Tuesday, August 13, 2013

ፅንሰታ ለማርያም

ቅዱሳን አባቶቻችን ስለ እመቤታችን ነገር በውዳሴያቸውና በቅዳሴያቸው እንዲህ ተናግረዋል፤ ቅዱስ ያሬድ “ማርያምሰ ተኀቱ እምትካት ውስተከርሱ ለአዳም ከመ ባሕርይ ጸዓዳ:- ማርያምስ ከጥንት ጀምሮ በአዳም ባሕርይ ውስጥ እንደ ነጭ ዕንቁ ታበራለች" አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም "ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ጸነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ:- ድንግል ሆይ በኃጢአት ፍትወት የተፀነስሽ አይደለም ፤በሕግ በሆነ ሩካቤ ከሐና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ" "እኔስ የማርያምን ነገር እናገራለሁ በማብዛት አይደለም በማሳነስ ነው እንጂ፣ በማርዘም አይደለም በማሳጠር ነው እንጂ " በማለት በተአምረ ማርያም ላይ የእመቤታችን ነገር እፁብ ድንቅ መሆኑን ዘወትር በዕለተ ሰንበት ያበስሩናል።

በኢየሩሳሌም አገር የሚኖሩ ኢያቄምና ሐና የተባሉ በጣም ደጋግ ሰዎች ነበሩ፡፡ አንድ ልጅ እንኳ ስላልነበራቸው እጅግ ያዝኑ ነበር፡፡ ወደ ቤተመቅደስ እየሄዱ እግዚአብሔር ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ አጥብቀው ይለምኑት ነበር፡፡ መባ ይዘው ለሊቀ ካህኑ ሮቤል ሲሰጡት ሊቀ ካህኑ እንኳ ሳይቀር እግዚአብሔር ብዙ ተባዙ ያለውን ህግ በእናንተ ላይ እንዳይፈጸም አድርጎ ልጅ የከለከላችሁ ኃጢአተኛ ብትሆኑ ነውና መባችሁን አልቀበልም ብሎ በእጅጉ አሳዝኗቸዋል። 
በሊቀ ካህኑ እያዘኑና እየተከዙ ሲመለሱ ከድካማቸው ያርፉ ዘንድ ዛፍ ስር ተቀመጠው ሳለ እርግቦች ጫጩቶቻቸውን ሲያጫውቱ ተመልክተው “ለነዚኽ ወፎች እንኳ ልጆችን የሰጠህ አምላክ ለእኛስ መች ይሆን ልጅ የምትሰጠን?” ብለው እጅግ አምርረው አለቀሱ፡፡ ሐምሌ 30 እሷ እርሱ ግምጃ ሲያስታጥቃት መቋሚያው አፍርታ ፍጥረት ፍሬዋን ሲመገቡ፣ እሱ ለእሷ ነጭ ርግብ ሰባቱን ሰማያት ሰንጥቃ መጥታ በቀኝ ጆርዋ ገብታ በማኅፀንዋ ስታድር ሕልም አለሙ። ሄደው ለመፈክረ ሕልም/ ሕህልም ተርጓሚ ሲነግሩት የከበረች ልጅ እንደሚወልዱ ነገራቸው። እነእርሱም ነገሩ እንግዳ ነገር ስለሆነባቸው ጊዜ ይፍታው ብለው ተመለሱ። የእግዚአብሔር ፈቃድ እንዲሆንላቸው በጸሎት ጠየቁ፡፡ እግዚአብሔር ወንድም ሆነ ሴት ልጅ ቢሰጣቸው አድጎ/አድጋ እኛን ያገልግለን/ታገልግለን  ሳይሉ ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ እንዲሆን እንደሚሰጡት ቃል ገቡ፡፡
ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ አብርሃምን እና ሳራን የተመለከተ አምላክ በኢያቄምና ሃና አማካኝነት ለዓለም ድህነት ምክንያት የሆነችውን እና ዓለም ሳይፈጠር በአምላክ ልቦና ታስባ ትኖር የነበረች የተነገረላት ትንቢት ሊፈጸም የአባት የእናቷ የቅድመ አያቶቿ ራዕይ ሊተረጎም ጌታ የፈቀደበት ጊዜ ሲደርስ እመቤታችን እግዝእትነ ማርያም እሁድ እለት ነሐሴ 7 ቀን በ16 ዓ.ዓ ተፀነሰች፡: ሐና በእርጅናዋ ጊዜ መፅነሷ የተመለከቱ ዘመዶቿና ያገሯ ሰዎች ተገርመው እየመጡ ይጠይቋት ነበር፡፡
እመቤታችን ማርያም በፅንስ እያለች ታምራትን አድርጋለች። ከእነዚህም መካከል ዐይነ ስውር የነበረችው የአርሳባን ልጅ ወደ ሐና መጥታ እውነትም ሐና መጸነሷን ለማረጋገጥ ሆዷን ዳሰሰቻት፡፡ በአድናቆትም ሳታስበው ዐይኗን ስትነካ ዐይኗ በራላት፡፡ በሌላ ጊዜም የአጎቷ ልጅ በህመም ምክንያት ይሞትና ሐና ትወደው ስለነበር ልታለቅስ ወደአረፈበት ቤት ትሔዳለች፡፡ እንደደረሰችም አስክሬኑ በተቀመጠበት መካከል አልጋ ዙሪያ ስታለቅስ ሳለ ድንገት ጥላዋ ቢያርፍበት የሞተው ሰው ተነስቶ ሐና የአምላክ እናት የምትሆን እመቤታችንን እንደምትወልድና በዚህም ሐና እጅግ የከበረችና ምስጋና የሚገባት መሆኗን መሰከረ፡፡ ከዚህም በኋላ እመቤታችን ግንቦት 1 ቀን በክብር ተወለደች።


እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ  ከልጅሽ ከወዳጅሽ ይቅርታው፣ ቸርነቱ፣ ምህረቱ በእኛ ላይ እንዲያድር ለምኝልን፡ አሜን!!!

No comments:

Post a Comment