Monday, March 24, 2014

ለምን ከምንወዳት አገራችን እንሰደዳለን? ክፍል 1

ከምንወዳት፣ ከአደግንባት፣ የማይረሳ የልጅነት ጊዜያችንን ካሳለፍንባትና አገራችንን ጥለን/ለቀን በባዕድ አገር በስደት በእምነት፣ በባህል፣ በቋንቋ እንዲሁም በአመለካከት ከማይመስሉን ጋር በተለያየ  ፈተናና ውጣ ውረድ እና ለአፍታ በማይዘነጋ አገራዊ ትዝታ እንድንኖር ያደረገን ትልቅ ምክንያት ይኖረናል፤አለንም። ማንም ሰው በአገሩ በሰላም እና በደስታ ባሳደገው ማህበረሰባዊ ባህል መኖር እና ማደግ ይፈልጋል። የራሱ የሆነ በቂ ምክንያት ከሌለው በስተቀር ስደትን ቤቴ ብሎ የሚኖር የለም። ባገሩ በሰላም መኖር የሚችል ሰው የስደትን አስከፊነት እና ትግዕስት አስጨራሽነት ተቋቁሞ መኖር ባልቻለ ነበር። ግን እርሱ ባለቤቱ የሚያውቀው አሳማኝ ምክንያት አለው። 

በእርግጥ ዛሬ ላይ ዓለም ሁሉ ለስደት የዳረገንን ምክንያት ዘመኑ በወለዳቸው ብዙኃን መገናኛዎች ምስክርነት መስጠት ከጀመሩ ጊዜያትን አሳልፈዋል። እውነታውንም በሚገባ ተገንዝበው ለሰሚዓን ምስክርነቱን ቀጥለውበታል። ከፊሎች ደግሞ ኢትዮጵያዊነት ስሜት የለለውን የመንግስትን ከእውነታ የራቀ ተራ ወሬ ተከትለው ስደተኞችን ሲተቹ እና ሲያንገላቱ ይታያል። እርግጥ ነው ብዙዎች የአፍሪካ መሪዎች የስልጣን ዘመናቸውን የሚያስረዝሙት በሀሰት እና በኃይል ረግጠው እናስተዳድረዋለን እንመራዋለን በሚሎት ህዝብ ላይ የመከራ ቀንበር በመጫን እና በማስጨነቅ ነው። የኢትዮጵያ መሪዎችም የስልጣን ዘመናቸውን ለማስረዘም ያዋጣናል የሚሉትን ማንኛውም መንገድ ይጠቀማሉ። ሲፈልጉ ያጸድቃሉ፤ ሲፈልጉ ይኮንናሉ፤ይሾማሉ፣ይሽራሉ፤ ይገድላሉ፣ ያኖራሉም።

በአገራችን አንድ ገሀዳዊ እውነታ አለ። ህዝቡ አገሩ ከመኖር ይልቅ ወደ ስደት ዓለም የሚሄድባቸውን መንገዶች በማፈለለግ ከጊዜ ወደ ጊዜ የስደተኛው ቁጥር በእጅጉ እየበዛ እና እየጨመረ መምጣቱ ዓለም በአንድ ድምጽ የሚመሰክረው እውነታ ነው። አገርን ያሳድጋል ያለማል ተብሎ ተስፋ የተጣለበት የተማረው ዜጋም ስደትን በመቀላቀል ግንባር ቀደም ቦታን ይዟል። ለአንድ አገር እድገት አይደለም የተማረ ዜጋ ቀርቶ ማንኛም ሰው በተፈጥሮአዊ እውቀቱ፣ ጉልበቱ እና ገንዘቡ አገርን የመለወጥ አቅም አለው። የአደጉ አገሮችን ታሪክ ብንመለከት ወደ ብልጽግናው ዓለም የተቀላቀሉ ያላቸውን የሰው ኃይል በሙሉ በነጻነት ለአገሩ ተቆርቋሪ ሁኖ በቻለው መጠን እንዲሰራ በማድረጋቸው ነው። 
ወደ ኢትዮጵያ አገራችን ስንገባ ግን በተቃራኒው ሁኖ እናገኘዋለን። በጣም የሚያሳዝነው የሚሰራ ሰው፣ የሚናገር ሰው፣ ለእውነት የቆመ ሰው እንዲኖርባት ያልታደለች አገር መሆኗ ነው። የዓለም መነጋገርያ የሆነውን የትናቱን የረዳት አብራሪ ኃይለመድህን አበራ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ ቁጥር ‪ET702‬ ይዞ ኢጣሊያ መግባት የነበረበትን ወደ ሲዊዝ ጀነባ መሄዱን መመልከት ከበቂ በላይ የነጻነት እጦትን ያረጋግጣልናል።


በብዙ ምክንያቶች ዜጎቿ ስደተኞች ሁነውል። በሚገርም ሁኔታ በአገር ውስጥ የሚኖሩ ዜጎቿም አብዛኞቹ ወደ ስደት የሚወጡበትን አጋጣሚዎች በመጣባበቅ የመንፈስ ስደተኞች ሁነዋል። በተለያየ አጋጣሚ ወደ ውጭ የሚወጣው ዜጋ ወደ አገሩ የሚመለሰው ቁጥር በእጅጉ አናሳ መሆኑን ጥናታዊ ባልሆነ መንገድ የምንሰማቸው እና የምናያቸው መረጃዎች ህያው ምስክሮች ናቸው። ግን ለምን? እንዴት? እስከ መቼ? ህዝቦቿ በስደት የሚሰቃዩት መልስ የለለው የዘወትር ጥያቄየ ነው። ለስደት የዳረገንን አንዱን እና ትልቁን ምክንያት ለማንሳት እሞክራለሁ። 
  
ነጻነት፣ ነጻነት፣ ነጻነት???

ነጻነት የሚለውን ቀጥተኛ ትርጉም በአጭሩ ከዚህ በፊት "ነጻነት ወይስ ቅኝ ግዛት" በሚል ባወጣውት ጽሁፌ ላይ ለመግለጽ ሞክሬ ነበር። (ነጻነት ወይስ ቅኝ ግዛት/ባርነት) በዚህ ጽሁፌ ደግሞ የነጻነት እጦት ምን ያክል ለስደት እንደዳረገን ውስጣዊ ስሜቴን ለመግለጽ እዎዳለሁ።
ነጻነት ተፈጥሮአዊ ነው። እግዚአብሔር ለሰው ልጆች የሰጠው ትልቁ ጸጋ ነጻነት ነው። እሱን እንድናመልከው እንኳ ነጻ ፈቃድ ሰጥቶናል፤ አላስገደደንም። እግዚአብሔር የፈጠረውን ፍጥረት ሳያስገድድ የኢትዮጵያ መሪዎች ግን እነሱ ባልፈጠሩት፣ ባልሰሩት፣ ምንም ዋጋ በአልከፈሉበት ህዝብ ላይ አምባ ገነናዊ አገዛዛቸውን አስፍተው እኛን ሲጨቁኑን እና መከራ ሲያበዙብን እናያለን። እነርሱ እና የእነርሱ አጫፋሪዎች በነጻነት ይኖራሉ። ብዙኃኑ ህዝብ ግን በነጻነት እጦት ብዙዎች ተሰደዱ፣ ተንገላቱ፣ መከራን ተቀበሉ። ብዙዎችም ነጻነት ይኑር ብለው በመናገራቸው ተገደሉ፣ ታሰሩ፣ ሃብት ንብረታቸው ተወረሰ፣ የሚናገሩበት አንደበት እንዲዘጋ ተደረጉ፣ ለነጻነት የሚጽፉበት ብዕራቸው ተወረወረ እጃቸውም ታሰረ። ቤተ እምነቶችም ሳይቀሩ ነጻነትን በመስበካቸው የአምልኮ ስርዓታቸውን እንዳያካህዱ ተደረጉ። የአምልኮ ቦታዎች በምክንያት እንዲፈርስ ተደረገ። ባህላችንን፣ ታሪካችንን እና ማንነታችንን እንድናጣ ተደረግን። 

የኢትዮጵያ ህዝብ በሁሉም መስክ ነጻነቱ ተገፏል፤ በነጻነት መናገር፣ በነጻነት መጻፍ፣ በነጻነት መደራጀት፣ በነጻነት መሰብሰብ፣ በነጻነት ማህበራዊ ተግባራትን ማካሄድ፣ በነጻነት መስራት እና በነጻነት መንቀሳቀስ እንዲሁም በነጻነት ማምለክ ታሪክ ሆኖብናል። ህዝቡ በእጅጉ ነጻነትን ይፈልጋል። ነጻነት ፍለጋም ስደትን እንደ አንድ ዓቢይ ምርጫ አድርጎ በየቀኑ በብዙዎች የሚቆጠሩ ይፈልሳሉ። የስደትን አስገፊ ህይወት በጸጋ ተቀብሎ መኖር አማራጭ የለለው መፍትሔ አድርገነዋል። የዱር እንስሳት እንኳ ሳይቀሩ የእለት ከእለት ኗሯቸውን በነጻነት ማካሄድ የማይችሉበት ሁኔታ ሲፈጠር ነጻነት ወደሚያገኙበት ቦታ/ጫካ ይሰደዳሉ። የሰው ልጅ ደግሞ ከእንስሳት በተለየ የአስተሳሰብ አድማሱ ሰፊ በመሆኑ ነጻነትን ከምንም በላይ ይፈልጋል። "ጎመን በጤና ይላል" እንዲሉ ነጻነትን ተነፍጎ የቁም እስረኛ ከመሆን ይልቅ በነጻነት በድህነት መኖር አእምሯዊ ረፍት ይሰጣል። 

ስለዚህ የስደታችን ዋነኛ ምክንያት የነጻነት እጦት ነው። የህዝብ ነጻነት እስካልተመለሰ ድረስ ከስደት ወደኋላ ይላል ብሎ ማሰብና መፍረድ የቁም እስረኛ ሁኑ ብሎ እንደመፍረድ ይቆጠራል። ህዝብ ነጻነቱን ካገኘ ሁሉን ነገር ማድረግ ይችላል፤ ሰርቶ ድህነትን ማሸነፍ ይችላል፤ ማህበራዊ ህይወቱ ሰላማዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እድገቱ እውነታ ያለው እድገት እና ፖለቲካዊ አመለካከቱ የሰላ እና ዲሞክራሲያዊ ይሆናል።

 የኢትዮጵያ መንግስት ሆይ ነጻነታችንን መልሱልን!
አገራዊ ስሜታችንን ጠብቁል እናተም አገራዊ ስሜት ይኑራችሁ!
ተውን በነጻነት እንጻፍ፣ እንናገር፣ እንቀሳቀስ፣ እንስራ!
አምልኮታችንንም ለአምላካችን በነጻነት እናቅርብ!