተርፈዋል፡፡ እርሱ ግን እዚያ በመሄዱ በኪዳተ እግሩ /በእግሩ በመርገጥ/ ምድሪቱን ቀድሷታል፡፡

በዚህ ራሱን ዝቅ በማድረጉ መሀልም ግን የአምላክነቱ ማሳያዎች /ምልክቶች/ ተገልጸዋል፡፡ ሰብአ ሰገልና እርሱን ለማምለክ በኮከብ እየተመሩ መጡ፤ አውግስጦስ ቄሳርም የሕዝብ ቆጠራ አዋጅ በማወጅ ልደቱ ቤተልሔም እንዲሆን አገለገለ፤ በግብጽም በርካታ ተዓምራት ተደርገዋል፡፡

አሁን ወደ ግብጽ ብንሄድ በረሃው ከማንኛውም የአትክልት ስፍራ የተሻለ ሥፍራ ያማረ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በመላእክት አምሳል ያመሰግኑበታል የሰማእታት ብሔር፣ የደናግል በአት፣ የሰይጣን አገዛዝ ድል የተመታበትና የክርስቶስ መንግስት ደምቆ የሚያበራበት ቦታ ነው፡፡

በትምህርተ ሃይማኖታቸው /doctrine/ ካላቸው ትክክለኛነት በተጨማሪ፣ በህይወታቸውም ያላቸውን ቁርጠኝነት ያሳያሉ፡፡ ያላቸውን ሁሉ ትተው ራሳቸውን ከዓለም ካገለሉና ለዓለሙ በሙሉ ከተሰቀሉ በኋላ በድጋሚ የተቸገሩትን ይረዱ ዘንድ የጉልበት ሥራ ይሠራሉ፡፡

ስለሚጾሙና ብዙ ጊዜ በተመስጦ ስለሚያሳልፉ፤ ቀናቱን /ጊዜን/ ሥራ በመፍታት /ቦዝነው/ ማሳለፍ ተገቢ ነው ብለው አያስቡም፡፡ ስለዚህም ቀኑን በጸሎት ሌሊቱንም በዝማሬና በትጋት ያሳልፉታል፡፡ ከዚህም የሐዋርያውን አሰር ይከተላሉ፡፡

«ከማንም ብር ወይም ወርቅ አላስፈለገኝም እነዚህ እጆቼ በሚያስፈልገኝ ነገር ለእኔና ከእኔ ጋር ላሉት እንዳገለገሉ እናንተ ታውቃላችሁ፡፡ እንዲህ እየደከማችሁ ድውያንን ልትረዱና፣ «እርሱ ራሱ ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብጽዕ ነው» የሚለው የጌታን የኢየሱስን ቃል ልታስቡ ይገባችሁ ዘንድ አሳየኋችሁ፤» ሐዋ. 10-34 ይህንን የሐዋርያውን ቃል ሲሰሙ በበረሃ ያሉት የግብጽ መነኮሳት እንዲህ ይላሉ፡- «እርሱ /ሐዋርያው/ በእግዚአብሔር ቃል እንዲመግባቸው ብዙዎች እየጠበቁት የእጅ ሥራ ይሠራ ከነበረ፣ መኖሪያችንን በገዳም፣ በዱር፣ በበረሃ ያደረግን፣ የከተማ ጾር /ፈተና/ የቀረልን እኛማ ከጸሎታችንና ከተመስጦአችን የተረፈንን ጊዜ ለተመሳሳይ ሥራ ልናውለው ምን ያህል ይገባናል)!»

እኛም ራሳችንን እንመርምር ሀብታምም ድሃም የሆንን እነዚህ መነኮሳት ከሰውነት /እጅና፣ እግር/ በስተቀር ምንም የሌላቸው ሲሆኑ የተቸገሩትን ለመርዳት እንዲህ ከወጡና ከወረዱ የተረፈንን እንኳን ለእነዚህ ሰዎች /ችግረኞች፣ ድውያን/ የማንሰጥ እኛ ለዚህ አድራጎታችን ምን ምክንያት፣ ምን ማስተባበያ ማቅረብ እንችላለን፡፡

ታላቁን አባት ቅዱስ እንጦንስን እናስታውስ፡፡ ይህ ሰው የተወለደው ፈርኦን በተወለደበት ሀገር ነው፡፡ ነገር ግን በዚህ ምክንያት እነርሱን አልመሰለም፡፡ የነበረው ሰማያዊ ራእይ ስለጠበቀው እግዚአብሔር በሚወደው መልኩ ህይወቱን አሳልፏል፡፡ ከጽድቁ የተነሳ ከእርሱ በኋላ የሚመጡ መነኮሳት ምን ዓይነት እንደሚሆኑ እግዚአብሔር አሳይቶታል፡፡

ጻድቁ እንጦንስን ታሪክ ማንበብና ማድነቅ ብቻ ሳይሆን በሕይወት መተርጎምም ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን አለመበርታት ቦታን፣ አለመማርን፣ የአባቶችን መርገም... ምክንያት አናድርግ፡፡
ነገሮችን በማስተዋል ስንመለከት እነዚህ ሁሉ ነገሮች ለእኛ መሰናክል መሆን አይችሉም፡፡ አብርሃም ጣኦት አምላኪ አባት ነበረው /ኢያ. 24-2/ ነገር ግን የአባቱን ክፋት አልወረሰም፣ የሕዝቅኤልም አባት አካዝ ኀጢአተኛ ሰው ነበር፡፡ ሕዝቅያስ ግን የእግዚአብሔር ወዳጅ ነበር፡፡

ዮሴፍም በግብጽ ሆኖ ራሱን በትምህርት አስጊጧል፡፡ ሦስቱ ሕፃናትም በባቢሎን ቤተመንግስት ሆነው ታላቅ ራስን መግዛት አሳይተውናል፡፡ ሙሴም በግብጽ ነበር፣ ቅዱስ ጳውሎስም በዓለም ነበር፤ ነገር ግን እነዚህን ሁሉ ያሉበት ቦታና ሁኔታ ከጽድቅ ጉዞአቸው አላደናቀፋቸውም፡፡


ዘመነ ጽጌ በዲ/ን ዳንኤል ክብረት

                                                        

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን!

ምንጭ፦ ማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ