Tuesday, June 11, 2013

የዘንድሮው ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ውሳኔ ተግባር ላይ ከዋለ ለቤተክርስቲያን አስትዋጾው የጎላ ነው


የቅዱሳን ጳጳሳት ተግባር "በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ።"(ሐዋ 20:28)  ተብሎ በቅዱስ መጽሐፍ እንደተገለጸው የዘንድሮ ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖደስ ጉባኤ ከመነሻው እስከ ፍጻሜው ይኽን የማሳይና የሚያረጋግጥ ነበር።
ጉባኤው ሲጀመር ፓትርያሪኩ ያነሷቸውን ነጥቦች ስንመለከተ ለዚች ቅድስት ቤተክርስቲያን ችግር ለሚያሳስበው ለሚያንገበግበው እውነተኛ የቤተክርስቲያን ልጅ የዘወትር ጥያቄዎች ነበሩ። ዘመን አመጣሹን(ዘረኝነቱን)ና የተለያዩ ችግሮችን ወደኋላ በመተው ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅማትን የመወያያ አጀንዳ አድርገው ጉባኤውን በመጀመራቸው ቅዱስ ፓትርያሪኩን ልናመሰግናቸው ይገባል። እግዚአብሔር በእርሳቸው ላይ አድሮ ቤተ ክርስትያኗ ከአለችበት ከተለያዩ ዘርፈ ብዙ ችግሮች ሊታደጋት እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል።
ቅዱስ ፓትርያሪኩ በዋናነት ያነሷቸው ነጥቦች፦
  1.  መንፈሳዊነትን የለቀቁ/ ብልሹ አሠራርን ማረምና ማስወገድ
  2. አስተዳደሩን በአዲስ መልክ ማዋቀር
  3.  የፋይናንስ አያያዝን ማስተካከል
  4. የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን እንደገና ማዋቀር 
እነዚህ 4ቱም ነጥቦች የቤተ ክርስቲያን መሰረታዊና ቤተ ክርስቲያኗን ወደፊት እንዳትጓዝ ያደረጉ ችግሮች ናቸው። የቤተ ክርቲያኗ የበላይ ጠባቂ ጳጳሳት በእነዚህና ሌሎች ጉልህ ችግሮች ላይ መወያየታቸውና ለችግሮች  መፍትሔ የሚሆኑ ዝርዝር ተግባራትን ማስቀመጣቸው የቤተ ክርስትያንን የነገ ጉዞ ያመላክተናል። ምንም እንኳ የቤተ ክርስቲያን ጉዞ የመስቀል ጉዞ ቢሆንም ውስጣዊ ችግሯን ማስወገድ ግን የአባቶቻችን እና የእያንዳንዳችን ተሳትፎ ጉልህ አስትዋጾ አለው።
ጉባኤው ከብዙ ውይይትና ምክክር በኋላ ለቤተ ክርስቲያን አስፈላጊ ናቸው ብሎ ያመነበትን ውሳኔዎች ወስኖ መግለጫ ስጥቷል። ከውሳኔዎችም መካከል፦
  • በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ የሚታዩ ብልሹ የአስተዳደርና የአሰራር ችግሮችን  እንዲሻሻሉ ማድረግ፤ 
  • ጥራት የጎደለውን የፋይናንስ አያያዝን በተገቢው መልኩ ማስተካከል እንዳለበት፤ 
  • ሙስናንና ለብክነት የተጋለጡ/መንፈሳዊነትን የለቀቁ አሰራሮችን ለመቅረፍ ዓብይ ኮሚቴ ማዋቀርና ችግሮች እንዲቀረፉ ማድረግ
  • የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በአንድ ሀገረ ስብከት፤ በአንድ የቅዱስ ፓትርያርክ ረዳት ሊቀ ጳጳስ እንዲመራ መድረግ 
  • የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ ምርጫ
  • ከሀገር ውጪ ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር የተጀመረው የሰላም ውይይት ጥረት መቀጠል እንዳለበት 
  • በመካከለኛው ምሥራቅና በሌሎች የዓለም ክፍሎች ለሥራ ፍለጋ በሕገ ወጥ መንገድ በሚሄዱ ወገኖቻችን ላይ የሚደርሰውን ዘግናኝ ድርጊት ለማስቆም በኹኔታው ጎጂነት ላይ ግንዛቤ የሚፈጥር ትምህርት በስፋት እንዲሰጥ ቅ/ሲኖዶስ ለመምህራን፣ ካህናትና ሰባክያን ሁሉ መመሪያ ሰጥቷል
ይህ ውሳኔ  ተግባራዊ ከሆነ ቤተ ክርስቲያናችን ከመቸውም በበለጠ ተጠቃሚ ትሆናለች። አገራችን ኢትዮጵያም በእድገት ወደፊት ትገሰግሳለች። ምክንያቱም 
  1. ዘመን አመጣሹንና የዘመኑ ፖለቲካ ያመጣውን የዘረኝነት መንፈስ አሶግዳ አገራዊ ስሜት ያለውና በህገ እግዚአብሔር የሚመራ ዜጋ መፍጠር ስለምትችል፤
  2. ከሙስና እና አለማዊነት የተላቀቀ የአሰራር መርህ መዘርጋት ስለምትችል፤
  3. ለ21 ዓመታት በአስተዳድር ጉዳይ የተለያዩት አባቶችና በቅዱስ ሲኖዶስ መዋቅር ስር የማይተዳደሩ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ወደ ቀደምት አንድነታቸው መምጣት ስለሚችሉ፤
  4. በተጠቀሱት ችግሮች  ምክንያት ከቤተ ክርስቲያን የራቁ ምዕመናን ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መመለስና መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን መቀጠል ስለሚችሉ፤ 
  5. ህዝበ ክርስቲያኑ በሙሉ ከሥጋዊ አስተሳሰቦች ርቆ በመንፈሳዊ ሕይወት እየተጋ ለልማትና ለአገር እድገት መሥራት ስለሚችል ቤተ ክርስቲያናችንና አገራችን በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተጠቃሚ ይሆናሉ።

ቅዱስ ሲኖዶስ ቢያስብበት፦

ቅዱስ ሲኖዶስ በውጭ ሀገር በልዩነት ከሚገኙ አባቶች ጋር የሰላም ውይይት መቀጠል እንዳለበት መወሰኑ  ይበል የማሰኝ ነው።  አባት ልጅን ይፈልጋል፤ ኢየሱስ ክርስቶስ 99ኙን ነገደ መላእክት ትቶ አንድ ልጁን አዳምን ፍለጋ ከሰማየ ሰማያት እንደ ወረደ፤ ለሰሚና ለአጠራር በማይመች መልኩ ቤተ ክርስቲያንን ገለልተኛ ብለው ራሳቸውን ያገለሉ ወገኖቻችንን በቅዱስ ሲኖዶስ ስር እንዲተዳደሩ ያለመሰልቸት በተደጋጋሚ የአንድነት ጥሪ ቢያስተላልፍ መልካም ነው።  

በውጭ ለምትገኙ ብፅዕዋን አባቶች፡

ልዩነቱን ትታችሁ፣ ቅዱሳን አባቶቻችን እንዳስተማሩት በትህትና ራሳችሁን ዝቅ አድርጋችሁ፣ ለቤተ ክርስቲያን ሰላምና አንድነት ስትሉ ይህ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ሁሉንም የሚያስማማ ስለሆነ ሰላምና አንድነት የምትፈጥሩበትን ሁኔታ አመቻቹልን። እናንተም ከታሪክ ተወቃሽነት ነጻ ትሆናላችሁ እኛም ልጆቻችሁ ከእናንተ ትህትናንና እርቅን በተግባር እንድንማር አድርጉ።

ገለልተኞች፦

ምንም እንኳ ገለልተኛ የሚለው ትርጉም ለቤተ ክርስቲያን የሚሰጥና የሚመች ባይሆንም አትፍረዱ ይፈረድባችኋል የሚለውን ቃል በማስታውስ እኔም እንደናንተ ከትችት ራሴን አግልዬ፤ 
ለመገለላችሁ እንደ አንድ ምክንያት ስታቀርቡ የነበረው ብልሹ አስተዳደርን ነበር፤ ዛሬ ግን ቅዱስ ሲኖዶስ በዋናነት የአስተዳደር ችግሩን አጀንዳ አድርጎ  ስለተወያየበትና ውሳኔ ስለሰጠበት ተግባራዊ ይሆን ዘንድ የእናንተም አስትዋጾ በእጅጉ ያስፈልጋል። ስለሆነም ቅዱስ ጳውሎስ "ሁሉም በአግባብና  በስርዓት ይሁን" (1ኛ ቆሮ 14:40) ብሎ እንዳስተማረው እናተም መገለሉን ትታችሁ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ ትመሩ ዘንድ የታናሽነት መልእክቴን በእግዚአብሔር ስም ማስተላለፍ እወዳለሁ። መገለል ከክፉ ሥራ፣ መገለል ከተንኮል፣ መገለል ከአለማዊነትና መገለል ከኃጢአት እንጂ ከቅዱስ ሲኖዶስ ሊሆን አይገባምና። 

ስለዚህ ቅዱስ ሲኖዶስ በመግለጫው ለቤተ ክርስቲያን ክብርና ሉዓላዊነት መጠበቅ፣ ለህልውናዋ መቀጠልና ለዕድገትዋ መስፋፋት የሚቆረቆሩ የቤተ ክርስቲያናችን አገልጋዮችና ምእመናን በሙሉ ቅ/ሲኖዶስ የሚያሳልፋቸውን ውሳኔዎች ለመተግበር አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርጉ በጠየቀው መሰረት ሁላችንም ውሳኔው ተግባር ላይ እንዲውል ርብርብ ልናደርግ ይገባል።

                                        ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

No comments:

Post a Comment