Monday, January 6, 2014

“እነሆ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኅን ተወልዶላችኋል” (ሉቃ.2፡11)


“ዘሎቱ ሰብአ ሰገል ሰገዱ ሎቱ፤ አማን መንክር ስብሐተ ልደቱ፤
ለእርሱ ሰብአ ሰገል የሰገዱለት፣ የልደቱ ክብር ድንቅ ነው።”

እግዚአብሔርን በእምነት ደስ ያሰኙ ቅዱሳን ከእስራኤላውያን ተነሥተው ነበር።(ዕብ.11) የአባቶች አለቃ ከሆነው ከአብርሃም ጀምሮ እስከ ጌታችን ሰው መሆን (ዘመነ ሥጋዌ) ድረስ ብዙ ታላላቅ አባቶችና እናቶች በእስራኤል ዘንድ ተገኝተዋል።

የእስራኤል ታሪክ ሁልጊዜ መልካም ታሪክ ብቻ ግን አይደለም፤ እግዚአብሔርን ያሳዘኑባቸው ጊዜያት ጥቂቶች አይደሉም። በዚህ ጊዜ በዙሪያቸው ባሉ ነገሥታት እየተማረኩ ወደ ፋርስ፣ ባቢሎንና ግብጽ እየወረዱ ለአሕዛብ የተገዙበትና የገበሩበት ጊዜም ነበር። ንስሐ ገብተው ወደ እግዚአብሔር ሲመለሱ ደግሞ እግዚአብሔር ከእነርሱ መካከል ሰው እያስነሣ ያድናቸው ነበር። ለአባቶቻቸው የገባውን የዘለዓለም ቃልኪዳን እያሰበ ይረዳቸውም ነበር። (መዝ.77 (78))
እነሆ በዚህ የታሪክ መስመር ውስጥ ወደር የሌለው፣ ሁለተኛ በዓለም ታሪክ የማይደገም ታላቅ ነገር ተከሰተ። የእግዚአብሔር ልጅ የሰውን ሥጋ ለብሶ እንደ ሰው በምድር ላይ ተገለጠ። ጥበበኛው ሰሎሞን “አበባ በምድራችን ታየ” ብሎ የተናገረው ትንቢት ተፈጸመ፤ አበባ ክርስቶስ ምድር በተባለ ሥጋችን ተገልጧልና(መኃ.2፥12)። የዓለም መድኃኒት እግዚአብሔርነቱን ሳይተው ሰው ሆነ። እነሆ የእግዚአብሔር ልጅ የአብርሃም ልጅ ተባለ፤ የዳዊት ጌታ የዳዊት ልጅ ተባለ። (ማቴ.1፥1) የዳዊት ፈጣሪ በዳዊት ከተማ በቤተልሔም በከብቶች በረት ተወለደ። አባቶቻቸው በአንድ ዘመን ዳዊት የነገሠባትን ከተማ ያፈረሱ፣ የዳዊትን ልጆች በባርነት የገዙ የፋርስና የአረብ ነገሥታት የዳዊትን መንግሥት ለዘለዓለም ለሚያጸናው ሕፃን ለኢየሱስ ክርስቶስ ሰገዱ፤ ተገዙ።

ልጁን ለእግዚአብሔር መስዋዕት አድርጎ ለማቅረብ እንኳ እንቢ ያላለውን፣ የአብርሃምን ልጆች ያስገበሩት የአሕዛብ ነገሥታት ዛሬ ለአብርሃም ልጅ ወርቅ፣ እጣን፣ ከርቤ ገበሩ። (ማቴ.1፥11) በበደለኞች እስራኤላውያን ልጆቻቸው ኃጢአት ምክንያት ዝቅ ዝቅ ያለው የእስራኤል ክብር ከእነርሱ ዘር ሥጋን በነሣው በኢየሱስ ክርስቶስ ለዘላለም ከፍ ከፍ አለ።

የክርስቶስ ሰው መሆን ግን ከእስራኤል ታሪክ ያለፈ የሰው ልጅ ሁሉ ደስታ ነው። እነሆ ሰው የመሆኑ ዜና የሰው ልጆችን ሁሉ ደስታ አሰኘ “እነሆ ለህዝቡ ሁሉ የሚሆንchristmas ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና።” የሚል ዜና በሰማያውያን መላእክት ተሰበከ። (ለቃ.2፥11) የምድር ኃያላን ነገሥታት በከብቶች በረት ውስጥ በጨርቅ ተጠቅልሎ ለተኛው ሕፃን መብዐ አቀረቡ። ንጹሐንና ኃያላን የሚሆኑ የሰማይ መላእክት እግዚአብሔር ለሰው ፍቅር ሲል እንደ ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግም ተኝቶ ሲያዩ በታላቅ ትሕትና ከእረኞች ጋር ዘመሩ። (ሉቃ.2፥13)

“ብርሃንህንና እውነትህን ላክ፤ እነርሱ ይምሩኝ፣ ወደ ቅድስናህ ተራራና ወደ ማደሪያህ ይውሰዱኝ።” ያለው የዳዊት ጸሎት መልስ አገኘ (መዝ. 42፥3)። ማንም ሊቀርበው በማይችል ዘለዓለማዊ ብርሃን ዉስጥ ከአባቱ እና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የሚኖር ብርሃን ወልድ ለጨለማው ዓለም ብርሃን ይሆን ዘንድ ተወለደ። ወደ ጽድቅ ፀሐይ ያደርሳቸው ዘንድ የእርሱ የሆነው ኮከብ ሰብአ ሰገልን ከምሥራቅ መራቸው። እነሆ ለዘለዓለም የሚያበራው ፀሐይ በቤተ ልሔም ወጣ። ነቢዩ ኢሳይያስ “በጨለማ የሄደ ሕዝብ ብርሃን አየ በሞት ጥላ አገርም ለኖሩ ብርሃን ወጣላቸው” ብሎ የተናገረው ትንቢት ተፈጸመ (ኢሳ.9፥2)። እርሱ የቅድስናው ተራራና ማደሪያው ወደ ሆነች ወደ መንግሥተ ሰማያት ይወስደናል፤ በዚች የዘለዓለም አገራችንም የሚያበራልን ፀሐይ እርሱ ነው(ራእይ.21፥23)።

በዳዊት ከተማ በቤተልሔም ድንቅ ነገር ተደረገ። ዳዊት በወርቅ ያጌጠ የተልባ እግር መጎናጸፊያ የለበሰባት ቤተልሔም የሰማይና የምድር ፈጣሪ በጨርቅ ተጠቅልሎ ተገኘባት። ቤተልሔም ከዳዊት ዘመን አብልጣ ከበረች፤ የእግዚአብሔር ክብር አብርቶባታልና፤ የልዑላን መላእክት ዝማሬ ተሰምቶባታልና።(ሚክ.5፥2)

Picture2“የእሥራኤል እረኛ ሆይ አድምጥ …በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ ተገለጥ” ብሎ የለመነው የዳዊት ልመና በእውነት ተፈጸመ።(መዝ.70(71)፥1) የእስራኤል እረኛ በእረኞች መካከል በከብቶች በረት ተወለደ። (ሉቃ.2፥7)እረኞች ለእረኛቸው ዘመሩ፤ ላሞችና በጎች በበረት የተኛውን ሕፃን በትንፋሻቸው አሟሟቁት። በኦሪት ድንኳን በሙሴ ሕግ መሠረት ለመስዋዕት ይቀርቡ የነበሩ እንስሳት በልደቱ ደስ ተሰኙ፤ የእነርሱን መሥዋዕት የሚያስቀር አማናዊው የእግዚአብሔር በግ ተወልዷልና።

ለሰው ሁሉ ብርሃን የሚሰጥ እግዚአብሔር በጨለማው ዓለማችን ተወለደ።(ዮሐ.1፥9-14) ነቢያትና መምህራን ጠፍተውባት፣ የኃጢአት ጨለማ ዉጧት፣ በድንቁርና ባሕር ውስጥ ሰጥማ በነበረችው የሰው ልጆች ዓለም የእውነት ፀሐይ ወጣ። እነሆ ይህን ይገልጥ ዘንድ መድኅን በእኩለ ሌሊት ተወለደ፤ በተወለደ ጊዜ ግን የእግዚአብሔር ክብር በዙርያው አበራ። (ሉቃ.2፥8-9)

ለመንግሥቱ ወርቅ ተገበረለት። ኃያል መንግሥቱን ግን በምድር ላይ በትሕትና ገለጠው፤ በከብቶች በረት በመወለድና በአህያ ውርንጭላ ተቀምጦ በመሄድ።Picture1 (ሉቃ.19፥28-38) የአባታችን የዳዊት መንግሥት ያለልክ ከፍ ከፍ አለች፤ እግዚአብሔር ሰው ሆኖ የዳዊት ልጅ ሆኗልና። ቅዱስ ገብርኤል ቅድስት ድንግል ማርያምን ባበሠራት ጊዜ “እርሱ ታላቅ ይሆናል፣ የልዑል ልጅም ይባላል፤ ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል፣ በያዕቆብ ቤትም ላይ ለዘለዓለም ይነግሣል፣ ለመንግሥቱም መጨረሻ የለዉም” ብሎ የተናገረው ዛሬ ተፈጸመ(ሉቃ.1፥32) በባሕርይው የፍጥረት ሁሉ ገዥ የሆነው የእግዚአብሔር ልጅ ከዳዊት ልጅ ሥጋን ነሥቶ ሰው በሆነ ጊዜ የአባቱን የዳዊትን ዙፋን እስከ ጽርአ አርያም ድረስ ከፍ ከፍ አደረጋት። እነሆ ንጉሥ ክርስቶስ በያዕቆብ ቤት(በምዕመናን) ላይ ለዘለዓለም ነገሠ። ለመንግሥቱ የአሕዛብ  ነገሥታት ተገዙላት፤ የእግዚአብሔር መንግሥት ናትና ፍጥረታት ሁሉ ይገዙላታል።(ኤር.23፥5)

ለክህነቱ እጣን ተሰጠው። ክህነቱም የአበውን እና የሌዋውያንን ክህነት የምትፈጽም የዘለዓለም ሰማያዊት ሥራው ናት። እነሆ የአብ ሊቀ ካህናት እርሱ የሰውን ባሕርይ ከራሱ ጋር አስማማ። ራሱ ካህን፣ ራሱ መስዋዕት፣ ራሱ ተቀባይ ሆኖ የፈጸማት የክህነት ሥራው የዘለዓለም ድኅነትን አስገኘች።

ለሞቱ ከርቤ ቀረበለት። እነሆ እግዚአብሔር ሰው የሆነበት ዋናው ምክንያት በሞቱ ሞትን ድል ለመንሣት ነውና በልደቱ ሞቱ ተሰበከ። ከርቤ ለሞቱ ሲቀርብለት የማይሞተው እርሱ ለሰው ልጆች ሲል የሚሞት ሥጋን እንደለበሰ ታወቀ።

የአሕዛብ ነገሥታት ወርቅ ገበሩለት፤ ምእመናን ደግሞ ጽሩይ፣ ንጹሕ፣ ሰማያዊ የሆነ ልቦናን እና እምነትን ለእርሱ እናቀርባለን። (1ኛ ጴጥ.1፥6) ሰብዐ ሰገል እርሱ የፈጠረውን ወርቅ ገበሩለት፤ እኛም በርሱ ጸጋና ሥራ ያገኘነውን ንጹሕና ሰማያዊ እምነታችንን እናቀርብለታለን።(ይሁ.3)

ነገሥታቱ ዕጣን ገበሩለት፤ ምእመናን ደግሞ ቂም በቀል የሌለበትን፣ ከመልካም እና ንጹሕ ልብ የሚወጣ የምስጋና ጸሎት እናቀርባለን፤ “ጸሎቴን በፊትህ እንደ ዕጣን ተቀበልልኝ፥ እጅ መንሣቴንም እንደ ሠርክ መስዋዕት ትሁን።” እንዳለ ንጉሥ ዳዊት።(መዝ.140፥2)

ስለሰው ልጆች ፍቅር ሲል ለሚቀበለው ሞት ከርቤ ገበሩለት፤ ምእመናን ደግሞ ለእግዚአብሔርና ለሰው ልጆች ያለንን ፍቅር ለእርሱ እናቀርባለን። ነገሥታቱ እርሱ ከፈጠረው ከርቤ ወስደው እጅ መንሻ አቀረቡ፤ ምእመናን ደግሞ ከእርሱ ከተማርነው፣ ከመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ከተቀበልነው ፍቅር መልሰን ለእርሱ እናቀርባለን። “እርሱ ስለኛ ነፍሱን አሳልፎ ሰጥቷልና በዚህ ፍቅርን አውቀናል፤ እኛም ስለ ወንድሞቻችን ነፍሳችንን አሳልፈን ልንሰጥ ይገባናል(1ኛ ዮሐ.3፥16)።”

ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክብር አሜን!!!

 ምንጭ፦ ማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ታኅሣሥ 27/2004 ዓ.ም

Tuesday, December 31, 2013

ታኅሳስ ፳፪ - ብስራተ ገብርኤል (“ትጸንሲ”)


በቤተ ክርስቲያናችን አስተምሮ መሰረት ታኅሣስ 22 መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እመቤታችንን ጌታን እንደምትፀን የአበሰረበት ቀን ነው።  
‹‹እንዘ ትፈትል ወርቀ ወሜላተ ወሪዳ ምድረ ቆላ ገብርኤል መጽአ እንዘ ይረውጽ በሰረገላ ክንፎ ክንፎ ክንፎ ጸለላ ተፈስሒ ተፈስሒ ለድንግል ይቤላ፤ ወደ ቆላው ምድር ወርዳ እመቤታችን ወርቅን ከሐር ጋር አስማምታ እየፈተለች ሳለች መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በሰረገላ እየሮጠ መጣ፣ ክንፉንም እያማታ እየሰገደ ድንግል ሆይ ደስ ይበልሽ አላት›› እንዲል ደራሲው አንድም “ተፈሥሒ ፍሥሒት ኦ ምልዕተ ጸጋ፤ ጸጋን የሞላብሽ ሆይ ደስ ይበልሽ” ሉቃ 1፡28 “ስብሃት ለኪ ማርያም እሙ ለፀሃየ ጽድቅ ለአብ ሙሽራው ለወልድ ወላዲቱ ለመንፈስ ቅዱስ ጽርሃ ቤቱ ተፈስሂ ደስ ይበልሽ” እንዳሉ አበው፡፡
እመቤታችን የብፅዓት ልጅ ናት። ሶስት ዓመት ሲሆናት አባት እናቷ ለካህን ሰጥተዋታል፤ ካህናትም በቤተ መቅደስ ከመካነ ደናግል አስገብተዋት ፲፪ ዓመት በቅዱስ ፋኑኤል አማካኝነት ኅብስት ሰማያዊ ጽዋዕ ሰማያዊ እየመጣላት ያን እየተመገበች መላእክት እየጎበኟት ኖራለች። ፲፭ ዓመት ሲሆናት ቅዱስ ገብርኤል ለእመቤታችን ጌታን እንደምትወልድ በዚህ ቀን ብስራቱን ነገራት። ውሃ ቀድታ ስትመለስ የጠተማ ውሻ እያለከለከ ሲመጣ በወርቅ ጫማዋ ለዛ ለተጠማው ውሻ ውሃ ስታጠጣ አብሯት የነበሩ ሴቶች ማድጋሽን አጎደልሺው፤ ቀድቼ እሞለዋለሁ እንዳትይ ጉድጓዱ ጥልቅ ነው መቅጃም የለሽም አሏት። “ውሃ የሚገኘው ከወደላይ ነው እንጂ ከወደታች ነውን ፍጥረቱን ያጠጣ ጌታ ይሞላልኛል” አለቻቸው። በተዓምራትም ሞልቶላታል። “በዚህ ዘመን አምላክ ከድንግል ይወለዳል ይላሉ ካንቺ ይሆን?” ብለው ዘበቱባት። ወዲያ ከወደኋላዋ ቅዱስ ገብርኤል መጥቶ “ትጸንሲ” አላት። ዞር ብትል አጣችው። አባቴ አዳምን እናቴ ሔዋንን ያሳተ ጠላት ይሆናል ብላ ሄደች።
ከቤት ደርሳ ማድጋዋን ስታስቀምጥ ዳግመኛ “ትጸንሲ” አላት። ይህ ነገር ደጋገመኝ እንዲህ ያለውን ነገር ቤተ መቅደስ ሄደው ሊረዱት ይገባል ብላ ወደ ቤተ መቅደስ ሄዳ በወርቅ ወንበሯ ተቀምጣ ከደናግለ እስራኤል ጋር የተካፈለችውን ወርቅና ሐር እያስማማች ስትፈት ቅዱስ ገብርኤል ተገልጾ “ተፈሥሂሒ ፍሥሒት ኦ ምልዕተ ጸጋ፤ መልአኩም ወደ እርስዋ ገብቶ። ደስ ይበልሽ፥ ጸጋ የሞላብሽ ሆይ፥ ጌታ ከአንቺ ጋር ነው፤ አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ አላት። እርስዋም ባየችው ጊዜ ከንግግሩ በጣም ደነገጠችና። ይህ እንዴት ያለ ሰላምታ ነው? ብላ አሰበች። መልአኩም እንዲህ አላት። ማርያም ሆይ፥ በእግዚአብሔር ፊት ጸጋ አግኝተሻልና አትፍሪ። እነሆም፥ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፥ ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ። እርሱ ታላቅ ይሆናል የልዑል ልጅም ይባላል፥ ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል፤ በያዕቆብ ቤትም ላይ ለዘለላም ይነግሣል፥ ለመንግሥቱም መጨረሻ የለውም። ማርያምም መልአኩን። ወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆናል? አለችው። መልአኩም መልሶ እንዲህ አላት። መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፥ የልዑልም ኃይል ይጸልልሻል ስለዚህ ደግሞ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል። እነሆም ዘመድሽ ኤልሳቤጥ፥ እርስዋ ደግሞ በእርጅናዋ ወንድ ልጅ ፀንሳለች፥ ለእርስዋም መካን ትባል ለነበረችው ይህ ስድስተኛ ወር ነው፤ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና። ማርያምም። እነሆኝ የጌታ ባሪያ እንደ ቃልህ ይሁንልኝ አለች። መልአኩም ከእርስዋ ሄደ።” ሉቃስ ፩፡፳፰-፴፰ እንዲል ወንጌል።
“ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በኃጢአት ፍትወት የተፀነስሽ አይደለም፤ በሕግ በሆነ ሩካቤ ከሐና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ፡፡(አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም)
አበው አባቶችና ሊቃውንተ ቤተ ክርስተቲያን እንሚያስረዱንና እንደሚያስተምሩን መልአኩ ብስራቱን የነገጋት መጋቢት 29 ቀን በዕለተ እሁድ ከቀኑ ሦስት ሰዓት ላይ ነው። ታዲያ ዛሬ ለምን እናከብረዋለን ለሚለው ጥያቄ፤ ምንጊዜም ወርሃ መጋቢት ታላቁ ዓቢይ ጾም የሚውልበት ወር ነው፤ በዚህ በዓቢይ ጾም ደግሞ ሐዘን፤ ለቅሶ፤ ጾም፤ ጸሎት እንጂ ደስታ፤ ፌሽታ እልልታ፤ ጭብጨባ የለም። ፍጹም የሐዘን ወራት ነው፤ ታቦት አውጥቶ በዓል ማክበርም ስህተት ነው። ፍትሃ ነገስት አንድምታ አንቀጽ 15 ተመልከት ፤ ታዲያ ቅዱሳን አባቶቻችን እንደዚህ ዓይነት ስርዓት ሰሩ፤ የመጋቢት 27 ስቅለቱን ጥቅምት 27 ቀን እንዲሁም የመጋቢት 5 አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ዕረፍት ቀን ወደ ጥቅምት 5 ቀን ዞሮ እንዲከበር አደረጉ፡፡ የመጋቢት 29 ብስራቱን ደግሞ ታህሳስ 22 ቀን ዞሮ እንዲከበር ያደረገው ታላቁ አባት የጥልጥልያ ኤጲስ ቆጶስ ደቅስዮስ ይባላል። ደቅሲዮስ በተጨማሪም የእመቤታችንን ተዓምራቶቿን የጻፉ ታላቅ አባት ነው። በእመቤታች ፍቅር ልቡ የነደደ ታላቅ ጻድቅም ነው። የእመቤታችንን ታአምራቷን የሚናገር መጽሐፍ የሰበሰበ አባት ነው፡፡ የጌታን ልደት ከመከበሩ አንድ ሳምንት ቀደም ብሎ ብስራቱ መከበር አለበት ብሎ ስርዓት ሰራ። አገሬውንም ሰብስቦ ታላቅ የደስታ በዓል አደረገ። እመቤታችን ተገለጸችለት ወዳጄ ደቅስዮስ ባንተ ደስ አለኝ። እንዳከበርከኝ እኔም አከብርሃለው አለችው። ሰማያዊ ልብስና ሰማያዊ ወንበር ሰጠችው ይህችን ልብስ ካንተ ሌላ ማንም አይለብሳትም፤ ይህችንም ወንበር ካንተ ሌላ ማንም አይቀመጥባትም አለችው። የዚህ ታላቅ አባት ዕረፍቱ ታህሳስ ፳፪ በዛሬዋ ቀን ነው። ከእርሱ በኋላ ሌላ ኤጲስ ቆጶስ ተሾመ ልብሱን እለብሳለው በወንበሩም እቀመጣለው አለ፤ ተው ይቅርብህ እመቤታችን እንዲህ ብላ ተናግራለች ይሉታል፤ እርሱም ሰው እኔም ሰው እርሱም ኤጲስ ቆጶስ እኔም ኤጲስ ቆጶስ ብሎ በትዕቢት ልብሱን ለበሰው። በወንበሩም ተቀመጠ ክፉኛ አወዳደቅ ወደቀ ሞተም። ይህን ያዩ እመቤታችንን በጣም ፈሯት ይላል ተዓምረ ማርያምን ተመልከት፡፡ ደቅስዮስ ሰርቶልን ያለፈውን ስርዓት ቤተክርስቲያን ተቀብላ ይኸው ዛሬም ድረስ ታከብረዋለች። በተለይም በመዲናችን አዲስ አበባ ብስራተ ገብርኤል ቤተክርስቲያን ታቦተ ህጉ ወጥቶ በደማቅ ተከብሮ ይውላል፡፡ 
ከእመቤታችን ከወላዲተ አምላክ እንዲሁም ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን፡ አሜን!

Sunday, December 29, 2013

ከሳውዲ አረቢያ በግፍ ተገፍተው ለተመለሱ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን ምን እየተደረገ ነው?

                                     ፎቶ፡ ምሳ ግብዣ በማኅበረ ቅዱሳን

የተለያዩ የዜና ምንጮች እንደገለጹት ከሳውዑዲ አረቢያ በግፍ ተገፍተው የተመለሱ ኢትዮጵያን ቁጥር ከመቶ በላይ ደርሰዋል። አሁን በዋናነት ማንሳት የፈለኩት ስለ ቁጥር መጠናቸው ትክክለኛነት፣ ያሳለፉትን ስቃይና መካራ፣ ማን በአስቸኳይ ደረሰላቸው ወይም በምን መልኩ ትውልድ ሀገራቸው ተመለሱ የሚለውን የትናት ገሀዳዊ እውነታ መተረክ ሳይሆን ለእነዚህ ወገኖቻችን ምን የተደረገላቸው ነው የሚለውን ቄ አዘል ሃሳቤን ለማካፈል ነው።
ለእነዚህ ለተጎዱ ወገኖቻችን በህብረትና በግል የውስጥ ሃዘናችንን በእንባ፣ በልቅሶ፣ በጩኸት የዓለም ጀሮ በቃኝ እስኪል ድረስ ገልጸናል፤ ተናግረናል፤ ጽፈናልም። መቼም ቢሆን ሀዘኑና ድርጊቱ ከልባችን አይጠፋም። ይህ በራሱ አንዱ የአንድነታችን መገለጫ ነው። ይህን አንድነታችንንና ሃዘናችንን ወደ ተግባር ቀይረን ማሳየት ብንችል የበለጠ ለእኛ ለህሌናችን ውስጣዊ እርካታ፤ ለተጎዱ ወገኖቻችን ደግሞ መጠገኛ/መቋቋሚያ ይሆናቸዋል።
በእርግጥ ድርጊቱ ከተፈጸበት ጊዜ ጀምሮ በተለያየ መልኩ ከግለሰብ እስከ ተለያዩ ማህበራት ድረስ እርዳታ ለመስጠት ጥረት እያደረጉ ይገኛሉ። ይህ ጥረት ግን ተግባራዊ ይሆን ዘንድ ሁላችንም ልዩ ትኩረት ልንሰጥበት የሚገባ ተግባር ነው። እንዴትና በምን መልኩ ለወገኖቻችን ልንደርስላቸው እንደ ሚገባ ግልጽ ታማኒነት ባለው መልኩ እንቅስቃሴያችንን ማስኬድ ይኖርብናል። ለዚህ ተግባር ግልጽነትና አንድነት ባራዊ የሆነ ሥራ ለመስራት በእጅጉ ያስፈልጉናል።

  ሀ. አንድነት፦ ለዚህ በጎ ተግባር ድጋፍ ለማድረግ ሰው መሆን ብቻ በራሱ በቂ ነው። ችግሩን በትክክል ለተገነዘበ ሰው ሌላ የተለየ ቅስቀሳ አያስፈልገውም በተለይ ደግሞ  በውጭው ዓለም ያለ ሰው በአንድም በሌላም የችግሩ አካል በመሆኑ ለዚህ ተግባር ግንባር ቀደም ድጋ ሰጭ እንደሚሆን እርግጠኛ ሁኖ መናገር ይቻላል። አስተባባሪ አካላት ግን መንግስት፣ ተቃዋሚ፣ ጾታ፣ ብሄር፣ ሃይማኖት፣ ድርጅት፣ ማህበር የውጭ የውስጥ ብሎ ልዩነት ሳይፈጥሩ አንድማስተባበር ከቻሉ በቀላሉ ተጎጅዎችን ማቋቋም የሚቻልበትን መስመር መዘርጋት ይቻላል።  ይህ ችግር ሃገራዊ እንጂ የአንዱን ቡድን ብቻ መለከ አይደለም። ቢሆንም እንኳ ከጠባብነት የአስተሳሰብ ጎራ ተላቀን ለዚህ በጎ ተግባር አንድነት መፍጠር ይኖርብናል። ይህን ችግር ምክንያት አድርጎ ፖለቲካዊም ሆነ ሌላ የተለየ ጥቅም ለማግኘት መሞከር ሰባዊ ት ወደ እንስሳዊነት ባህሪ የመቀየርን ያክል አሳፋሪ ይሆናል  ስለዚህ ሁላችንም በተለይ አስተባባሪ አካላት በመካከላችን የቱንም ያህል ልዩነት ቢኖርም ለዚህ አንገብጋቢ ተግባር ከማነኛውም ሰው ጋር በቅንጅት ድጋፍ ለማድረግ መወሰን እና መስራት ይኖርብናል። 
  ለ. ግልጽነት፦ በዚህ በአለንበት ዘመን የቱንም ሥራ ለመስራት ግልጽነት ያስፈልጋል። ግልጽት የጎደላቸው ተግባሮች ሁሉ ውጤታቸው እዚህ ግባ የባይባል ነው። ለዚህ በጎ ተግባር ገንዘብ ከመሰብሰብ ጀምሮ እንዴትና በምን መልኩ ለተቸገሩ ወገኖቻችን ሊደርሳቸውና ምን አይነት ድጋፍ ሊደረግላቸው እንደታሰበ በግልጽ ለእኛንዳንዱ ህብረተሰብ ር ያስፈልጋል ግልጽ መሆናችን 3 ጥቅሞች አሉት። አንድ ድጋፍ የሚሰጡ ሁሉ ራቻከጥርጣሬ እና ከሌላ እይታ አልፈው የተቻላቸውን ያክል ድጋፋቸውን እንዲሰጡ ያደርጋል። ሁለት ለአስተባባሪዎችም ሆነ ገንዘብ ለሚሰበስቡት ሁሉ ታማኝነት ያገኛሉ። ነጻ ሁነው ማንኛውንም ሰው ለዚህ ድጋፍ ተባባሪ እንዲሆን መጠየቅ ይችላሉ። ሦስት ድጋፍ የሚደረግላቸው ወገኖች የበለጠ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ያስችላቸዋል። ምክንያቱም በግልጽነት የምንሰበስበው የገንዘብ መጠን የተሻለ እና የታሰበውን ፕሮጀክት መሸፈን የሚችል በቂ ገንዘብ መሰብሰብ ስለሚቻል ነው። ግልጽነትን ካለምክንያት አላነሳሁትም ለዚህ ድጋፍ ተብሎ ር ውስጥም ሆነ በውጭው ዓለም የተለያዩ ተቋማትና ግለዘቦች ገንዘብ ለመሰብሰብ በመቀሳቀላይ ናቸው። እየሰበሰቡ ያሉም አሉ ነገር ግን ገንዘብ ከመሰብሰብ ውጭ እንዴት፣ በምን መልኩ እና ግንኙነቱ ከማን ጋር የሚሉ መሰረታዊ ጥያቂዎችን በግልጽ ለማወቅ አልተቻለም። ስለዚህ ለእነዚህ እና ለመሳሰሉት ጥያቄዎች ግልጽነታችን በጣም አስፈላጊ ስለሚሆን እያንዳንዷን እንቅስቃሴ በግልጽነት ማካሄድ ትን መስመር ዘርግቶ መንቀሳቀስ ከምንም በላይ ትኩረት ልንሰጥበት የሚገባ ተግባር ነው።

ከላይ ያነሳኋቸውን መሰረታዊ ነገሮች አንድትን እና ግልጽነትን ሰንቀን ድጋፋችን ዘላቂነት እንዲኖረው ኃላፊነቱን ደረጃ በደረጃ መውሰድ ይኖርብናል።
1.      መንግሥት፦  ምንም እንኳ አስተዳደራዊም ሆነ ሌሎች ዘርፈ ብዙ ችግሮች በአገሪቱ ውስጥ ቢሰፍኑም ለዚህ ችግር ግንባር ቀደም መፍትሄ ሊሰጥ የሚገባው አካል መንግሥት ነው። ይህን ማድረግ አልነበረበትም? የችግሩ መንስኤ መንግሥት ራሱ ነው? እና ሌሎችንም ጥያቄዎች በትችት መልክ ሁልጊዜ ማንሳቱ ለውጥ ሊያመጣልን አልቻለም። በእርግጥ በተለያየ መልኩ አቅጣጫ የሚያሳዩ ኢትዮጵያውያዊ ሙህራን በርካታ ናቸው። ምናልባት አብዛኞቹ ከትችት ስለሚጀምሩ ሃሳባቸውን ላለመቀበል ምክንያት ሊሆን ይችል ይሆናል። ሆኖም ግን ጠቃሚ ሃሳቦችን መውሰድ ደግሞ ብልህነት ነው።
መንግሥት እንደ መንግሥት ካሰበ በግፍ ወደ ሃገራቸው ለተመለሱ ወገኖች ዘላቂነት ባለው መልኩ ድጋፍ ሊያደርግላቸው ይገባል። በአጭሩ ሦስት ተግባራትን መከተል ቢቻል ዘላቂነት ያለው ድጋፍ ማድረግ ይችላል።
Ø  ወደ አገር የተመለሱትን ስም ዝርዝርና በቀላሉ ሊገኙ የሚችሉበትን አድራሻ መያዝና ስለ እያንዳንዱ በቂ መረጃ መሰብሰብ(የት/ት ደረጃ፣ የሥራ መስክ፣ የቤተሰብ ሁኔታ፣ ፍላጎት)። ከምንም አድሎአዊነት ነጻ ሁኖ በትክክል እርዳታ የሚያስፈልጋቸውን ማወቅና መለየት።
Ø   በሰበሰብነው መረጃ መሰረት ሁሉን ሊያካትት የሚችልና ዘላቂ ፕሮጀክት መቅረጽ። ለምሳሌ፦ ለውጭ ባለ ሃብቶች የምንሰጠውን መሬት ማለትም የእንስሳት ልማት፣ የአበባ ልማት፣ እና የተለያዩ የንግድ ሥራወችን  ዘመናዊ በሆነ መልኩ ሊሰሩ የሚችሉበትን እድል ማመቻቸት። እንዲሁም መማር ለሚፈልጉ ነጻ የትምህርት እድል መስጠት።
Ø    ፕሮጀክቱ ዘላቂነት እንዲኖረው እና ትርፋማ ሁኖ በትክክል ለተፈለገው ዓላማ እንዲውል የባለሙያ ድጋፍና ክትትል እንዲያገኝ ማድረግ። 

2.   ማህበራትና ተቋማት፦ ሊታይና ሊቆጠር የሚችል ፕሮጀክት ቀርጾ ገንዘብ መሰብሰብ። ፕሮጀክቱ የት፣ ለእነማንና በምን መልኩ ሊተገበር እንደሚችል ይፋ ማድረግና ገንዘብ ሊገኝ ከሚችልባቸው የመንግሥትም ሆነ የግል ድርጅቶች፤ ከውጭም ሆነ ከአገር ውስጥ መሰብሰብ። ለዚህ ተግባር ይመለከታቸዋል ከምንላቸው ድርጅቶች ጋር በቅንጅት መስራት ድጋፋችንን ዘላቂነት እንዲኖረው ያደርግልናል።
በተለይ በውጭው ዓለም ገንዘብ ከመሰብሰብ ጀምሮ የተለያዩ ድጋፎችን ለማድረግ በተለያየ መልኩ እንቅስቃሴዎች ተጀምረዋል። ይህን እንቅስቃሴ ተግባራዊ ለማድረግ አገር ውስጥ ከአሉ ድርጅቶች ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ማድረግ እና በውጭ በተለያዩ  ችግሮች ውስጥ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ዘላቂነት ባለው መንገድ የሰባዊ መብት ጥሰትን ማስቆም የሚቻልበትን ሁኔታ ማመቻቸት ትልቅ ተግባርና ሃላፊነት ነው።

3.   ባለሙያዎች፦ ለዚህ በጎ ተግባር ዘላቂነት ያለው ፕሮጀክት ከመቅረጽ ጀምሮ ሙያዊ ድጋፍ ለማድረግ በራስ ተነሳሽነት ለሚመለከታቸው አካላት ሃሳባችንን ማካፈል። ሁሉም የሙያ ዘርፍ በተለያየ መልኩ ስለሚያስፈልግ እኔ አላስፈልግም ሳንል ለወገኖቻችን ድጋፍ መስጠት ከቻለን በቀላሉ ለችግሩ መፍትሔ ማግኘት የሚቻልበትን አማራጮች ማስቀመጥ ይቻላል።

በአጠቃላይ በግፍ ወደ ሃገራቸው ለተመለሱትም ሆነ በዓለም ላይ ኢ_ሰባዊ ድርጊት የሚፈጸምባቸውን ኢትዮጵያውያንን ለመታደግ የእያንዳንዳችን ድርሻ ወሳኝ መሆኑን ተረድተን ዜጋዊ ኃላፊነታችንን መወጣት ይኖርብናል። የገንዘብ ድጋፍ ከማድረግ ባለፈ መረጃ ከመስጠት ጀምሮ ኢ_ሰባዊ ድርጊቶችን ማስቆም የሚቻልበትን መንገድ ማመቻቸት ጊዜ የማይሰጠው ተግባር መሆን ይኖርበታል የሚል ጽዕኑ እምነት አለኝ። ኮሚቴ ማቋቋም ብቻ ትርጉም የለውም። እንዲህ ሰሩ ለመባል ሳይሆን ተግባራዊ ስራ ሰርተን አገራዊ ኃላፊነታችንን እንወጣ።   


Saturday, December 7, 2013

ኔልሰን ማንዴላ

ይህንን ፎቶ ሳነሳ ሁለት አይነት ስሜት ተሰማኝ። የመጀመርያው የኩራት፣የደስታ ስሜት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ የሃዘን ስሜት ተሰማኝ። ብዙ አፍሪካውያን በዓለም በበርካታ ስራዎች የሚታወቁ ሰዎች እንዳሉ ቢታወቅም እንደ ኔልሰን ማንዴላ ግን በመሪነት ደረጃ ለአለም ምሳሌና አርያ የሆነ የለም። በዚያ ላይ ከብዙ ስቃይና መከራ ፣ እንግልትና እስር በኋላ የሰላም፣ የነጻነት፣ የአንድነት፣ የይቅርታ አባት መሆን በእጅጉ ታላቅነት ነው። የበደሉትን፣ያሰቃዩትን፣ አንተ ጥቁር ሰው አይደለህም ከነጮች ጋር አብረህ ልትኖር፣ ልትማር ፣ በአንድ ባስ ውስጥ ልትጓዝ አይገባይህም ብለው አዋጅ አውጀው በመላ ጥቁር ደቡብ አፍርካውያን ላይ ከባድ ወንጀል የፈጸሙትን ለሰላምና ለአንድነት ሲል በይቅርታ እንዲታለፉ ያደረገ ታላቅ የይቅርታ አባት መሆኑን ዓለም ሁሉ በአንድ አፍ ሲመሰክር ሳይ በባዕድ አገር የደስታ ስሜት ተሰማኝ።

በተቃራኒው ደግሞ ይህን ታላቅ ሰው እርጅና የሚሉት በሽታ፣ ሞት የሚሉት ለሰው ልጅ አይቀሬ እጣ ፈንታ ሲነጥቀን ያለ ቢሆንም ሐዘን ተሰማኝ፡፡ በይበልጥ ግን ዓልም ይቅርባይነት ጠፍቶባት፣ መቻቻል አቅቷት፣የበቀልና የጥላቻ መንፈስ ነግሶባት እያየ ታላቁ ማንዴላ አንድ ሰው እንኳ ሳይተካ ማለፉን ሳስብ ደግሞ ሐዘኔ ይበልጥ በረታ። ግን እኮ ማንዴላ ፍቅርን፣ ይቅርባይነትን፣ መቻቻልን፣ የውይይት/ድርድር ልምድን በተግባር አሳይቶናል። እኛ እንዴት ከእሱ መማር አቃተን? ምነው ለይቅርታ ዘገየን? ምነው ለበቀል ቸኮልን?
ታላቁን የሰላም አባት ማንዴላን ለማስታወስ በኖርዎይ ኦስሎ ዩኒቨርስቲ ብሊንደር ላይበራሪ መግቢያ በር ላይ በትልቅ ጠረጴዛ የእርሱ ፎቶና ስለ እርሱ የተጻፉ መጻሕፍት ከተቀመጠበት በ06/12/2013 እኤአ ያነሳኋቸው ፎቶዎች ናቸው።


Wednesday, December 4, 2013

ሰንደቅ ዓላማ

ከከበደ ሚካኤል (ታሪክና ምሳሌ ፩ኛ መጽሐፍ የተወሰደ)
ሰንደቅ ዓላማ የነጻነት ምልክት፣ የአንድ ህዝብ ማተብ፣ የኅብረት ማሰርያ ጥብቅ ሐረግ ነው።
              "ተመልከት ዓላማህን፤ ተከተል አለቃህን"
ነጋሪቱ እየተጎሰመ፣ ሠራዊቱ እየተመመ ሲሄድ ሰንደቅ ዓለማ ትምህርተ ኃይል፣ ትምህርተ መዊዕ ነው።
ሰንደቅ ዓላማችን አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ ሦስት ቀለማትን ይዟል። ምሳሌአቸውም አረንጓዴው ተስፋ፣ ልምላሜ ሃብት፤ ቢጫው ሀይማኖት፣ አበባና ፍሬ፤ ቀዩ ፍቅር፣ መሥዋዕትነትና ጀግንነት ነው።

Saturday, November 30, 2013

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ታቦተ ጽዮን

                                                    በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

እግዚአብሔር አምላክ ሕዝበ እስራኤልን ከግብጽ ባርነት ካወጣቸው በኋላ የአምልኮ ሥርዐታትን ይፈጽሙበት ዘንድ የምስክሩን ድንኳን፣ የቃል ኪዳኗ ታቦትንና ለአምልኮ ሥርዐቱ ማከናወኛ የሚያገለግሉ ልዩ ልዩ ንዋያተ ቅድሳትን እንዲሠሩ በሙሴ በኩል ታዘው ነበር፡፡ ከቃል ኪዳኗ ታቦት ውስጥም በእግዚአብሔር ጣት ዐሥርቱ ትእዛዛት የተጻፉበት የሕጉ ጽላት፣ አርባ ዓመት ሙሉ እስራኤላውያን በሲና ምድረ በዳ የተመገቡትን መና የያዘች መሶበ-ወርቅ፣ አሮን ለክህነት አገልግሎት ስለመመረጡ ምስክር የሆነችው ለምልማና ፍሬ አፍርታ የተገኘችው የአሮን በትር ይገኙባታል፡፡(ዕብ.9፡4)
ታቦተ ጽዮን በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትመሰላለች፡፡ ይህን ለመረዳት ግን ስለ ታቦተ ጽዮን አሠራርና መንፈሳዊ ትርጉም አስቀድመን ልንረዳ ይገባናል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ታቦተ ጽዮንን እንዲሠራ ብልሃትን፣ ጥበብን፣ ማስተዋልን፣ ዕውቀትን ይለይ ዘንድ መንፈሱን ያሳደረበትን ከይሁዳ ወገን የሆነውን ባስልኤልን መረጠ ፡፡(ዘፀ.25፡9) እርሱም እግዚአብሔር በሰጠው ማስተዋል ከማይነቅዝ እንጨት ርዝመቷ ሁለት ክንድ ተኩል፤ ወርዱዋም አንድ ክንድ ተኩል፣ ቁመቷም አንድ ክንድ ተኩል እንዲኖራት አድርጎ ታቦቷን ሠራት፡፡ በመቀጠል በውስጥም በውጪም በጥሩ ወርቅ ለበጣት፣ ከታቦቷም ዙሪያ የወርቅ አክሊልን አደረገላት፡፡ ካህናት ታቦተ ጽዮንን ለመሸከም እንዲረዳቸውም በአራቱም መዓዘናት በወርቅ የተሠሩ ቀለበቶችንና በእነርሱም ውስጥ የሚገቡ ሁለት መሎጊያዎችን ሠራ፡፡ ከጥሩ ወርቅም የስርየት መክደኛውን በቃል ኪዳን ታቦቷ ላይ በርዝመቷና በወርደዋ ልክ ሠራ፡፡ የስርየት መክደኛውን እንዲጋርዱት አድርጎም ጥሩ ከሆነ ከተቀጠቀጠ ወርቅ ኪሩቤልን ሠራ፤ በስርየት መክደኛው ግራና ቀኝም አደረጋቸው፡፡ እነዚህ በጥሩ ወርቅ የተሠሩት ሁለቱ ኪሩቤል ፊታቸው ወደ ስርየት መክደኛው ሆኖ እርስ በእርሳቸው የሚተያዩ ተደርገው የተሠሩ ናቸው ፡፡ በዚህ በስርየት መክደኛው በሁለቱ ኪሩቤል መካከል እግዚአብሔር ለሙሴ በመገለጥ ሰው ከባልንጀራው እንደሚነጋገር ያነጋግረው ነበር፤ ለሕዝቡ በደመና አምድ ይታያቸው ነበር፡፡(ዘፀ.25፡22፤33፡8-11)
ወደ ትርጓሜው ስንመጣ ታቦተ ጽዮን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ስትሆን፣ በውስጡዋ የያዘችው የሕጉ ጽላት የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ታቦቷ ከማይነቅዝ እንጨት መሠራቷ የጌታን እናት ንጽሕናን የሚያመለክት ሲሆን በውጪም በውስጧም በጥሩ ወርቅ መለበጡዋ የቅድስናዋና ድንግል በሕሊና ወድንግል በሥጋ መሆኗን የሚያስረዳን ነው፡፡ ታቦቷን አራት ሌዋውያን ካህናት ይሸከሟት ዘንድ በግራና በቀን በተዘጋጁ አራት ከወርቅ የተሠሩ ቀለበቶች ሲኖሩአት፤ በነዚያ የወርቅ ቀለበቶች ውስጥ ሁለት መሎጊያዎች ይገቡባቸዋል፡፡ ታቦተ ጽዮንን ለማንቀሳቀስ ሲፈለግ አራት ካህናት በመሎጊያዎቹ ይሸከሟታል፡፡ይህ ሥርዐት በሰማያትም የሚታይ እውነታ ነው፡፡ የጌታን መንበር ገጸ ንሥር፣ ገጸ ሰብእ፣ ገጸ ላህም፣ ገጸ አንበሳ ያላቸው አርባዕቱ እንስሳት ይሸከሙታል፡፡(ኢሳ.6፡1-5፤ ሕዝ.1፡1-16) እንዲሁም ለአማናዊቷ ታቦት ቅድስት ድንግል ማርያም “የምስራች የሚናገሩ፣ ሰላምንም የሚያወሩ፣ የመልካምንም ወሬ፣ መድኃኒትንም የሚያወሩ፣ ጽዮንንም አምላክሽ ነግሦአል የሚሉ እግሮቻቸው በተራሮች ላይ እጅግ ያማሩ ናቸው” የተባለላቸው የእርሱዋንና የጌታችን ስም ተሸክመው የሚሰብኩ ወንጌላውያን አሏት፡፡(ኢሳ.52፡7)የስርየት መክደኛው ታቹ መቀመጫው ንጹሐን አንስት ላዩ መክደኛው የንጹሐን አበው ግራና ቀኙ የወላጆቹዋ የሐናና የኢያቄም ምሳሌ ነው፡፡ እርሱን በክንፎቻቸው የጋረዱት ኪሩቤል የጠባቂ መልአክ ቅዱስ ሚካኤልና የአብሣሪው መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ምሳሌዎች ናቸው፡፡

የስርየት መክደኛው ስርየቱ የሚፈጸምበት ስፍራ ነው፡፡ ነገር ግን እውነታውን ስንመለከት በዚህ ቦታ ምንም ዓይነት መሥዋዕት ሲቀርብ እንዳልነበር እንረዳለን፡፡ ይህም በጊዜው አማናዊው መሥዋዕት ገና እንዳልተሠዋ ያስገነዝበናል፡፡ ይህ ስፍራ እግዚአብሔር ለሙሴ የሚገለጥበት ቦታ ነው፤ ከእርሱ ውጪ ሌላ ነገር በእዚያ ላይ ማረፍ የለበትም፡፡ ይህ በራሱ የሚሰጠን አንድ ማስተዋል አለ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለአዳም የገባውን ቃል ኪዳን ሊፈጽም ሰው በሆነ ጊዜ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ የሚያቀርብበት ልዩ ስፍራ እንዳለ ያመላክተናል፡፡ ስለዚህም ይህ ስፍራ ለዚህ እንደተጠበቀ ወይም በዚህ ምሳሌ አማናዊ መሥዋዕት የሚቀርብበት ሥፍራ እንደሚያስፈልግ የሚያሳስብ ነው፡፡ ይህ እንደሆነ ለማመልከት ሲባል ለኃጢአት የቀረበው መሥዋዕት ከታረደ በኋላ ካህኑ ደሙን በጣቱ በመንከር ሰባት ጊዜ በስርየት መክደኛው አንጻር በመገናኛ ድንኳን ውስጥ ይረጨው ነበር፡፡(ዘሌዋ.4፡6) ነገር ግን ይህ ደም ከዚያ ስርየት መክደኛው ላይ አያርፍም ነበር ምክንያቱም በዚህ ስፍራ መቅረብ ያለበት መሥዋዕት መለኮት የተዋሐደው ነፍስ ግን የተለየው የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ክቡር ሥጋውና ቅዱስ ደሙ ነውና፡፡

ይህ የስርየት መክደኛ ሌላም ለእኛ የሚያስተላለፈው መልእክት አለው፡፡ መልእክቱም አማናዊው መሥዋዕት መቅረቡ እንደማይቀርና፣ መሥዋዕቱ የሚቀርብበት ስፍራ በቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ ሆኖ እግዚአብሔር በምህረት በሚገለጥበት በጸጋ ዙፋኑ በጽላቱ ላይ መሆን እንዳለበት ነው፡፡(ዕብ.4፡16) በዚህም እግዚአብሔር አምላክ በነቢዩ ሚልክያስ “ከፀሐይ መውጫ ጀምሮ እስከ መግቢያዋ ድረስ ስሜ በአሕዛብ ዘንድ ታላቅ ይሆናልና በየስፍራውም ስለስሜ ዕጣንን ያጥናሉ ንጹሕም ቁርባን ያቀርባሉ”(ሚል.1፡11) እንዳለው የስርየት መክደኛው በዓለም ዙሪያ ላለችው አንዲት ቅድስት ቤተክርስቲያን ምሥጢረ ቁርባንን ለምትፈጽምበት ጽላት ወይም ታቦት ምሳሌ መሆኑን ያሳየናል፡፡ በሐዲስ ኪዳን ጽላቱ(ታቦቱ) የሚያርፍበት ስፍራ መንበር ተብሎ ሲጠራ የእግዚአብሔር ስም የተጻፈበትና ቅዱስ ሥጋው ክቡር ደሙ የሚፈተትበት ደግሞ ጽላት ወይም ታቦት ወይም መሠዊያ ተብሎ ይጠራል፡፡

የስርየት መክደኛው በታቦቱ አናት ላይ መሆኑም ቅዱስ ኤፍሬም “ የእኛን ሥጋ ለነሣኸውና ፣ መልሰህ ለእኛ ለሰጠኸን ፣ ለአንተ ክብር ምስጋና ይሁን ፡፡ ከእኛ በሆነው ሥጋህ በኩል እጅግ የበዛውን የአንተን ስጦታ ተቀበልን፡፡” ብሎ እንዳመሰገነ፤ እግዚአብሔር ቃል ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ማቅረቡን ያሳየናል፡፡ የስርየት መክደኛውን የሚጋርዱት በጥሩ ወርቅ የተሠሩት የኪሩቤል ምስሎችም አማናዊው መሥዋዕት በሚሠዋበት ጊዜ በዙሪያው ረበው የሚገኙ የመላእክት ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ይህን ለማስገንዘብ ቅድስት ቤተክርስቲያናችን በመንበረ ታቦቱ ላይ ምስለ ፍቁር ወልዳ እንዲቀመጥ ታዝዛለች፡፡ ምስለ ፍቁር ወልዳን ላስተዋለ ሰው በትክክል የታቦተ ጽዮንን መንፈሳዊ ትርጉምን ይረዳል፡፡

ይህን ድንቅ የሆነ መንፈሳዊ ትርጉምን ይበልጥ ለመረዳት አንድ ምሳሌ የሚሆነንን እውነታ እንመልከት፡፡ ንጉሥ ዳዊት የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳኑ ታቦት ከአቢዳር ቤት ወደ ጽዮን ከተማ ባስመጣበት ጊዜ በታቦተ ጽዮን ፊት ለእግዚአብሔር በሙሉ ኃይሉ በደስታ እየዘለለ መንፈሳዊ መዝሙርን አቅርቦ ነበር ፡፡(2ሳሙ.6፡12-17) ይህን ዓይነት ተመሳሳይ ድርጊት በሐዲስ ኪዳንም ተፈጽሞል ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቅድስት ኤልሳቤጥን በተሳለመቻት ጊዜ የስድስት ወር ፅንስ የነበረው ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ የጌታችንን እናት የሰላምታ ድምፅ በሰማ ጊዜ እንደ አባቱ እንደ ዳዊት ከእናቱ ማኅፀን ውስጥ ሳለ በደስታ ዘሎአል(ሰግዶአል)፡፡ (ሉቃ.1፡44) ቅዱስ ዳዊት በታቦተ ጽዮን ፊት እንዲያ ደስ መሰኘቱና ለአምላኩ የምስጋና ቅኔን መቀኘቱ ለሰው ልጆች ሁሉ የመዳናቸው ምክንያት የሆነችውን ቅድስት ድንግል ማርያምንና ልጁዋን ኢየሱስ ክርስቶስን በታቦተ ጽዮን በኩል በማየቱ ነበር፡፡

ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን አባቶችም ይህንን እውነታ ይጋሩታል ፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ኤፍሬም፡- “ከአዳም ጎን በተገኘችው አንዲት አጥንት ምክንያት ሰይጣን ከአዳም ማስተዋልን አራቀ፡፡ ነገር ግን ከእርሱ አብራክ በተገኘችው በቅድስት ድንግል ማርያም ምክንያት በእርሱ ላይ ሠልጥኖ የነበረው ሰይጣን እንደ ዳጎን ተሰባብሮ ወደቀ፡፡ ታቦተ ጽዮን በተባለችው በቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ውስጥ ባደረው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የድል አዋጅ ታወጀ ፡፡ በቃል ኪዳኑዋ ታቦት ሥር ዳጎን ተሰባብሮ እንደተገኘ እንዲሁ ክፉው ሰይጣን በታመኑበት ፊት ድል ተነሳ፡፡ እግዚአብሔር በቃል ኪዳኗ ታቦት ኃይሉን በመግለጥ ዳጎንን ሰባብሮ እንደጣለው እንዲሁ እግዚአብሔር ቃል ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ በመወለድ በኃጢአት ምክንያት በእኛ ላይ ሠልጥኖ የነበረውን ሰይጣንን ድል ነሳው፡፡” (1ሳሙ.5፤6) ሲል ቅዱስ ጀሮም ደግሞ “ቅድስት ድንግል ማርያም ቅድስትና ንጽሕት ነበረች፡፡ በቃል ኪዳኗ ታቦት ውስጥ የሕጉ ጽላት ብቻ እንደነበር እንዲሁ እርሷም በሕሊናዋ ከእግዚአብሔር ሕግጋት ውጪ ሌላ ምንም ሃሳብ አልነበራትም፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም በውስጥም በውጪም ነውር የሌለባት ንጽሕት ናት፡፡ እንደ ቃል ኪዳኗ ታቦት በውጪም በውስጥም በቅድስና የተጌጠችና ሕጉንም ጠብቃ የተገኘች የክርስቶስ ሙሽራ ናት ፡፡ በቃል ኪዳን ታቦቱ ውስጥ ከሕጉ ፅላት ውጪ ሌላ ምንም ነገር እንደሌለ እንዲሁ አንቺም ቅድስት ሆይ በሕሊናሽ ምንም ነውር የሌለብሽ ቅድስት ነሽ፡፡” ብሎ ሲያመሰግናት፤ የእስክንድርያው ዲዮናስዮስ ደግሞ “ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ካህን ይሆን ዘንድ በሰው እንዳልተመረጠ እንዲሁ ቅድስት ድንግል ማርያም የጌታ ማደሪያ ትሆን ዘንድ በእግዚአብሔር የተመረጠችና በመንፈስ ቅዱስ ለእርሱ ማደሪያነት የተዘጋጀች ናት፡፡ የመለኮት ማደሪያ ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር የከተመባት ከተማ ሆና ትኖር ዘንድ ለዘለዓለም በእግዚአብሔር ታትማለች” በማለት ስለእርሱዋ ይመሰክራል፡፡

አዳም ድኅነቱ ከሴት ወገን በሆነች በቅድስት ድንግል ማርያም በኩል እንደሆነ ተረድቶ ለሚስቱ “ሔዋን” ብሎ ስም እንደሰጣት እንዲሁ ንጉሥ ዳዊት በቅድስት ድንግል ማርያም በኩል እንደሚድን በመረዳቱ አምባዬና መጠጊያዬ ነሽ ሲላት “ጽዮን” ብሎ ለድንግል ስያሜን እንደሰጣት በመዝሙራቱ ማስተዋል እንችላለን፡፡ጽዮን የንጉሥ ዳዊት ተራራማዋ ከተማ ስትሆን፣ የስሟ ትርጓሜ አምባ፣ መጠጊያ ማለት ነው፡፡ ይህን ይዘው ብዙዎች ነቢያት ስለድንግል ሲናገሩ ጽዮን የሚለውን ስም ተጠቅመዋል፡፡

ነቢያት ስለቅድስት ድንግል ማርያም ሲናገሩ ጽዮን የሚለውን ስም እንደሚጠቀሙ ወደ ብሉይ ኪዳን ሳንገባ በሐዲስ ኪዳን ብቻ ስለ ጽዮን የተጻፉትን በማንሣት ማረጋገጥ እንችላለን፡፡ ለምሳሌ ነቢዩ ኢሳይያስ ከአይሁድ ወገን የሆኑ የራሳቸውን ሥርዐትና ሕግ ለማቆም ሲሉ በክርስቶስ ከማመን ስለተመለሱት ሲጽፍ፡- “እነሆ በጽዮን የእንቅፋት ድንጋይና የማሰናከያ አለት አኖራለሁ”(ኢሳ28፡16፣8፡14) አለ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ስለክርስቶስ የተነገረ ነው በማለት በሮሜ 9፡33 ላይ ጠቅሶት እናገኛለን፡፡ስለዚህም ነቢዩ ኢሳይያስና ቅዱስ ጳውሎስ ጽዮን ያሏት ቅድስት ድንግል ማርያምን እንደሆነ በዚህ ኃይለ ቃል መረዳት እንችላለን፡፡ የማሰናከያ አለት የተባለው ክርስቶስ እንደሆነም “እነሆ የብዙዎች ልብ ሐሳብ ይገለጥ ዘንድ ይህ ለእስራኤል ላሉት ለብዙዎች ለመውደቃቸውና ለመነሣታቸው ለሚቃወሙትም ምልክት ተሾሞአል፡፡”(ሉቃ.2፡34-35) ተብሎ ተጽፎአል፡፡ ስለዚህ የማሰናከያ አለት የተባለውን ክርስቶስን ፀንሳ የወለደችው ቅድስት ድንግል ማርያም ጽዮን መባሉዋን በእነዚህ ጥቅሶች ማረጋገጥ እንችላለን፡፡

ነቢዩ ዳዊትና ኢሳይያስ ጽዮን ከተሰኘች የሙሴ ፅላት ካህኑ በሚያቀርበው መሥዋዕት አማካኝነት አፋዊ ድኅነት እንደተደረገ፣ ከእመቤታችን ከተወለደው አማኑኤል አማናዊ ድኅነት እንዲፈጸምልን“መድኃኒት ከጽዮን ይወጣል ከያዕቆብም ኃጢአተኝነትን ያስወግዳል”(መዝ.13፡10፤ኢሳ.59፡20) በማለት ስለክርስቶስ ትንቢትን ተናግረዋል፡፡ ይህንንም ቅዱስ ጳውሎስ ለጌታችን ለመድኃኒታችን ሰጥቶ በሮሜ.11፡26 ላይ ተጠቅሞበታል፡፡ በዚህም ቦታ ጽዮን ያሏት ቅድስት ድንግል ማርያምን መሆኑን ማስተዋል እንችላለን፡፡ ምክንያቱም እርሱ ከእርሱዋ እንጂ ከሌላ አልተወለደምና፡፡ ነገር ግን “መድኃኒት” የተባለው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለመሆኑ “መልአኩም እንዲህ አላቸው፡-እነሆ ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁ በዳዊት ከተማ መድኅኒት እርሱ ክርስቶስ ተወለደ” (ሉቃ.2፡10)በማለት ገልጾልናል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ኢየሱስ ማለት “መድኃኒት ማለት ነው (ማቴ.1፡21) የኢየሱስም እናት ደግሞ ቅድስት ድንግል ማርያም መሆኑዋን ማንም የማይክደው ሐቅ ነው፡፡ ስለዚህም ነቢያቱ “መድኃኒት ከጽዮን ይወጣል” ሲሉ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጽዮን ከተባለችው ከቅድስት ድንግል ማርያም ይወለዳል ማለታቸው እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡

ምንም እንኳ ቅዱስ ዳዊትና ሌሎች ነቢያት ስለቅድስት ድንግል ማርያም ለመናገር ሲሉ ጽዮን የሚለውን ስም አብዝተው ይጠቀሙ እንጂ አልፎ አልፎ ግን ጽዮን በማለት ስለ ከተማዋ ተናግረው እናገኛለን፡፡ ለምሳሌ ሚክያስ “ስለዚህ በእናንተ ምክንያት ጽዮን ትታረሳለች”(ሚክ.3፡12)ይላል፡፡ ይህ በቀጥታ ስለጽዮን ከተማ የተነገረ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ስለጌታችን መናገር ሲፈልግ ስለእርሱ የሚናገሩትን ብቻ መርጦ እንደተጠቀመ እንመለከታለን፡፡ እኛም እንዲሁ ለቅድስት ድንግል ማርያም የተነገሩትን አስተውለን ልንለያቸው ይጠበቅብናል፡፡ ምክንያቱም አንዳንድ ስለቅድስት ድንግል ማርያም ያልተጻፉ ነገር ግን ጽዮን የሚለውን ስም ይዘው የሚገኙ የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባት አሉና፡፡ ቢሆንም ስለታቦተ ጽዮን የተጻፉ ገቢረ ተአምራት ሁሉ እግዚአብሔር ቃል ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወለዶ ለፈጸማቸው ታላላቅ የድኅነት ሥራዎች ምሳሌዎች ናቸው፡፡

በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በብሉይ ኪዳን በታቦተ ጽዮን የተፈጸሙትን ገቢረ ተአምራት ለድንግል ማርያምና ለጌታችን ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በመስጠት ተርጉማ ለልጆቹዋ ታስተምራለች፡፡ በኅዳር 21 ቀንም በታቦተ ጽዮን የተፈጸሙት ታላላቅ ተአምራት የሚታሰቡበት ቀን ነው፡፡ በዚህ ቀን ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በታቦተ ጽዮን የተፈጸሙትን ታላላቅ ተአምራት እግዚአብሔር ቃል ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ በመወለድ ከፈጸማቸው ታላላቅ የድኅነት ሥራዎች ጋር በማነጻጸር በድኅነታችን ውስጥ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ድርሻ ምን እንደሆነ ትገልጻለች፡፡ ለምሳሌ ታቦተ ጽዮንን የተሸከሙ ካህናት እግራቸው የዮርዳኖስን ባሕር በመንካቱ ባሕሩ ለሁለት እንደተከፈለ እንዲሁ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ ተወልዶ ጥምቀትን በራሱ ጥምቀት በመመሥረት ከሰይጣን ባርነት ወደ እግዚአብሔር ልጅነት እንዳሸጋገረን እናወሳበታለን(ኢያ.3፤ ማቴ.3፡13-17) ፡፡ ፍልስጥዬማውያን ከእስራኤላውያን ጋር ውጊያ በገጠሙ ወቅት ታቦተ ጽዮንን ማርከዋት ዳጎን በሚባለው ቤተ ጣዖታቸው ውስጥ አኑረዋት ነበር፡፡ ነገር ግን ታቦቷ ዳጎኑን በፊቷ ሰባብራ እንደጣለችው እንዲሁ ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደው በጌታችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእኛ ላይ ሠልጥኖ የነበረው ሰይጣን ድል መነሳቱን እናወሳበታለን፡፡ ((1ሳሙ.5፤6)

በዚህ መልክ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መንጎቹዋን ስለቅድስት ድንግል ማርያምና ስለልጁዋ ስለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲሁም በእርሱ ስለተሰጠን ሰማያዊ የአገልግሎት ሥርዐት፣ ስለታቦት ጥቅምና አገልግሎት፤ ታቦተ ጽዮንንና ቅድስት ድንግል ማርያምን በማነጻጸር በሰፊው እንደምታስተምር መረዳት እንችላለን ፡፡
እግዚአብሔር አምላክ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ረድኤትና በረከት ያሳትፈን፡፡ የእግዚአብሔር አብ ጸጋ የእግዚአብሔር ወልድ ቸርነት የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አንድነት በእኛ ላይ ለዘለዓለም ጸንቶ ይኑር አሜን!!



ምንጭ፦  ማኅበረ ቅዱሳን ድኅረ ገጽ




Monday, November 25, 2013

ቅኔአዊ ግጥም የሳዑዲን ግፍና በደል አስመልክቶ

          (በሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው)saudi and ethiopians

እንዲህ እንዲያ ብለው አሙን ፤ ተጠይቀው ሲመልሱ
የወገኖቻችንን ደም ፤ በእብደት ግፍ ያፈሰሱ
የኢትዮጵያ ስደተኞች ፤ ባሕላችንን ተቃረኑ
ንጽሐችንን አረከሱ ፤ ነፍሳችንን አስኮነኑ
መጠጥ በማዘዋወር ፤ በስርቆት ወንጀል በምኑ
አንተ አረመኔ እንስሳ ፤ ምኑን ብየ ላውጣልህ ስም
መጠጥ ምንህ ነውና ፤ ስካርህ የአንተ በሰው ደም
አስገድዳ አልደፈረችህ ፤ ደፈርካት እንጅ በማደም
መድፈርህ ሳያንስ ሳይበቃ ፤ አርደህ በላሃት ርጉም
አንተ ውሉደ አጋንንት ፤ አረመኔ ዘረ ሰዶም ፡፡
    ሌቦች ነበረ ያልካቸው ? እሰይ እንኳንም ሰረቁ
    ፈልገውት እንዳይመስልህ ፤ ምንም ነገር አይደል ድንቁ
    እባክህ ለከት ይኑርህ ፤ በዚህ አይታማም ወገኔ
    ነቢይህ ያውራህ ታሪኩን ፤ ያበሻን ማንነት ብያኔ
    የፍትሕ ደግነት ባለቤት ፤ ሕዝብ እንደሆነ መናኔ
    ነገር ግን እንዲያ ማድረጉ ፤ ሲያደርግ ባላይም በዓይኔ
    የሚነግርህ ስለነበረ ፤ መንገሩ ነበር በቅኔ
    በቋንቋው ጸጋ በዘይቤ ፤ በሰምና ወርቅ ምጣኔ ፡፡
ሐበሻ እንደዚህ ማስኖ ፤ የመከራ ዓይነት ለመጋቱ
ሞት በመንገዱ እየበላው ፤ አሁንም ለስደት መትጋቱ
ውዲቷ ሀገሩን እንደጠላ ፤ እየጣለለት መውጣቱ
ቅድስቲቱን እናት ሀገር ፤ ያረገብንን ያሳር ጓዳ
ለዜጎች ሲዖል ገሃነም ፤ ምቾት የሞላት ለእንግዳ
ሀገር ወገንን አውድሞ ፤ ተግቶ የሚሠራ ለባዳ
ይሄንን ቅጥረኛ መንግሥት ፤ ለጠላት ያደረን ባንዳ
ወልዳቹህ በማሳደግም ፤ ለዚህ ያበቃቹህት ይሁዳ
እናንተው ስለሆናቹህ ፤ የታሪኩ ሀሁ ሠሌዳ
ምሰሶው ወራጅ ማገሩ ፤ መሠረቱና ግድግዳ
ለችግራችን ተጠያቂ ፤ የምስቅልቅሉ ባለዕዳ
እናንተው መሆናቹህን ፤ ሊጠቁምና ሊያስረዳ
ያለንበትን ስንክ አሳር ፤ አውጥቶ ሊያሳይ ከሜዳ
ለማድረግ ነበረ እንጅ ፤ ከቶም አልነበር ሊጎዳ
መናኛ ነገርን ወስዶ ፤ ሊጠቀም ሊሆነው ጋዳ
እናንት በምቾት በቅንጦት ፤ እየኖራቹህ በተድላ
በሠራቹህት ሸር ክፋት ፤ እሱ መዋጡን ባሜኬላ
የስሕተታቹህን ርቀት ፤ የክብደቱንም ልክ ጣራ
ትኩረታቹህን በማግኘት ፤ ሊያሳውቅ እንጅ ያን ዳራ
አነፃፅራቹህ እንድታዩት ፤ በግብረገባዊ ተዋስኦ
በእምነታቹህ ሚዛን ልክ ፤ እንድትለኩት ያለ አድልኦ
ለማድረግ ነበረ እንጅ ፤ ከቶም አይደለም የአመል
የእውነት ምስክር አለን ፤ ከፈላስፋ እስከ አምላክ ቃል ፡፡
    የልቅ ማሰብ ያለባቹህ ፤ ለዚህ ለዚያ ሁሉ ሴራ
    ሀገራችንን ለማፍረስ ፤ ላረጋቹህት ስርሠራ
    ብትከፍሉ የማትጨርሱት ፤ አለባቹህና ብዙ ዕዳ
    ከቶ እንዴት ትሆናላቹህ ፤ አስቡበት አለው ፍዳ
    ይብላኝ ለእናንተ እንጅ ፤ እኔስ አለኝ ሀገር የእርሻ
   ጊዜአዊ ነው የኔ ችግር ፤ ለነገ አለኝ መፈወሻ
   መግቢያ አላጣም እኔ እንዳንተ ፤ አልነቀል መጨረሻ ፡፡
አርቃቹህ ብታስቡ ፤ መኖሪያቹህ ምድረበዳ
እህል ዘርቶ የማያበቅል ፤ የማያቆም አገዳ
አሁን ነገ ላይ ተሟጦ ፤ በሚያልቀው ዘይት ታብዮ
እንዲህ በግፍ ላይ መጫወት ፤ ፍርጃህ ነው የልቅ በል ወዮ
ሐምሳ ዓመታት ለማይቆየው ፤ አቤት ስንቱ ተደረገ
ደጅህ ላይ አለ ጠብቀው ፤ ይነቅልሀል ስደት ነገ
ዘይትህን ሲጨርስ መሬቱ ፤ ሌላ የለው የተነፈገ
ወዴት ይሆን መሰደጃህ ፤ ጎረቤትህ ከመሸገ
ጠላት አርገህ ካቆየኸው ፤ ፊትህን ማየት ካልፈለገ ፡፡
ላለው ሆኖልህ ነገሩ ፤ ዛሬ ላንተ ያደገደገ
ነገ አጠገብህ አይኖርም ፤ በሩን ይዘጋል እያሸገ
ያው በተራህ ትቆጥራለህ ፤ በየዓይነቱ ግፍ ወፍዳ
የዘሩትን ማጨድ አይቀር ፤ አጥቶ መውጫ ቀዳዳ
ወገን ንቃ ይግባህ ሴራው ፤ እኛን ማጥፋት የፈለጉት
እርስ በርስህ እያፋጁ ፤ አስቀምጠው ባንዳ መንግሥት
ሀገርህን ለመውረስ ነው ፤ ሲነጥፍባቸው ሲሳይ ሀብት ፡፡
    ብዙ ነው ሴራው ትብትቡ ፤  ምኞታቸውን ለማስመር
    እግዜርን ይዘህ ታገለው ፤ ሳትከፋፈል በብሔር
    ወጥመዱ ይከሽፋል ሴራው ፤ ይወድቁበታል ለአሳር
    የአንተ ቀን ደግሞ ይመጣል ፤ ይኖርህማል አኩሪ ሀገር ፡፡