Saturday, December 7, 2013

ኔልሰን ማንዴላ

ይህንን ፎቶ ሳነሳ ሁለት አይነት ስሜት ተሰማኝ። የመጀመርያው የኩራት፣የደስታ ስሜት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ የሃዘን ስሜት ተሰማኝ። ብዙ አፍሪካውያን በዓለም በበርካታ ስራዎች የሚታወቁ ሰዎች እንዳሉ ቢታወቅም እንደ ኔልሰን ማንዴላ ግን በመሪነት ደረጃ ለአለም ምሳሌና አርያ የሆነ የለም። በዚያ ላይ ከብዙ ስቃይና መከራ ፣ እንግልትና እስር በኋላ የሰላም፣ የነጻነት፣ የአንድነት፣ የይቅርታ አባት መሆን በእጅጉ ታላቅነት ነው። የበደሉትን፣ያሰቃዩትን፣ አንተ ጥቁር ሰው አይደለህም ከነጮች ጋር አብረህ ልትኖር፣ ልትማር ፣ በአንድ ባስ ውስጥ ልትጓዝ አይገባይህም ብለው አዋጅ አውጀው በመላ ጥቁር ደቡብ አፍርካውያን ላይ ከባድ ወንጀል የፈጸሙትን ለሰላምና ለአንድነት ሲል በይቅርታ እንዲታለፉ ያደረገ ታላቅ የይቅርታ አባት መሆኑን ዓለም ሁሉ በአንድ አፍ ሲመሰክር ሳይ በባዕድ አገር የደስታ ስሜት ተሰማኝ።

በተቃራኒው ደግሞ ይህን ታላቅ ሰው እርጅና የሚሉት በሽታ፣ ሞት የሚሉት ለሰው ልጅ አይቀሬ እጣ ፈንታ ሲነጥቀን ያለ ቢሆንም ሐዘን ተሰማኝ፡፡ በይበልጥ ግን ዓልም ይቅርባይነት ጠፍቶባት፣ መቻቻል አቅቷት፣የበቀልና የጥላቻ መንፈስ ነግሶባት እያየ ታላቁ ማንዴላ አንድ ሰው እንኳ ሳይተካ ማለፉን ሳስብ ደግሞ ሐዘኔ ይበልጥ በረታ። ግን እኮ ማንዴላ ፍቅርን፣ ይቅርባይነትን፣ መቻቻልን፣ የውይይት/ድርድር ልምድን በተግባር አሳይቶናል። እኛ እንዴት ከእሱ መማር አቃተን? ምነው ለይቅርታ ዘገየን? ምነው ለበቀል ቸኮልን?
ታላቁን የሰላም አባት ማንዴላን ለማስታወስ በኖርዎይ ኦስሎ ዩኒቨርስቲ ብሊንደር ላይበራሪ መግቢያ በር ላይ በትልቅ ጠረጴዛ የእርሱ ፎቶና ስለ እርሱ የተጻፉ መጻሕፍት ከተቀመጠበት በ06/12/2013 እኤአ ያነሳኋቸው ፎቶዎች ናቸው።


No comments:

Post a Comment