Tuesday, April 23, 2013

የተግባር ፍቅር


ፍቅርን የሃይማኖት አባቶች፣ የፍልስፍና ሰዎችና ዘመናዊ ወጣቶች በተለያየ መልኩ ይገልጹታል፤ እኛም ሁላችን ፍቅርን ግለጹ ተብሎ ጥያቄ ቢቀርብልን በተረዳነው መጠንና በሚመቸን መልኩ እንገልጸዋለን። ነገር ግን የገለጽነውን፣ የተረጎምነውን፣ የተረክነውን በተግባር መኖር እንችላለን ወይ የሚለው ለሁሉም ሰው ትልቅ ጥያቄ ነው።
ስለ ፍቅር መጻፍ ቅዱስ ከዘፍጥረት እስከ እራይ ዮሐንስ በግልጽና በምንረዳው መልኩ ተገልጾልናል። ብርሃን ዓለም ቅዱስ ጶውሎስ ስለ ፍቅር በአስተማረበት አንቀጹ በ1ኛ ቆሮ 13፡1 ጀምሮ_ ፍቅርን በሚገባ ከተረጎመው በኋላ "እምነት፣ ተስፋ፣ ፍቅር እነዚህ ሦስቱ ጸንተው ይኖራሉ፤ ፍቅር ግን ከሁሉም ይበልጣል። ዛሬ ላይ የሁሉ ሰው ጥያቄ ሊሆን የሚገባው ይህን ከሁሉ የሚበልጠውን ፍቅርን ምን ያክል በተግባር እየተገበርነው ነው? በምን መልኩ እየኖርንበት ነው? የሚሉትን ጥያቄዎች መመለስ ይገባናል።
  ዓለም ይህን ታላቅ የእግዚአብሔር ስጦታ በተግባር ተግብሮ የሚያሳያት ብታገኝ ኑሮ ባልጠፋች፤ ከብርሃን ወደ ጨለማ፣ ከሰላም ወደ ጠብና ክርክር፣ ከጽድቅ ወደ ኩነኔ፣ ባአጠቃላይ ወደ መከራ፣ ችግር፣ረሃብ፣ ቸነፈር፣ ጦርነትና ራስን ማጥፋት ደረጃ ባልደረሰች ነበር።
በትዳራችንና በጓደኝነታችን መካከል ወደድኩሽ፡ ወደድኩህ፣ ወደድኩህ ወደድኩሽ ከሚለው አልፈን ፍቅርን በተግባር መተግበር ብንችል ትዳራችን እንደ አብርሃምና ሳራ ተብሎ እንደተዘመረልን ሰላምን፣ ደስታንና መተሳሰብን ተጎናጽፈን እከመጨረሻው የጸናን እንሆን ነበር ዳሩ ግን ፍቅራችን የንግግር እንጂ የተግባር ስላልሆነ ፍቅር ከመካከላችን ቀዝቅዛ ዓለም በምቀኝነትና በጥላቻ ወድቃ፤ በትዳራችንና በእኛነታችን ውስጥ ያለው ፍቅር የታይታና የውሸት ፍቅር እየሆነ በመምጣቱ መተማመን እንዲጎለን አድርጎታል።
አባቶቻችን ስለፍቅር ሲናገሩ፡ "ፍቅርን ይኖሩታል እንጂ በቃላት አይገልጹትም" ብለው ፍቅርን በተግባር እንጂ ለሰዎች ማሳየት/መግለጽ የምንችለው በቃላት፣ በንግግር፣ በሐተታ መግለጽ እንደማይቻል ያስረዳሉ። ፍቅርን በተግባር የሚተገብሩ ምንኛ የታደሉ ናቸው? ምክንያቱም ፍቅር ማለት ራሱ እግዚአብሔር ነውና። «እግዚአብሔር ፍቅር ነው፣ በፍቅርም የሚኖር በእግዚአብሔር ይኖራል፡ እግዚአብሔርም በእርሱ ይኖራል» 1ዮሐ 4፡16። ሁላችንም ቢሆን ፍቅርን በቃላት እናውቀዋለን፣ እንናገረዋለን፣ እንተርከዋለን ነገር ግን ተግባር ላይ የለም፤ አንኖርበትም። እግዚአብሔር አምላክ እንደሚወደን፣ እንደሚያፈቅረን ነገረን በተግባር በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ነፍሱን ስለኛ ሲል በፈቃዱ ሰጦ ፍቅርን ገለጸልን። እኛ ዛሬ የዘመኑን የሀሰት ፍቅር ከየት አመጣነው? ከማን ወረስነው? መጨረሻችንስ ምን ይሆን? እና መሰል ጥያቄዎችን ለመመለስ የተግባር ፍቅር ያስፈልገናል።

የተግባር ፍቅር ከአባቶች፦ አባቶቻችን በትምህርታቸው፣ በስብከታቸው፣ በንግግራቸው ሁሉ ፍቅርን ይገልጻሉ። ነገር ግን ፍቅርን በተግባር ተግብሮ የሚያሳየን አባት ያስፈልገናል። አርያና ምሳሌ የሚሆን አባት ለቤተ ክርስቲያን፣ ለመንግሥትና ለዓለም ያስፈልጋል። አባቶች ፍቅር በተሞላ አገልግሎታቸው ዓለምን የመለወጥ ጸጋውም ልምዱም ብቃቱም አላቸው ነገር ግን ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረ "ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?" ገላ 3፡1 ፍቅርን በተግባር በእውነት እንዳንተገብር ፖለቲካው፣ ዘረኝነቱና አለማዊነቱ አዚም ሁኖብናል። አባቶች ዓለም ከዚህ እንድትወጣ ቁልፉ እናተ ጋር ነውና በጸሎታችሁና በፍቅር ሳቡን፤ እኛ ዓለሙንና ምኞቱን ወደናልና ዘላለማዊ ሞትና መከራ እንዳያገኘን።
የተግባር ፍቅር ከመምህራንና ከሰባኪያን፦ እውነት ነው በሁሉም የመድረክና የጉባኤ አስተምሯችሁ ላይ ፍቅርን በአንደበታችሁ ትመሰክራላችሁ። ነገር ግን ፍቅርን በተግባር የሚያሳየን መምህርና ሰባኪ እኛ ተማሪዎቻችሁና ተሰባኪያን እንፈልጋለን። ፍቅርን ከቃላት ይልቅ ተግብራችሁ አሳዩን፤ ፍቅርን በስብከታችሁ ብቻ ሳይሆን በህይወታችሁ አሳዩን፤ አርያና ምሳሌ ሁኑን። የዘመኑ ትውልድ መስማት ብቻ ሳይሆን ማየት ይፈልጋል፤ ማስረጃን ይሻል። የአማላካችን የኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል ሰባኪዮች ናችሁና እንደ አምላካችን እያደረጋችሁና እየተገበራችሁ "ከእኔ ተማሩ" ልትሉን ይገባል።
የተግባር ፍቅር ከመንግሥት፦ መንግሥት ሆይ መንግሥት ከአለህዝብ ሊኖር አይችልምና ለግዛትህ ምክንያት የሆነልህን ህዝብ በፍቅር ግዛው። ህዝቤን እወዳለሁ ብለህ በአንደበትህ በመገናኛ ብዙኃን እንደምትነግረን በተግባር አሳየን። መድሎው፡ ሙስናው፡ዘረኝነቱና በቀሉ ይቅርና እንደምትወደን በተግባር አሳየን። ሁሉም ብሄር፣ ሁሉም የእድሜ ክልል፣ የተማረ ያልተማረ ለግዛትህ ያስፈልግሃልና በህዝብህ ላይ መከራና ስቃይ አታብዛብን። መንግሥት ሆይ "ሺህ ዓመት ንገሥ" ብሎ ህዝህ የሥልጣን ዘመንህን እንዳራዝምልህ ፍቅርን በተግባር አሳየን።
የተግባር ፍቅር ከሁላችን፦ "እኔ እንደ ወደድኋችሁ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ ትእዛዜ ይቺ ናት" ዮሐ 15:12 ብሎ አምላካችን እንዳስተማረን ማንንም ሳንመለከት በመስቀል ላይ የተሰቀለውን የክርስቶስን ፍቅር እየተመለከትን ሁላችንም እርስ በእርሳችን እንዋደድ፣ እንፋቀር። ፍቅርን በተግባር ተግብረን ለሌሎችም አርያ እንሁን።

የፍቅር ሰው እንድንሆን የአምላካችን መልካም ፈቃድ፤ የቅዱሳን ተራዳኢነት አይለየን።

No comments:

Post a Comment