Wednesday, April 16, 2014

የሰሙነ ሕማማት ትርጓሜ፣ ክንዋኔና ሚስጢር

ጌታችን መድሀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ኢየሩሳሌም ከገባ ጀምሮ ያሳለፈውና ከትንሳኤው በፊት ያለው አንድ ሳምንት " የመጨረሻ ሳምንት " ተብሎ ይጠራል፡፡ በሌላ አጠራር ደግሞ " ሰሙነ ሕማማት " ይባላል፡፡ በጌታ ላይ የሞት ምክር የተመከረበትና በብዙ መከራና ሕማማት የተገደለበት ስለሆነ ነው፡፡ ስለዚህም ሰሙነ ሕማማት የሚለው ስያሜ ጌታ የተቀበለውን ፀዋትዎ መከራን ለማዘከር የሰጠ ስያሜ ነው፡፡ የጌታ የመስቀሉ ሕማሞች ወይም " ሕማማት መስቀል " ተብለው የሚዘከሩት አሥራ ሦስት ሲሆኑ እነዚህም፦

1. በብረት ሐብለ መጋፊያና መጋፊያው እስኪጋጠም ድረስ የኋሊት መታሰሩ
2. ከአፍንጫው ደም እስኪውጣ ድረስ 25 ጊዜ በጡጫ መመታቱ
3. 65 ጊዜ ከግንድ ማጋጨታቸው
4. 120 ጊዜ በድንጋይ ፊቱን መመታቱ
5. 365 ጊዜ በሽመል መደብደቡ
6. 80 ጊዜ ጽህሙን መነጨቱ
7. 6666 ጊዜ መገረፉ
8. አክሊለ ሦክ በራሱ ላይ መደፋቱ
9. 136 ጊዜ በምድር ላይ መውደቁ
10. ሳዶር፡ አላዶር፡ ኤዴራ፡ ዳናትና ሮዳስ በሚባሉ 5ቱ ቅንዋተ መስቀል በችንካር መቸንከሩ
11. መራራ ሐሞትን መጠጣቱ
12. መስቀሉን ተሸክሞ መንገላታቱ
13. በመስቀል መሰቀሉ ናቸው።
በዚህ ሳምንት ውስጥ ካህናትና ምዕመናን በአፀደ ቤተ ክርስትያን ተሰብስበው ከሀጥያት ርቀው ከምግብና ከመጠጥ ተቆጥቦ በጾምና በጸሎት የሕማሙን ነገር የሚያወሳውን ዜማ ሲያዜሙ ግብረ ሕማም የሚባለውን መጽሐፍ እያነበቡ ሲሰግዱና ሲጸልዩ ይሰነብታሉ።

ከአባታችን አዳም በደል ወይንም ስሕተት በኋላ በሕማማት፣ በደዌያት፣ በመቅሰፍታት፣ ወዘተ በብዙ መከራ የሰው ልጅ ሊኖርባቸው ግድ የሆነባቸው ዘመናት ጥቂቶች አልነበሩም፡፡ ጥሮ ግሮ ወጥቶ ወርዶ ለፍቶ ማስኖ የዕለት ጉርስ የቀን ልብስ ማግኘት እጅግ አዳጋች ነበር፡፡ ሁልጊዜ የሰው ልጅ ቢያጠፋ ቢበድል ከሕገ እግዚአብሔር ቢወጣ እንኳ የዋህ፣ ታጋሽ፣ ቸር፣ አዛኝ የሆነ አምላክ የጠፋውን ሊፈለግ የተራበውን ሊያጠግብ የታረዘውን ሊያለብስ፣ ፍቅር ያጣውን ፍጹም ፍቅር ሊለግስ፣ ሰላም ለሌለው ፍጹም ሰላም ሊሰጥ፣ ተስፋ የሌለውን ተስፋ ሊያጐናጽፍ ከሰማይ ወረደ፤ ከድንግል ማርያም ተወለደ፤ በገዳመ ቆሮንቶስ አርባ ቀንና ሌሊት ጾመ፡፡ በጾሙም የኃጡአት ሥሮች ወይም ራሶች የተባሉትን ስስትን፣ ትዕቢትንና ፍቅረ ንዋይን ድል አደረገልን፡፡ እኛ እርሱ የጾመውን ጾም እንድናከብር እንድንጾም ምሳሌ ሆነን፡፡ ዲያብሎስን ድል አድርጐ ድል እንድንነሣው ኃይልና ምሳሌ ሆነን፡፡

ሰሙነ ሕማማት ምንድን ነው?

ሰመነ ስምንት /ሳምንት/ አደረገ ማለት ነው፡፡ ይኸውም ከዕለተ ሆሣዕና ሰርክ እስከ ትንሣኤ ሌሊት ያለውን ጊዜ ወይም ቀናት የሚያመለክት ነው፡፡ ሐመ ማለት ታመመ ማለት ሲሆን ይህም የሰውን ዘር ሁሉ ከዲያብሎስ ባርነት ነፃ ለማውጣት ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፈቃዱ የተቀበላቸውን ጸዋትወ መከራዎች የሚያሳስብ ነው፡፡ ዕለታቱ የዓመተ ኩነኔ ወይም የዓመተ ፍዳ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ክርስቲያኖች የክርስቶስን ውለታ እያሰቡ እጅግ የሚያዝኑበት፣ የሚያለቅሱበት፣ የሚሰግዱበት ቤት ንብረታቸውን ትተው ከሌላው ቀናትና ጊዜያት በተለየ መልኩ ቤተ ክርስቲያናቸውን የሚማጸኑበት፤ ጧት ማታ ደጅ የሚጠኑበት፤ ኃጢአታቸውን በቤተ ክርስቲያን አደባባይ ለካህኑ የሚናዘዙበት በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የሚገኝ ሳምንት ነው፡፡

በዚህ ሳምንት ብዙ አዝማደ መባልእት አይበሉም፤ ይልቁን በመራብ በመጠማት በመውጣት በመውረድ በመስገድ በመጸለይ በመጾም በየሰዓቱ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ጸዋትወ መከራዎች በማሰብ አብዝቶ ይሰገዳል፡፡ መከራውን፣ ሕማሙን፣ ድካሙን የሚያስታውሱ ከቅዱሳት መጻሕፍት ኢሳይያስ፣ ኤርምያስ መዝሙረ ዳዊት ግብረ ሕማማት ወዘተ በየሰዓቱ ይነበባል፡፡

መስቀል መሳለም የለም፡፡ ካህናትም እግዚአብሔር ይፍታህ አይሉም የሳምንቱ ሥርዓተ ፍትሐት አይደረግም፡፡ ይኸውም ይህ ሳምንት ከሞት ወደ ሕይወት የተሸጋገርንበት ከጨለማ ወደ ብርሃን የተጓዝንበት የመሸጋገሪያ ወቅት ምሳሌ በመሆኑ ነው፡፡ በዕለተ ምጽአት መላእክት የመለከት ድምጽ በማሰማት የዳግም ምጽአትን ዕለት ለማሳሰብ ምእመናን ጥሪውን ሰምተው ለዚህም አስቀድመው ተዘጋጅተው የበዓሉ ታዳሚዎች መሆናቸውን በማጠየቅ በዚህ ሳምንት ዲያቆኑ ቃጭል እየመታ በየሰዓቱ ምእመናኑን ያሳስባል፡፡

በሰሙነ ሕማማት የሚገኙ ዕለታትና ስያሜያት

ዕለተ ሰኑይ /ሰኞ/

ይህ ዕለት አንጾሖተ ቤተ መቅደስ /የቤተ መቅደስ መንጻት/ እና መርገመ በለስ የተፈጸመበት ዕለት ነው፡፡ /ማር.11-11፣ ማቴ.21-18-22 ሉቃ.13-6-9/፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ «ወመሰለ ሎሙ ወይቤሎሙ አሐዱ ብእሲ በለሰ ቦቱ ውስተ አጸደ ወይኑ ወየሐውር ይንሣእ ፍሬሃ ወኢይረክብ ...»፤ ይህንም ምሳሌ አለ ለአንድ ሰው በወይኑ አትክልት የተተከለች በለስ ነበረችው ፍሬም ሊፈልግባት ወጥቶ ምንም አላገኘም፡፡ በማለት በበለስ ስለተመሰለ የሰው ልጅ ሕይወት በማሰብ እንዲመለስ ንስሐ እንዲገባ በሕይወትም እንዲኖር እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ማሳሰቡን ያጠይቃል፡፡ ንስሐ አልገባም አልመለስም ያለም በለሷ እንደጠወለገችና እንደተቆረጠች ሁሉ ፍሬ ባለማፍራታቸው እንደሚቆረጡ እንዲሁም ወደ እሳት እንደሚጣሉ መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ ያስረዳል፡፡ በለስ የተባለች ቤተ እስራኤል ፍሬ የተባለ ደግሞ ሃይማኖትና ምግባርን ነው፡፡ ሁላችን ቤተ እስራኤላውያን ፍሬ ሃይማኖት ወምግባር አስተባብረን ይዘን መገኘት ይገባናል፡፡ ፍሬ አልባ እንዳንሆን ጌታ ሲመጣም እንዳናፍር የመጽሐፉን ቃል ልንጠብቅና ልንፈጽም ይገባናል፡፡ በዚህ የሕማማት የመጀመሪያ ቀን ዕለተ ሰኑይ የምናስበው የምንዘክረው የሰው ልጅ ሕይወት በከንቱ በቸልተኝነት እንዳይደክም እንዳይጠወለግ እንዳይደርቅ ወደ እሳትም እንዳይጣል ማድረግ ይገባናል፡፡

ዕለተ ሠሉስ /ማክሰኞ/

ይህ ቀን ጌታችን ሰኞ በተናገረውና ባደረገው ላይ አይሁድ ጥያቄ ያቀረቡበት እርሱም መልስ በመስጠት ያስተማረበት ዕለት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የጥያቄ እና የትምህርት ቀን በመባል ይታወቃል፡፡ ጥያቄውም ጌታ ባደረገው አንጽሖተ ቤተ መቅደስ ምክንያት ለጸሐፍትና ፈሪሳውያን ይኸውም ትምህርት ማስተማር፣ ተአምራት ማድረግ፣ ገበያ መፍታትን በማን ሥልጣን ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን ማን ሰጠህ?» የሚል ነበር፡፡ /ማቴ.21-23-27/፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ «ወይቤሎሙ ኢየሱስ አማን እብለክሙ ከመ መጸብሓውያን ወዘማውያት ይቀድሙክሙ ውስተ መንግሥተ እግዚአብሔር»፤ ኢየሱስ እንዲህ አላቸው እውነት እላችኋለሁ ቀራጮችና ጋለሞቶች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በመግባት ይቀድሙአችኋል ሲል አስተምሯል፡፡ /ማቴ.21-28/

ዕለተ ረቡዕ/እሮብ/

ይህ ዕለት ደግሞ የአይሁድ ሊቃነ ካህናትና ጸሐፍት ጌታን እንዴት መያዝ እንደሚችሉ ምክር የጀመሩበት ቀን ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ዕለቱ" የምክር ቀን" በመባል ይጠራል፡፡" መልካም መዓዛ ያለው" እና "የእንባ"ቀንም ይባላል። ምክንያቱም ማርያም ዕንተ እፍረት ዋጋው ብዙ የሆነ ሽቶ ጌታችንን በመቀባታና ስለ ሀጥያቷ ስቅስቅ ብላ በማልቀሷ ይህንን ስያሜ ተሰጠ። ማቴ 26፦3_13 ማር 14፦ 1_11 ሉቃ 22፦3_6

ዕለተ ሐሙስ/ሐሙስ/

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዕለት ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆኑን ለመግለጥ እና ለአርአያነት ጸሐፍት ፈሪሳውያን የአይሁድ ካህናት መጥተው እስኪይዙት ድረስ ሲጸልይ በማደሩ ምክንያት ጸሎተ ሐሙስ በመባል ይታወቃል፡፡ ትሕትና ፍቅር መታዘዝ እንዲሁም የአገልግሎትን ትርጉም ለማስረዳትና ለማስገንዘብ የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠቡ ሕጽበተ ሐሙስ በመባልም እንደሚጠራ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይናገራሉ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስም «ወሶበ ኀፀቦሙ እገሪሆሙ ነሥአ አልባሲሁ ወረፈቀ ካዕበ ወይቤሎሙ አእመርክሙኑ ዘገበርኩ ለክሙ ... ወሶበ አነ እንከ ሊቅክሙ ወእግዚእክሙ ኀፀብኩክሙ እገሪክሙ ከማሁኬ አንትሙኒ ይደልወክሙ ትኅፅቡ እግረ ቢጽክሙ፡፡»፤ «እግራቸውንም አጥቦ ልብሱንም አንሥቶ ዳግመኛ ተቀመጠ እንዲህም አላቸው ያደረግሁላችሁን ታስተውሉታላችሁን?... እንግዲህ እኔ ጌታና መምህር ስሆን እግራችሁን ካጠብሁ እናንተ ደግሞ እርስ በእርሳችሁ ትተጣጠቡ ዘንድ ይገባችኋል ሲል ተናግሯል፡፡ /ዮሐ.13-12-20/፡፡

ይህ ስለ እናንተ በመስቀል ላይ የሚቆረሰው ሥጋዬ ነው እንካችሁ ብሉ፤ ይህ ስለ እናንተ የሚፈስ ደሜ ነው ከእርሱ ጠጡ በማለት ምሥጢረ ቁርባንን የመሠረተበት ወይም ራሱ ምስጢረ ቁርባንን የጀመረበት ቀን በመሆኑ የምስጢር ቀን ተብሎ ይጠራል፡፡ ይኸውም የሰው ልጆች ሥጋውንና ደሙን ተቀብለን ከእርሱ ጋር አንድነትና ኅብረት እንዲኖረን ጥንተ ጠላት ዲለብሎስንም ፍጹም ድል ነሥተን ሰማያዊት ርስት መንግሥተ ሰማያትን እንድንወርስ ለማስቻል ነው፡፡ /ማቴ.26-26-29/፡፡

አይሁድ ጌታችንን ለመያዝ በእነርሱ ጥበብና ፍላጐት ቀስ ብለው መጥተው የያዙበት ቀን ስለሆነ በዚህ ዕለት በለሆሳስ /ብዙ የድምጽ ጩኸት ሳይሰማ/ የቅዳሴ ሥርዓት ይፈጸማል፡፡ ስለሆነም መላው ሕዝበ ክርስቲያን በዚህ የሕጽበት፣ የምስጢር፣ የጸሎት ቀን በተባለው በዚህ ዕለት በንስሓ ታጥበው ሥጋ ወደሙ እንዲቀበሉ ቤተ ክርስቲያን በአጽንኦት ታስተምራለች፡፡

ዕለተ ዐርብ/ዓርብ/

ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ «አውቀውስ ቢሆን የክብርን ጌታ ባልሰቀሉት» /1ቆሮ.1-18/፡፡ እንዳለ ይህ ዕለት የአይሁድ ካህናት ያለበደል ያለጥፋት ንጹሕና ጻድቅ የሆነውን ጌታ የሰቀሉበት ዕለት ነው፡፡ ዕለቱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለም ሁሉ መድኃኒት ለአዳምና ለልጆቹ ሲል በመልእልተ መስቀል በቀራንዮ አደባባይ ተሰቅሎ መዋሉን የምናስብበት ታላቅ ቀን ነው፡፡ /ማቴ.27-35-75/፡፡ በዚያን ጊዜ አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ እንደተፈረደበት አይቶ ተጸጸተ ሠላሳውንም ብር ለካህናት አለቆችና ለሽማግሎች መልሶ ንጹሕ ደም አሳልፌ በመስጠቴ በድያለሁ አለ፡፡ እነርሱ ግን እኛስ ምን አግዶን? አንተው ተጠንቀቅ አሉ፡፡ ብሩንም በቤተ መቅደስ ጥሎ ሔደና ታንቆ ሞተ፡፡ የካህናት አለቆችም ብሩን አንሥተው የደም ዋጋ ነውና ወደ መባ ልንጨምረው አልተፈቀደም አሉ፡፡ ተማክረውም የሸክላ ሠሪ መሬት ለእንግዶች መቃብር ገዙበት፡፡ ስለዚህ ያ መሬት እስከ ዛሬ ድረስ የደም መሬት ተባለ፡፡ /ማቴ.27-3-9/
የሰው ልጆች በዘር ኃጢአት /ቁራኝነት/ ይኖሩበት የነበረው የጨለማ ሕይወት ያከተመበት ፍጹም ድኅነት ያገኙባት ታላቅ ዕለት ናት፡፡ ክርስቲያኖች ሁልጊዜም ዕለተ ዓርብ ሲመጣ ሕማሙን ስቅለቱን ሞቱን የሚያስቡበት ጊዜ ነው፡፡ በሮማውያን ሕግና ሥርዓት መስቀል የወንጀለኞች መቅጫ ምልክት የሕይወት መቅጫ አርማ ሆኖ ሳለ ለእኛ የዲያብሎስ ድል መንሻ ስላደረገው በስቅለቱና በሞቱም ሕይወትን ስለአገኘን በዚህም ምክንያት መልካሙ ዓርብ በመባል እንደሚታወቅ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ያትታሉ፡፡

በመስቀል ላይ ሳለ 7 ነገሮችን ተናገረ/7ቱ " አጽርሐ መስቀል " በመባል ይታወቃሉ። እነሱም፦
" አምላኬ አምላኬ ለምን ተውከኝ" ማቴ 17፦46
" አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው" ሉቃ 23፦34
" ዛሬ በገነት ከኔ ጋር እንድትኖር በእውነት እነግርሀለሁ" ሉቃ 23፦4
" አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ" ሉቃ 23፦ 46
" እነሆ ልጅሽ እነኋት እናትህ" ዮሐ 19፦26
" ተጠማሁ" ዮሐ 19፦28
" ሁሉ ተፈጸመ " ዮሐ 19፦ 30

ጌታ ሁሉ ተፈጸመ ብሎ ቅድስት ነፍሱን ከቅድስት ስጋው በራሱፈቃድ ከለየ በኋላ አምላክነቱን ለመግለፅ የታዩ ተአምራት የሚከተሉት ናቸው፤

በሰማይ፤ /ማቴ 24፦29 እና 27፦45/

1. ፀሐይ ጨለመች
2. ጨረቃ ደም ሆነች
3. ከዋክብት ረገፉ

በምድር፤/ማቴ 27፦51_53/
1. የቤተ መቅደስ መጋረጃ ከላይእስከ ታች ተቀደደ
2. ምድር ተናወጠች
3. መቃብሮች ተከፈቱ
4. ሙታን ተነሱ

ቀዳሜ ስዑር/ቅዳሜ/

ዕለተ ቅዳሜ እግዚአብሔር የሚታዩትንና የማይታዩትን፣ በእግር የሚሄዱትን እና በክንፍ የሚበሩትን በባሕር የሚዋኙትን እንስሳትን በመጨረሻም ሰውን በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ ያረፈበት ዕለት ነች፡፡ ይህች የመጀመሪያው ቅዳሜ ለእግዚአብሔር የዕረፍት ዕለት ናት እግዚአብሔርን ሥነ ፍጥረት ፈጥሮ ስላረፈበት ሰንበት ዐባይ /ታላቋ ሰንበት/ ትባላለች ታላቋን ሰንበት እስራኤላውያን እንዲያከብሯት ታዟል፡፡ ዘፍ.1፡3፡፡

ዕለተ ቀዳሚት /ሰንበት ዐባይ/ በዘመነ ሐዲስም የተለየ የደኅነት ሥራ ተከናውኖባታል፡፡ ጥንት ሥነ ፈጥረትን በመፍጠር ዕረፍት እንደ ተደረገባት ሁሉ የፍጥረት ሁሉ ቁንጮ የሆነውን አዳምን ለማዳን ሕማምና ሞት የተቀበለው ቸሩ አምላክ በመቃብር አርፎባታል፡፡ ማቴ.27፡61፡፡

በዚህች ዕለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከርሰ መቃብር ዐርፎ የዋለባት ዕለት በመሆኗ «ቀዳሜ ስዑር » ትሰኛለች፡፡ ስዑር ቀዳሜ የተባለችው በዓመት አንድ ቀን ስለ ምትጾም ነው፡፡ ምክንያቱም እናቱ ድንግል ማርያም ወዳጆቹ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታ ተላልፎ ከተሰጠበት ዕለት አንስተው ብርሃነ ትንሣኤውን እስኪያዩ ድረስ እህል ውኃ በአፋቸው አልዞረም፡፡ ይመኩበትና ተስፋ ያደረጉት የነበረ አምላካቸው በመቃብር ስላረፈ ዕለቷን ሞቱን በማሰብ ትንሣኤውን በመናፈቅ በጾም አክብረዋታል፡፡
ከቅዱሳን ሐዋርያት ሲወርድ ሲወራረድ በመጣው ትውፊት መሠረት ቅዱሳን ሐዋርያት በማዘን በመጾምና በመጸለይ ዕለቷ እንዳከበሯት የተዋሕዶ ልጆች የተቻላቸው ከዓርብ ጀምረው የሚያከፍሉ /የሚጾሙ/ ለሁለት ቀን እህል ውኃ ሳይቀምሱ ያድራሉ ያልተቻላቸው ደግሞ ዓርብ ማታ በልተው ቅዳሜን በመጾም ትንሣኤን ያከብራሉ፡፡

በዚህ ዕለት ከሰኞ ከሆሣዕና ማግሥት ጀምረው እስከ ስቅለተ ዓርብ ድረስ በስግደት እና በጾም ያሳለፉ ምእመናን በዕለተ ቅዳሜ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ይሰበሰባሉ፡፡ የጠዋቱ ጸሎት ሲፈጸም ካህናቱ «ገብረ ሰላመ በመስቀሉ፡-በመስቀሉ ሰላምን መሠረተ» የምሥራች እያሉ በቤተ ክርስቲያን ለተሰበሰቡት ምእመናን ቄጠማ ይታደላል ቄጠማው የምሥራች ምልክት ነው፡፡ ቄጠማው የምሥራች ምልክት ተደርጐ የተወሰደው በኖህ ዘመን ከተፈጸመው ታሪክ ጋር በማቆራኘት ነው፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን በጻድቁ ኖኅ ዘመን የነበሩ ሕዝቦች ከሕገ እግዚአብሔር ውጪ ሆነው እጅግ የሚያሳዝን ኃጢአት በሠሩ ጊዜ በንፍር ውኃ ተጥለቅልቀዋል፡፡ በወቅቱ ጻድቁ ኖኅ ወደ መርከብ ይዞአቸው ከገባው እንስሳት መካከል የውኃውን መጉደል ለመረዳት ርግብን በመርከብ መስኮት አሾልኮ ይለቃታል፤ እርሷም ቄጠማ በአፍዋ ይዛ ትመልሳለች፡፡ ዘፍ.9-1-29፡፡ ኖኅም በዚህ ቄጠማ የውኃውን መድረቅ ተረድቶ ተደስቷል፡፡

«ቄጠማ»፣ ለጥፋት ውኃ መድረቅ የምሥራች መንገሪያ እንደሆነ አሁንም በክርስቶስ ሞት ሞተ ነፍስ ከሰው ልጆች ተወገደ ስትል ቤተ ክርስቲያን ለልጆቿ ቄጠማ ታድላለች፡፡ ምእመናንም የምሥራች ተምሳሌት የሆነውን ቄጠማ በግንባራቸው ያስሩታል፡፡
የክርስቶስ ተከታዮች ሁሉ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሚያቃጥለው ዋዕየ ሲኦል /የሲኦል ቃጠሎ/ ወደ ልምላሜ ገነት ጥንተ ማኅደራቸው መመለሳቸውን በዚህ አኳሃን እየገለጡ በዓለ ትንሣኤን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያከብራሉ፡፡

ሃይማኖታዊና ትውፊታዊ ክንዋኔዎች በሰሙነ ሕማማት

በዐቢይ ጾም ከሠርክ ሆሣዕና ጀምሮ እስከ ትንሣኤ ሌሊት ዕለታት የሚገኙበት ሳምንታት ሰሙነ ሕማማት ይባላሉ፡፡ ዕለታቱም የዓመተ ፍዳ፣ የዓመተ ኩነኔ መታሰቢያ ናቸው፡፡ በእነዚህ ዕለታት ውስጥ የተለያዩ ትውፊታዊ እና ሃይማኖታዊ ክንዋኔዎች አሉ፡፡ ከነዚህ ክንዋኔዎች ውስጥ አለ መሳሳም፣ አክፍሎት፣ ቄጤማ ማሰር፣ ጥብጣብ፣ ጉልባን እና ሕጽበተ እግር ይገኙበታል፡፡ ስለእነዚህ ክንዋኔዎች በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስላለው ትውፊታዊ አፈጻጸም መዛግብት አገላብጠን እና በኢትዮጵያ ኣርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት ጉባኤ አባል የሆኑትን ሊቀ ካህሃት ክንፈ ገብርኤል አልታዬን አነጋግረን እንደሚከተለው አቅርበናል፡፡

አለመሳሳም

በሰሙነ ሕማማት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች መስቀል እንደማይሳለሙት ሁሉ መጨባበጥ፣ መሳሳምና የትከሻ ሰላምታ መለዋወጠን አይፈጽሙም፡፡ ሰላምታ የማንለዋወጥበት ምክንያት፣ አይሁድ ጌታን ለመስቀል ሰኞ እና ማክሰኞ መከሩ አልሠመረላቸውም፡፡ ምክራቸው የተፈጸመው ረቡዕ ነው፡፡

ስለዚህ አይሁድ አያንሾካሾኩ “እንስቀለው… አንግደለው” ብለው ይማከሩ ነበር፡፡ ያነን ለማስታወስ ሰላምታ አንለዋወጥም፡፡ መስቀልም አንሳለምም፡፡ ሳምንቱ የክፋት ምክር የተመከረበት እንጂ የፍቅርና የደስታ ሰላምታ የታየበት ባለመሆኑ ይህንን በማሰብ ሰላምታ አንለዋወጥም፡፡
ይሁዳ ጌታን በጠላቶቹ ለማስያዝ “እኔ የምስመው እርሱ ነው፤ ያዙት” ብሎ በሰላምታው ምልክት ሰጣቸው ይህ ሰላምታ አምሐ ቅድሳት አይደለም፤ ተንኮል የተሞላበት እንጂ፡፡ የዲያቢሎስም ሰላምታ ተመሳሳይ ነው፡፡ ሔዋንን “ሰላም ለኪ” ብሎ ነው ያታለላት፣ የዲያቢሎስ እና የይሁዳ ሰላምታ ሰይጣናዊ ነው፡፡ ስለዚህ ይህንን ወቅትና ሁኔታ ለማሰብ በሰሙነ ሕማማት ሰላምታ ልውውጥ የለም፡፡ ዛሬ እየተስተዋለ ያለው ይኸው ሰላምታ ያለመለዋወጥ ሁኔታ ሥርወ መሠረቱ ይህ ነው፡፡ ከጥንት ጀምሮ እዚህ ትውልድ ላይ ደርሷል ይቀጥላልም፡፡

ሕጽበተ እግር

ጌታ በፍጹም ትሕትና የደቀ መዛሙርቱን እግር ያጠበበት፣ ከሐዋርያት ጋር ግብር የገባበትና የክርስትና ሕይወት ማሕተም የሆነውን ምሥጢረ ቁርባን ያከናወነበት ዕለት ነው ጸሎተ ሐሙስ፡፡

ሕጽበተ እግር ጌታችን በዚህ ዕለት “አናንተ ለወንድማችሁ አንዲህ አድርጉ” ለማለት የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠቡ ምክንያት የተሰጠ ምሳሌ ነው፡፡ ይህም የሚያሳየው “አኔ ለአናንተ እንዳደረግሁ እናንተ ደግሞ ታደርጉ ዘንድ ምሳሌ ሰጥቻችኋለሁና፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ ባሪያ ከጌታው አይበልጥም፣ መልእክተኛም ከላከው አይበልጥም፤ ይህን ብታውቁ ብታደርጉትም ብፁዓን ናቸሁ” /ዮሐ.13÷16-17/ በማለት ትሕትናውን አሳይቷል፡፡

ጌታ በዚህ ዕለት የደቀ መዛሙርቱን እግር ሲያጥብ “እኔ መምህራችሁ ስሆን እግራችሁን ካጠብኳችሁ አርአያዬን ሰጥቻችኋለሁ፤ እናንተም የወንድማችሁን እግር ታጥቡ ዘንድ ይገባል፡፡ ነገር ግን ከእናንተ አንዱ ለሞት አሳልፎ ይሰጠኛል” አለ፡፡ ደቀ መዛሙርቱም “ማን ይሆን?” አሉ፡፡ ጌታም “ኅብስት ቆርሼ፣ ከወጡ አጥቅሼ የምሰጠው እርሱ ነው” አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ደነገጡ፡፡ ይሁዳን ማመልከቱ ደነገጡ፡፡ ይሁደን ማመልከቱ ነበር፤ ለጊዜው አልገባቸውም፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን የሐዋርያቱን እግር በማጠብ ትሕትናን ካስተማራቸው በኋላ፤ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ሰጣቸው፤ የኦሪትን መሥዋዕት የሻረው እና መሥዋዕተ ሐዲስን የሠራው በዚሁ ዕለት ነው፡፡

በዚህ ሃይማኖታዊ መነሻነትም በገጠሪቱ ኢትዮጵያ የሚከናወኑ ድርጊቶች አሉ፡፡ ለምሳሌ፡- በወሎና በጎንደር ከጉልባን በተጨማሪ በተለይ በጸሎተ ሐሙስ ዕለት ብቻ የሚጋገር የተለየ ዳቦ አለ፡፡ ይህ ልዩ ዳቦ በወሎ “ትኩሴ” በጎንደር ደግሞ “ሙጌራ” ይባላል፡፡ ይህ ዳቦ ጌታ ለሐዋርያት የሰጣቸው ኅብስት አምሳያ ነው ተብሎ ስለሚታሰብ ከዚህ ቀን ውጪ በሌላ ጊዜ አይጋገርም፡፡ በመሆኑም ሰው ሁሉ ዳቦውን ለመብላት የሚጠባበቀው በታላቅ ጉጉት ነው፡፡ አልፎ አልፎ ግን ሃይማኖታዊ ሥርዓት በሚከበርባቸው እንደ ማኅበርና ሰንበቴ በመሳሰሉት መንፈሳዊና ማኅበራዊ ትውፊቶች የሚቀርብበት ጊዜ አለ፡፡
በትግራይ በዕለተ ስቅለት ከተለመደው የጾምና የስግደት ሥርዓት በተጨማሪ የሚከናወኑ ድርጊቶች አሉ፡፡ በዕለቱ ለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት መታሰቢያ ሲባል ወንዶች ልጆች በሙሉ ፀጉራቸውን እንዲላጩ ይደረጋል፡፡ ያን ቀን ያልተላጨ ልጅ “ኃጢአት ይሆንበታል” ስለሚባል ሳይላጭ የሚውል ልጅ የለም። ልጃገረዶች በበኩላቸው በዛፍ ላይ ገመድ በማሰር ዥዋዥዌ ይጫወታሉ፡፡ ይህንንም የሚያደርጉት የጌታን እንግልትና መስቀል ለማዘከር ነው ይባላል፡፡
እነሆ ይህንን ዕለት በማስታወስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሐዶ ቤተ ክርስቲያን ከሊቃነ ጳጳሳት ጀምሮ እስከ ቀሳውስት ያሉት አባቶች በያሉበት አጥቢያ /ደብር/ በመገኘት በመዓርግ የሚያንሷቸውን የካህናት፣ ዲያቆናት እና የምእመናንን እግር ያጥባሉ፤ የሚያጥቡትም የወይራ እና የወይን ቅጠል በመዘፍዘፍ ነው፡፡

አክፍሎት

በሰሙነ ሕማማት ዕለተ ዓርብ ከስግደት በኋላ ምእመናን በየቤታቸው ጥቂት ነገር ለቁመተ ሥጋ ቀምሰው እስከ እሑድ /የትንሣኤ ሰዓት/ ይሰነብታሉ፡፡ ይህ አክፍሎት ይባላል፡፡ ብዙው ምዕመን ከዓርብ ጀምሮ የሚያከፍል ሲሆን አንዳንዶች ግን ከሐሙስ ጀምረው ያከፍላሉ፡፡ ይህም እመቤታችን፣ ያዕቆብ እና ዮሐንስ የጌታን ትንሣኤ ሳናይ እህል ውኃ አንቀምስም ብለው እስከ ትንሣኤ መቆየታቸውን ተከትሎ የመጣ ትውፊት ነው፡፡

ይህንን ትውፊት አስመልክቶ ሄሬኔዎስ፣ አውሳብዮስ የተባሉ ጸሐፍት፤ ሐዋርያት በሰሙነ ሕማማት ከደረቅ ዳቦ አና ከትንሽ ውኃ በቀር እንደማይመገቡ እና ከሐሙስ ጀምረው እንደሚያከፍሉ ጽፈዋል፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን ሐዋርያት ሌሎቹንም እንዲያከፍሉ እንዳሳሰቡና ከሐሙስ ጀምሮ ያልተቻለው ቢያንስ ከዓርብ ጀምሮ እንዲያከፍል ማዘዛቸውን ጽፈዋል፡፡ የእኛ ቤተ ክርስቲያን ትምህርትም ይኸው ነው፡፡ ቅዳሜ ይበላል ማለት ግን ቅዳሴው ሌሊት ስለሆነ በልቶ ማስቀደስ ነውና በልቶ እንደመቁረብ ይቆጠራል፡፡

ጉልባን እና ቄጤማ

ጉልባን ከባቄላ ክክ፣ ከስንዴ ወይንም ከተፈተገ ገብስ ጋር አንድ ላይ ተቀቅሎ የሚዘጋጅና የጸሎተ ሐሙስ ዕለት የሚባላ ንፍሮ ነው፡፡ የጉልባን ትውፊት እስራኤላውያን ከግብፅ ተሰደው በሚወጡበት ጊዜ በችኮላ ስለነበር፤ አቡክተው ጋግረው መብላት ያለመቻላቸውን ሁኔታ ያመለክታል፡፡ ያን ጊዜ ያልቦካውን ሊጥ እየጋገሩ ቂጣ መብላት፤ ንፍሮም ቀቅለው ስንቅ መያዝ ተግባራቸው ነበር፡፡ ይህን ለማሰብ በሰሙነ ሕማማት ቂጣና ጉልባን በማዘጋጀት በዓሉ ይታሰባል፡፡
በጸሎተ ሐሙስ ይህንን መሠረት በማድረግ የሚዘጋጀው ጉልባን አንዲህም ቂጣ ጨው በዛ ተደርጎ ይጨመርበታል፡፡ ጨው ውኃ የሚያስጠማ በመሆኑ የጌታን መጠማት ያስታውሳል፡፡ ይህ ትውፊታዊ ሥርዓት ከእስራኤላውያን የመጣ ሲሆን በኢትዮጵያም አብዛኛዎቹ የትውፊት ክንዋኔዎች የብሉይ ኪዳን መነሻ ስላላቸው ሥርዓቱ ዛሬም ይከበራል፡፡

ጥብጣብ

በሰሙነ ሕማማት ዕለተ ዓርብ የስቅለቱ መታሰቢያ ነው፡፡ ምእመናኑ በሰሙነ ሕማማት የሠሩትን ይናዘዛሉ፡፡ ካህናቱም በወይራ ቅጠል ትከሻቸወን እየጠበጠቡ ቀን ከሰገዱት ስግደት በተጨማሪ ሌላ ስግደት ያዟቸዋል፡፡ ጥብጠባው የተግሳፅ ምሳሌ ነው፡፡ ጥብጣብ የሚደረግለት ሰው በሕማማቱ ወቅት የፈጸመው በደል ወይንም ኃጢአት ካለ ይህንኑ በመናገር የስግደቱ ቁጥር ከፍ እንዲል ይደረጋል፡፡
ይህ በስቅለት ቀን የሚፈጸም ሥነ ሥርዓት ሲሆን፤ ጠብጣቤ ማለት ቸብ ቸብ ማድረግ ማለት ነው፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑ በዕለተ ስቅለት ሲሰግድ ሲጸልይ፣ ሲያነብ ከዋለ በኋላ ሰርሆተ ሕዝብ /የሕዝብ መሰነባበቻ/ ከመሆኑ በፊት፤ በወይራ ቅጠል እያንዳንዱን ምእመን ጀርባ ቸብ ቸብ መደረጉ፣ የጌታን ግርፋት ያስታውሳል፡፡

ቀጤማ

በቀዳም ስዑር ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ቃጭል /ቃለ ዓዋዲ/ እየመቱ “ገብረ ሰላመ በመስቀሉ ትንሣኤሁ አግሃደ” የሚለውን ያሬዳዊ ዜማ በመዘመር፤ ጌታ በመስቀሉ ሰላምን እንደሰጠን እና ትንሣኤውንም እንደገለጠልን በማብሰር፤ ቀጤማውን ለምእመናን ይሰጣሉ፡፡ ምእመናኑም ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውል ገጸ በረከት ያቀርባሉ፡፡ ቀጤማውንም በራሳቸው ያስራሉ፡፡ ይህም አይሁድ ጌታችንን እያሰቃዩ ሊሰቅሉት ባሉ ጊዜ የእሾህ አክሊል ጭንቅላቱ ላይ የደፉበትን ድርጊት የሚያስታውስ ነው፡፡
በዚህ ዕለት ልብሰ ተክህኖ የለበሱ ካህናትና ዲያቆናት ቀጤማ ተሸክመው ቃጭል ሲያቃጭሉ መታየታቸው ዕለተ ትንሣኤውን ለሚናፍቅ ምእመን ትልቅ ብስራት ነው፡፡

ያብጽሃነ ያብጽሕክሙ!

(ምንጭ፦ ስምዐ ጽድቅ ልዩ እትም ዘሰሙነ ሕማማት መጋቢት 2002)

Friday, April 11, 2014

ስደት (ክፍል ፫)


ስደትን በተመለከተ በክፍል (Part 1)እና ፪(Part 2) በጻፍኳቸው መጣጥፎች ላይ ለስደት ያበቁንና ዛሬም ብዙ ኢትዮጵያውያንን ከአገራቸው እንዲሰደዱ እያደረጉ ያሉትን ጉዳዮች ጠቅለል አድርጌ ለማቅረብ ሞክሪያለሁ  የስደትን አስከፊነትም በመጠኑም ቢሆን ሳልጠቅስ አላለፍኩም። ዛሬም እኛ ኢትዮጵያዊያንን  ከስደት ሊታደገን የሚችል ሰማያዊ ኃል ካልመጣ በስተቀር የምንወዳትን አገራችንን ጥለን ወደ ባዕድ አገር መፍለሱን ተያይዘነዋል። ዓለምም ዋነኛ የዜና ክፍል አድርጎ ሲነግረን እንሰማለን።
ስደት ዘርፈ ብዙ ነው፤ አይነቱም መገለጫውም የተለያየ ነው። መንገዱም እንዲሁ አድካሚ፣ ውስብስብ፣ እልህ አስጨራሽና ለምን ወደዚህ ዓለም አመጣኸኝ እያሉ ከፈጣሪ ጋር ክርክር የሚያስነሳ ነው። ስደትን ሁሉንም በአንድ ላይ ጠቅልሎ  መግለጽ እጅግ ከባድና አስቸጋሪ ነው። ምክንያቱም ስደት በተለያየ መልኩ ሊገለጽ ይችላልና፤ የአካል ስደተኛ፣ የመንፈስ ስደተኛ፣ የአዕምሮ  ስደተኛ  በማለት መዘርዘር ይቻላል። በዋናነት ግን  የፖለቲካ  ስደተኛ(political migrant) እና የኢኮኖሚ ስደተኛ(Economic migrant) ብሎ ከአገራችን ኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁናቴ ማየት ይቻላል።
የፖለቲካ ስደተኛ ማለት በአጭሩ አንድ ሰው በፖለቲካ እንቅስቃሴ ምክንያት በመደገፍም ሆነ በመቃዎሙ በአገሩ መኖር ባለመቻሉ ህይወቱን እና እራሱን ነጻ አድርጎ መኖር ይቻላል ብሎ ወደሚያስበው አገር መሰደድ ማለት ነው። አንድ ሰው ከወንጀል በስተቀር የሚፈልገውን ነገር በነጻነት ማከናወን እና በነጻነት መኖር ካልቻለ ግዴታ ወደማይፈልገው የስደት ሕይወት ይገባል። በተለይ በማደግ ላይ የአሉ አገሮች የዚህ ችግር ሰለባዎች ናቸው። በአገራችንም የምናየው ዋነኛ ችግር ይህ ነው።
ሕወሓት በስልጣን ላይ እስካለ ድረስ በነጻነት መናገር፣ በነጻነት መጻፍ፣ በነጻነት መወያየት፣ በነጻነት መቃወም፣ በነጻነት መደገፍ፣ በነጻነት መስራት፣ በነጻነት መማር፣ በነጻነት መደራጀትና በነጻነት ማምለክ ፈጽሞ የማይሞከሩ ነገሮች ናቸው። በሌላ አነጋገር ሕወሓት እና ነጻነት አይተዋወቁም። ዲሞክራሴ ማለት ለወያኔ/ኢህአዴግ ህዝብን ካለምክንያት ማሰር፣መግደል፣ ማሰቃየት ማለት ነው። ነጻነት ለእነሱ እነሱን መደገፍ፣ ከእነርሱ ጋር አብሮ በሙስና መጨማለቅ ነው።መጻፍናመናገር ነጻነት ለእነርሱ ለፓርቲያቸው ውዳሴ ማቅረብ ነው ልማት ለእነርሱ በተግባር ሳይሆን በቃል ብቻ 11% ማደግ አገርን መሸጥ እና ሰባዊ መብትን ከመገንባት ይልቅ ህንጻና መንገድ መገንባት ማለት ነው። ማምለክ ለእነርሱወያኔ ወይም/እናባለዕራዩ መለስ ማምለክና መስገድ ብቻ ነው። ይህ ብቻ ነው ለሕወሓት ዲሞክራሲ፣ ነጻነትና ልማት። ይህ ነው ለእነርሱ ብልጽግና እድገት።
በኢህአዴግ/ወያኔ የአገዛዝ በደል እና የዘር ፖለቲካ ባመጣው መዘዝ ለአገር እድገት መልካም የሚያስብ ሰው በቀላሉ መኖር አልቻለም። እንዲኖርም አይፈቀድለትም። ብዙ ሰዎች ሥርዓቱን በመቃወም፣ አስተዳደራዊ ለውጥ፣ የፖሊሲ ለውጥ ያስፈልጋል ብለው የሚታገሉ ብዙ ሰዎች አፋቸውን እንዲዘጉ ተደረጉ፣ ታሰሩ፣ ተገደሉ የቀሩትም ከአገር እንዲወጡ ተደረገ። ሚዲያዎች፣ድረ ገጾች፣ የግል ኮምፒወተሮችና የስልክ መስመሮች ሳይቀሩ ሲዘጉና ተጠልፈው በእነርሱ ቁጥጥር ስር እንዲሆኑ አድርገዋል በዚህም ምክንያት ሰው እራሱን እንኳ መጠራጠር ጀምሯል።
እንዲሁም የምጣኔ ሃብት ስደተኛ (economic migrant's) ማለት ደግሞ በምጣኔ ሃብት እጦት ምክንያት ይበላውና ይጠጣው ያጣ ከእጅ ወደአፍ ለማግኘት ከቦታ ወደቦታ የሚያደርገው ፍልሰት ነው። እንደአገራችን ተጫባጭ ሁኔታ ስንመለከት ብዛት ያላቸው ወጣቶች ወደ ተለያዩ  የዓለም ክፍላት ሲጓዙ እንመለከታለን። ብዙዎችም በርሀ ለበርሀ ከአሰቡበት ሳይደርሱ በመንገድ ቀርተዋል፤ በአረብያውያን ቅኝ ግዛት ወድቀው የስቃይና የመከራ ድምጽ በማሰማት ላይ ያሉትን መጥቀስ ከበቂ በላይ ነው። 
እዚህ ላይ ግን የኢትዮጵያን የድህነት ሁኔታ ሳይሆን ማንሳት የፈለኩት መንግስት ነኝ ባዩ አገራችን  ኢትዮጵያ ስመዘገበች ንን ፈጣን እድገት(11%)  እና ዛሬ ላይ ያለውን የኑሮ ውድነት እንዲሁም ወጣቱ ትውልድ በሥራ አጥነት ሳቢያ ያደርገውን ስደት በቀላሉ ማነጻጸር እንድንችል ነው። በእውነት እድገት፣ ልማት የሚጠላ ሰባዊ ፍጡር የለም። ማንም ሰው ማደግመለወጥ የተሻለ ኑሮ መኖር በእጅጉ ይፈልጋል ይሻልም ውጥ እድገት መፈለግ ተፈጥሮአዊ ባህርይ ነው።
ታዲያ አገራችን ኢት ከአደገች፣ ፈጣን እድገት ካስመዘገበች፣ ለውጥና ነጻነት ካለ በየትኛው መመዘኛ ነው ህዝቦቿ ስደትን የመረጡት??? በምን ምጣኔ ሃብታዊ ቀመር ነው ህዝቦቿ በርሀብ አለንጋ የሚሰቃዩት? የዘርፉ ሙህራን እንደሚናገሩት የአንድ አገር እድገት የሚለካው ህንጻ በመገንባት ሳይሆን የህብረተሰቡ የእለት ከእለት ኑሮ መለወጥና ሰባዊ መብቶች ሲከበሩና ሲጠበቁ ነው። ሰባዊ መብቶች እየተገፈፉ፣ ርሀብና የኑሮ ውድነት ተባብሶ ልማት፣ ፈጣን እድገት፣ ብልጽግና የለም። እርግጥ ነው ሕወሓትና ደጋፊዎቹ የአገሪቱን ንብረት በመሰብሰብ ይህ ነው የማይባል ሀብት አካብተዋል፤ ነጻነቱንም ለግላቸው አድርገዋል።
በፖለቲካም ሆነ በኢኮኖሚ ምክንያት የኢትዮጵያ ህዝብ ስደትን እንዲመርጥ የተገደደው በሕወሓት አሳፋሪና አስነዋሪ የአስተዳደር ሥርዓት ነው። አስተዳደሩም ሆነ  ልማቱ ህዝብ ተጠቃሚ በሚሆን መልኩ ማስኬድና ለውጥ ማምጣት በእጅጉ ይቻላል። ነገር ግን ቅን ልቦና የለም፤ የህብረተሰቡን መለወጥም አይፈለጉም። ምክንያቱም ድርጅቱ ራስ ወዳድ እንጂ አገራዊ ስሜት የለውም። አገሪቱን እርሱ እና መሰሎቹ እንደፈለጉ አድርገው እየተጠቀሙባት ነው የተረፈውን ደግሞ ለውጭ ባለሀብት በዶላር ቆራርሰው እየሸጧት ነው (Land grabbing )። ዜጋው ግን በብሔር፣ በተቃማሚ ፖለቲካ ስም ስቃይና መከራን በማብዛት ከቦታው እንዲፈናቀል ይደረጋል ተደርጓልም። ፖለቲካዊ ነጻነት እና እንደ ዜጋ የአገሩን ሃብትና ንብረት በነጻነት መጠቀም የሚባል ነገር ፈጽሞ ባለመኖሩ ትውልዱ ስደትን መረጠ።

በአጠቃላይ እኛው እራሳችን ነጻነታችን ማወጅ ይኖርብናል እንጂ ሌላ ታምራዊ ኃይል ሊመጣና ከስደት ሊታደገን ከቶ አይችልም። እርግጥ ነው ፈጣሪ የህዝቡን ዋይታና እሮሮ ሰምቶ ለነጻነት ምክንያት የሚሆን ሰው ሊያስነሳ ይችላል። ነገር ግን እኛ ዝም ብለን የፈጣሪን ሥራ መጠበቅ ግን በእራሳችን ላይ የመከራ ጊዜን እንደማራዘም ይቆጠራል። ፈጣሪ የራሱን ሥራ  በራሱ ጊዜ ይሰራል። እኛም የራሳችንን ሥራ መስራት ይጠበቅብናል። ነጻነታችንን ማስጠበቅ፣ አገራችንን መታደግ፣ለወገናችን መድረስ ሰባዊ መብታችን ነው። ስለዚህ ሰባዊ መብታችንን ተጠቅመን ይህን ፈላጭ ቆራጭ መንግስት ነኝ ባይ የዘር ፖለቲካ አራማጅ ሕወሓትን በቃህ፣ ስደት ይብቃ ልንለው ይገባል።

Tuesday, April 1, 2014

ስደት (ክፍል ፪)


ስደትን በተመለከተ በክፍል ፩( በጻፍኩት ጽሁፍ ላይ ትልቁን ለሰው ልጅ የአእምሮ ረፍትና የወደፊት ተስፋ የሚሆነውን ነጻነት መነፈግ ለኢትዮጵያ ህዝም ብሎም ለዓለም ህብረተሰብ አስቸጋሪ በመሆኑ ለስደት ዋነኛ ምክንያት እንደሆነ ገልጨ ነበር። ጠቅለል ባለመልኩ እኛ ኢትዮጵያውያን የመተሳሰብ፣ አብሮ የመብላት፣ በነጻነት የመስራትና የመንቀሳቀስ፣ መሰረታዊ የሰው ልጅ የእዉቀት ደረጃዎችን ማለትም የመጻፍና የመናገር፣ እንዲሁም መንግሥት እራሱ በእራሱ ህገ መንግሥት ነው ብሎ ባረቀቀው "መንግሥት በሀይማኖት ጣልቃ አይገባም ሃይማኖትም እንዲሁ/The state shall not interfere in religious masters and religion shall not interfere in state affairs"(አንቀጽ 113) ያለውን የእራሱን ህግ ሳይቀር በመጣስ የማምለክ ነጻነታችንን በበሬ ወለድ ምክንያት ሲገፍ እና አንድነታችንን፣ ባህላችንንና ለነገ የሚያስበውን ትውልድ ሲያስር፣ ሲያንገላታና ለስደት ሲዳርግ ብሎም ሲገድል ድፍን 23 ዓመት አስቆጠረ።

ይህ የስቃይና የመከራ ዘመን የሚያበቃበትን ቀን እና ስዓት የኢትዮጵያ ህዝብ የሚያመልከውን አምላክ በመማጸን ላይ ነው። በተቃራኒው የህወሓት አገዛዝ ዘላለማዊ ነኝ ማለቱን ተያይዞታል። ታግሎ ነጻነቱን እንዳያስከብር ከጫካ ጀምሮ የሰራበትን የሥልጣን እድሜ ማራዘሚያ የብሔር ተኮር የዘር የእርስ በእርስ ግጭትና የሀይማኖት ተቋማትን የማፍረስ ፖለቲካ በህዝቡ ላይ በማሰራጨቱ ለነጻነት በህብረት በአንድነት እንዳንታገል አድርጎናል። እርስ በእርሳችን እንዳንተማመን አድርጎናል፤ ከፋፍሎናል። ህብረት አንድነት እንዳይኖረን በማድረግ ለስደት ዳርጎናል።

ኢትዮጵያ የምትባል አገር እንዳትኖር እና ካርታ እንዳይኖራት አድርጓታል። መለያ ምልክቷን ሰንደቅ ዓላማዋን ቀይሮባታል። በቅኝ ግዛት ያልተንበረከኩ ህዝቦቿን መከራ እና ስቃይ በማብዛት በግድ ለባርነት/ለስደት ዳርጓቸዋል። ሰላም የጠፋበት፣ ተስፋ የሌለው፣ ለማንነቱ የማይጨነቅ፣ ለአገር ለወገኑ የማያስብ ትውልድ መናኽርያ እንድትሆን አድርጓል። በራብ አለንጋ ሳይቀር ሰፊውን ህዝብ እየቀጣ ነው። ከራብ ጦር ይሻላል እንዲሉ ከራብ፣ ከጭቆና ነጻነት ከማጣት ስደትን መረጠ፣ በየአገሩ ስደተኛ ተብለው እንድንኖር አደረገን። አይ ህወሓት የስራችሁን ይስጣችሁ ሌላ ምን ይባላል.....የባለ ዕራዩን (የአምላካችሁን) መለስ ተብዬው እጣ ፈንታ ይስጣችሁ እንዳንል እርግማን ነው። የኢትዮጵያ ህዝብ የዋህ እና በፈጣሪው የሚያምን ነው እርግማን ፈጽሞ ይጠላል፤ ድህነታችሁን እንጂ ሞታችሁን አንሻም። ስቃዩን፣ መከራውን፣ እስራቱን አቅሉልን እንጂ ጣን ልቀቁ የማይል ህዝብ ነው። እንዳለመታደል ሁኖ እንጂ እንዴት ለዚህ ህዝብ ነጻነቱን ይገፈፋል፣ ማንነቱንና ታሪኩን እንዲያጣ ይደረጋል።

ለአገር እድገትና ብልጽግና ዋነኛ መሰረት ሙያዊ ነጻነት(academic freedom) መሆኑን የዘርፉ ሙህራን ይስማሙበታል። የሰው ልጅ በተፈጥራዊም ሆነ በግላዊ ጥረት እራሱን፣ ቤተሰቡን ከዚያም አልፎ አገርን መለወጥ መቀየር የሚያስችል እውቀት/ሙያ አለው። ሙያዊ ነጻነት ከደሞዝ፣ ከክፍያና ከማንኛውም ጥቅማ ጥቅም በላይ ነው፣ ከሹመትና ሽልማት በላይ ነው። ሁሉም ማለት ይቻላል ሙያዊ እውቀት ለማግኘት ወደ / ዓለም ሲገባ የሚያስደስተውን እና ቢሰራበት የበለጠ ውጤት ማምጣት ወደሚችልበት የት/ መስክ ይገባል። ለዚህ ትውልድ ያገኘውን እውቀት ካለንም ተጽዕኖ መስራት የሚችልበትን መልካም ከባቢያዊ ሁኔታዎችን ማመቻቸት እና ማስተካከል የነበረበት ዲሞክራሲያዊ እና ልማታዊ ነኝ የሚለው መንግሥት ነኝ ባዩ ፈላጭ ቆራጩ የህወሓት ቡድን ነበር። በተቃራኒው ግን እየሰራ ያለው ገና በለጋ እድሜያቸው ሳይቀር ተማሪዎችን የእርሱ ተከታዮች እንዲሆኑና የብሔር ፖለቲካን ሲዘራባቸው ይታያል። ወደከፍተኛ / ሲገቡም ሲወጡም ለጊዜው ለመኖር ዋስትና (green card) የሆነችውን ቁራጭ ወረቀት (የአባልነት መታወቂያ መሆኗ ነው) ይዘው እንዲወጡና የስራ ዕድል እጣ ፈንታ በዚያ እንደሚወሰን አጠንክሮ መልእክቱን ያስተላልፋል። ለማሳያም ያክል በየከፍተኛ / ተቋማት ውስጥ የመንግሥት ተልኮን የሚያራምዱትን አድር ባዮች ካለሙያቸው፣ ካለ እውቀታቸውና ካለችሎታቸው ከፌደራል እስከ ቀበሌ የየመስርያ ቤቱ ኃላፊዎች እያደረገ ይሾማል። የተለየ ጥቅማጥቅም ይሰጣቸዋል። በሙስና የተጨማለቁ እንዲሆኑ እና በፍራቻ የስርዓቱ ሎሌዎች አድርጓቸዋል።

ይህን እና መሰል ሁኔታወችን በማየት ሁሉም በሚያስብል መልኩ የከፍተኛ / ተቋማት ተማሪዎች ከልባቸውም ባይሆን የገዥው ፓርቲ ደጋፊ እና ተላላኪ እንዲሆኑ ተደርገዋል። ከዛም አልፎ በስራ ላይ ሰራተኛውን ስራውን በአግባቡ እንዳይሰራ ጀርባው እና የሚያደረገውን እያንዳንዱ እንቅስቃሴ ለማጥናት የስለላ ስራ እንዲሰሩ ይደረጋል። አንድ ለአምስት(15) በሚል ሚስጥራዊ የህወሓት ቡድን ሁሉም እንዲካተቱ እና የፓርቲው አገልጋዮች ተደርገዋል። የቀሩትም ከእጅ ወዳፍ ለማግኘት ሲሉ ወደው ሳይሆን ተገደው በቡድኑ ውስጥ ተካተዋል። በዚህ ቡድን እና ተመሳሳይ እኩይ ተግባር አንተባበርም ያሉት ኢትዮጵያውያን እና እድገቷን የሚሹ እውነተኛ ልጆች ስቃይና መከራ ሲበዛባቸው እና ከእስርና ከሞት የተረፉት ለስደት ተዳርገዋል።

በዚሁ ከቀጠለ አገራዊ ስሜት እና እውነተኛ ኢትዮጵያዊ ይገኛል ብሎ ማሰብ እጅግ ከባድ ይመስለኛል። ምክንያቱም ለእኛ አገራችንን ከእነ ሙሉ ክብሯ እና ከእነ ታሪኳ ያስረከቡን የደም መሰዋትዕነት ከፍለው ነው። 40ዎች ዓመታት በፊት የነበሩት መንግስታት ምንም እንኳ የራሳቸው ችግር ቢኖርባቸውም ለአገር አንድነትና እድገት፣ ለሰላምና መረጋጋት ከፍተኛ አስተዋጾ አድርገዋል። እንደ ህወሓት ፓርቲ አገሪቱን አልሸጡም፣ ይልቁንም ለክብሯና ለታሪኳ ይጨነቁ ነበር እንጂ። ህዝቦቻንም እንዲህ በይፋ ለስደት አልዳረጉም። አገርን የሚወድ ትውልድ እንጂ አገርን የሚክድና የሚሸጥ፣ ታሪክን የሚያጠፋ፣ አንድነትን የሚለያይ፣ ባህልን እና ሀይማኖትን የሚንቅ ትውልድ አላፈሩም። ው ነገር ግን መንግሥት ነኝ ባዩ ወያኔ/ኢህአዲግ የቀደሙ ነገሥታትን ሲተችና ታሪካቸውን ሲያጠፋ በይፋ ይታያል።

ወያኔ/ኢህአዲግ ግን ሙያዊ ነጻነት እንኳ ሳይቀር ተነፍገን ተመራማሪዎች እንዳይመራመሩ፣ ደራስያን እንዳይደርሱ፣ ተዋንያን እንዳይተውኑ፣ ጋዜጠኞች እንዳይዘግቡ፣ ነጋዴዎች እንዳይነግዱ(ከእርሱ አባላት በስተቀር) መምህራን እንዳያስተምሩ፣ እና ሁሉም በየሙያ ዘርፉ በነጻነት ሰርተው እንዳይበሉ አደረገ። ከእርሱ ዓላማ እና ተልእኮ ውጭ ማንም ምንም እንዳያደርግ የሞት፣ የእስር፣ የአክራሪነትና አሸባሪነት ህግ አጸደቀ። እስራትና ሞት ፈርተን ብዙዎች ተሰደድን ከስደት እንዳንመለስም ህይወት ናትና ፈራን።

ትናት ስደተኛ፣ ዛሬም ስደተኛ፣ ነገስ??? ነገ ምን አልባት ሙሴ ህዝበ እስራኤልን ከፈርኦን የመከራና የጭንቀት አገዛዝ ነጻ እንዳወጣቸው ሁሉ ኢትዮጵያውያንንም ነጻ የሚያወጣ ታምራዊ ኃይል ሊፈጠር እንደሚችል ባለሙሉ ተስፋዎች ነን። ህዝብ ታምራዊ የለውጥ ኃይል መሆን ይችላል። እያንዳንዱ ዜጋ ለመብቱ፣ ለነጻነቱ ከታገለ ታምራዊ ኃይል ሁኖ ይህን ጨቁኖ የሚገዛን መንግሥት በቀናት ውስጥ ማስወገድ ይችላል።

የኢትዮጵያ አምላክ ሆይ ከስደት የሚታደገንን ሙሴን ላክልን!

እውነተኛ ፍርድ የሚሰጠውን ዳዊትን ላክልን!

በጥበብና በማስተዋል የሚመራውን ሰሎሞንን ላክልን!