Monday, June 17, 2013

ተስፋ

እግዚአብሔር አምላክ የሰው ልጅ ተረጋግቶና በሰላም ይኖር ዘንድ ከሰጠው ስጦታ መካከል አንዱና ዋነኛው ተስፋ ነው። ከ22ቱ ፍጥረታት መካከል በተስፋ የሚኖር የሰው ልጅ ነው። ሰው በተስፋ የማይኖር ከሆነ ባዶ፣ ተቅበዝባዥና በጭንቀት የሚኖር ብሎም ራሱን ወደ መጥላትና ማጥፋት የሚጓዝ ግደለሽ ይሆናል።
ተስፋ ማለት በየዕለቱ ሊገጥሙን ለሚችሉ አስቸጋሪ ሁኔታዎች መፍትሔ፣ ለሃዘናችን መጽናኛ፣ ለደስታችን ፍሬ በጉጉት የምንጠብቅበት ብቻም ሳይሆን  አስቸጋሪ መስለው ለሚታዩን ነገሮች በጎ ነገርን የምናይበት ረቂቅ የአምላክ ስጦታ ነው። ለዚህም ነው ሰዎች በምክራቸው  "ተስፋችሁ ሕያው፣ ጠንካራ፣ ጽኑና የማይናወጥ መሆን አለበት" የሚሉት። ተስፋ ካለን ብዙ ንገሮች አሉን፤ የምንሄድበት አቅጣጫ፣ የምንንቀሳቀስበት ኃይል፣ ብዙ አማራጮች፣ ሺህ መንገዶችና ሊገመቱ የማይችሉ ህልሞች አሉን። ተስፋ ካለን መሄድ ወደ ምንፈልግበት ቦታ ግማሽ መንገድ ላይ ደርሰናል ማለት ሲሆን ተስፋ ከሌለን ወይም ተስፋ ከቆረጥን ግን ለዘለዓለሙ ጠፍተናል ማለት ነው።

ተስፋ
“ተስፋ” የሚለው ቃል መጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት እንዲህ ተብራርቷል፦

  • ተስፋ ምኞትና ናፍቆት ብቻ ሳይሆን አለኝታና መተማመን የሚገኝበት ነው (ሮም.15:13)
  • የክርስቲያን ተስፋ በክርስቶስ ትንሣኤ ላይ የተመሠረተ የእግዚአብሔር ስጦታ ነው (1ጴጥ. 1:3-5)
  • ተስፋ በዚህ ዓለም አይወሰንም (1ቆሮ.15:19)
  • በሚመጣው ዓለም የእግዚአብሔር መንግሥት ተካፋዮች እንድንሆን ለእኛም ለሌሎችም ተስፋ አለን (ኤፌ.1:18፤ 1ተሰ.2:19)
  • ተስፋችን ምንም እንኳን አሁን ባይታይም የተረጋገጠና የማይጠፋ ነው (ዕብ.11:1፤ ሮም 5:5)
  • እግዚአብሔር ስለማይዋሽ ተስፋችን ከንቱ አይሆንም (1ጢሞ.1:1፤ ቲቶ 1:1-2)
  • ተስፋ ከእምነትና ከፍቅር ጋር የተያያዘ ነው (1ቆሮ.13:13)
  • ተስፋ በቅድስና እንድንኖር መከራን እንድንታገስ ያበረታታናል (1ዮሐ.3:3፤ ሮም 8:18)
  • እግዚአብሔር ለሰጠው ተስፋ ተካፋዮች መሆናችንን በመንፈስ ቅዱስ አረጋግጧል (ሮም 8:14-16፤ ኤፌ.1:13-14)
ሆኖም የእግዚአብሔር ተስፋ ፈቃዱን ለሚያደርጉ መሆኑን አውቀን የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለመፈጸም መትጋት አለብን።

መንፈሳዊ ተስፋ፦
"አሁንስ ተስፋዬ ማን ነው? እግዚአብሔር አይደለምን? ትዕግሥቴም ከአንተ ዘንድ ነው።" (መዝ 38፥7) በእግዚአብሔር ለሚያምን  ሰው ተስፋው እግዚአብሔር ነው፤ ገነት መንግሥተ ሰማያት ነው። በኑሮውም አይጨነቅም፣ አይረበሽም። እግዚአብሔር መልካሙንና የሚያስፈልገውን ሁሉ በስዓቱና በጊዜው እንደሚሰጠው ያውቃል ይረዳል። ሁሉን ነገር ለአምላኩ ያስረክባል፣ በእግዚአብሔርም እንደሚከናወንለትም ያምናል። ቅዱስ ዳዊት "እግዚአብሔርን ተስፋ አድርግ በርታ፥ ልብህም ይጽና እግዚአብሔርን ተስፋ አድርግ።" (መዝ 26፥14) ብሎ ማነን ተስፋ ማድረግ እንዳለብን ስላስተማረን እኛም ዛሬ በጉዟችን፣ በኑሯችንና በሕይወታችን ሁሉ እርሱን ተስፋ በማድረግ ምድራዊ ሰላምና ሰማያዊ ሕይወት ማግኘት እንድንችል መንፈሳዊ ተስፋ ሊኖረን ይገባል።

ሥጋዊ/አለማዊ ተስፋ፦
ይህ አይነቱ ተስፋ ለሥጋችን የሚያስፈልጉ ነገሮችን በብርቱ የምንመኝበት ነው። በዚህ የተስፋ ጉዞ ብዙ ነገሮች ተስፋ ቢስ ሊያደርጉን ይችላሉ። ነገር ግን ጽናትን፣ ብርታትንና ትዕግስትን ገንዘብ ካደረግን ተስፋችንን መመለስ እንችላለን። ምክንያቱም ሰው ካለ ተስፋ ለስዓታት መቆየት አይችልምና። የአደጉ አገሮች እራሳቸውን በማጥፋት የቀዳሚነቱን ቦታ ይዘዋል፤ ለዚህም አይነተኛውና ዋነኛው ምክንያት ተስፋ በመቁረጣቸው ነው፤ ለሰው ልጅ የሚያስፈልገው ሁሉ አላቸው ነገር ግን ተስፋ የሚያደርጉት ነገር የለም። ለእኛ ለታዳጊ አገሮች ግን ብዙ ነገሮች ተስፋ የምናደርጋቸው አሉን። ለምሳሌ፦ በፖለቲካው፣ በማህበራዊውና በኢኮኖሚው ዘርፍ ዘመናዊ ፖለቲካንና ዲሞክራሲን፣ የማህበረሰብ አንድነትንና ፍቅርን እንዲሁም አገራችን በሀብት አድጋ ከበለጸጉ አገሮች ጋር ተወዳድራ የማየት ተስፋ አለን። እነዚህና መሰል ነገሮች በተስፋ እንድንኖር ያደርገናል አድርጎናልም። ልክ ዛሬ እንደምናየው የእግር ኳስ ተስፋ፤ በኳስ በቅርብ ከአለም ጋር እንደምንቀላቀል ሙሉ ተስፋ አለን።
በአጠቃላይ መንፈሳዊም ሆነ ሥጋዊ ተስፋ ለሕይወታችን መሰረት ነው። ወደ ጥፋትና ኃጢአት ሊመራን የሚችል ተስፋም ስላለ ተስፋ ስለምናደርገው ነገር ቆም ብለን ልናጤነው ይገባል። እግዚአብሔር አምላክ ከኃጢአት በስተቀር ተስፋ የምናደርገውን ነገር በጸጋው ያድለን፡ አሜን!!!

No comments:

Post a Comment