Monday, September 30, 2013

400,000 ብር እና አዲስ ፕሬዝዳንት

በአዲስ ዓመት እንደ አገርም እንደ ግለሰብም አዲስ ሥራ ለመሥራት ይታቀዳል። በዚህ አመት ደግሞ ልዩ የሚያደርገው አገራችን ኢትዮጵያ ፕሬዝዳንታዊ "ምርጫ" (ምርጫ የሚለውን ቃል የተጠቀምኩት ሕገ መንግሥቱን ለማክበር እንደ ሆነ ይታወቅልኝ) የምታካሂድበት ጊዜ መሆኑ ነው። መንግሥት (አገራችን ብሎ ለመናገር አስቸጋሪ ስለሚሆን ነው) በሕገ መንግሥቱ መሰረት በየስድስት ዓመቱ የአዲስ ፕሬዝዳንት ምርጫ ያካሂዳል። በዚህ አመትም ክቡር ፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ የ12 አመት የፕሬዝዳትነት ስልጣናቸውን የሚለቁበት ጊዜ ነው። ከዚሁ ጋር ተያይዞ 2 አነጋጋሪ ጉዳዮች ጎልተው ወጥተዋል።

1. ቀጣይ አገሪቱን በፕሬዝዳትነት ማን ይምራት

 ለአገራችን እድገትና ሰላም የሚያስቡና የሚቆረቆሩ ምሁራን በተለያየ መልኩ አገሪቱን ማን ቢመራት የተሻለ ሊሆን ይችላል ብለው ሃሳባቸውን በማካፈል ላይ ይገኛሉ። ከእነዚህም መካከል በኖርዎይ ኦስሎ, ዩኒቨርስቲ መምህር የሆኑት ረዳት ፕሮፌሴር ተክሉ አባተ በጡመራ ድረ ገጻቸው ላይ ሃሳባቸውን አስቀምጠዋል።

በአንድም በሌላም አገራችንን የተሻለ ሰው ቢመራት የሁሉም ኢትዮጵያዊ ምኞት ነው። ነገር ግን ማነው የተሻለውን ሰው በፕሬዝዳንትነት ቦታ ላይ እንዲቀመጥ ማድረግ የሚችል የሚለው ትልቁ ጥያቄ ነው፤ በሌላ በኩል ደግሞ መቀመጥ ቢችልስ አቅሙንና እውቀቱን ተጠቅሞ መስራት የሚችልበት ከባቢያዊ አየር አለ ወይ ነው። በግልጽ ቋንቋ መንግሥት እንዲህ አይነት ሰዎችን ይፈልጋል ወይ የሚለው የሁላችንም ገሃዳዊ ጥያቃችን ነው።

ስለ አዲስ ፕሬዝዳንት ስናነሳ በስፖርቱ አለም ታዋቂነትን ያተረፈውና አገራችን ኢትዮጵያን ለአለም ስሟን ያስተዋወቀው አንበሳው ኃይሌ ገ/ስላሴ በምርጫው እንደሚሳተፍ የተገለጸበት ሌላው ትልቁ ወቅታዊ ጉዳይ ነው።



ኃይሌ ገ/ስላሴ Google pic

ኃይሌ ገ/ስላሴ በህብረተሰቡ በኩል ትልቅ ቦታና ክብር ያለው ሰው እንደ መሆኑ መጠን በዚህ ምርጫ የሚሳተፍ ከሆነ ብዙ ነገሮችን መመልከትና መወሰን ይኖርበታል።

  1. የመንግሥትንና የህብረተሰቡን የአንድነት ሁኔታ
  2. የመንግሥትን ምንነት(እውቀቱንና ስልጣኑን በነጻነት መጠቀም መቻሉን)
  3. በመንግሥትና በተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል ያለውን ልዩነት
  4. በመንግሥትና ውጭ በሚኖሩ ኢትዮጵያውን መካከል ያለውን ልዩነት
  5. ለቀጣይ 6 ወይም 12 አመት አገሪቱን በፕሬዝዳትነት ለመምራት የሚያስችል በቂ እውቀት መኖሩን ...ወዘተ
ወደ ምርጫ ከመግባቱ በፊት እነዚህንና መሰል ነገሮችን በሚገባ ማጤን ይኖርበታል። ነገሮችን ሳይመለከት ቢገባ ግን ክብሩንና የወደፊት ጉዞውን በቀላሉ ሊያጣ እንደሚችል መገመት አያዳግትም። ምክንያቱም የአገራችን መንግሥት በህብረተሰቡ ዘንድ በተለያየ መልኩ ተቀባይነቱ በእጅጉ የቀነሰበት ሁኔታ ላይ በመሆኑ የኃይሌንም የወደፊት ጉዞ አስቸጋሪ እንዳያደርግበት የብዙዎች ሃሳብ ነው።

2. የክቡር ፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ የወደፊት የኑሮ ሁኔታ




የክቡር ፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ የወደፊት ሕይወት ነው። ከኃላፊነት የተነሱት የአገርና የመንግሥት መሪዎች፣ ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች፣ የምክር ቤት አባላትና ዳኞች የሚያገኙዋቸውን መብቶችና ጥቅሞች ለመወሰን መንግሥት ባወጣው አዋጅ መሰረት ለተሰናባቹ ፕሬዚዳንት ቤት በወር 400,000 ብር መከራየቱን ጠቅሳል፡፡ ይህ ከፍተኛ የቤት ኪራይ ወጪ ግን ከአገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ ሲገናዘብ ለማመንና ለመቀበል አስቸጋሪ ነው። እኔ ግን ትልቅ ጥያቄ የፈጠረብኝ መንግሥት ለፕሬዝዳንቱ የተከራየው ቤት መኖርያ ወይስ የንግድ የሚለው ነውና ደሞዛቸውስ ስንት ነበር የሚለው ነው። መኖርያ ቤት እንደሆነ ደግሞ ተገልጾልናል፤ ነገር ግን መኖርያ ቤት ይህን ያክል ወጪ እንዴት ሊያወጣ ቻለ የሚለው የብዙዎችን ትኩረት ስቧል።
ስለዚህ አገሪቱ ለአንድ ከኃላፊነት ለለቀቀ ባለስልጣን ለቤት ኪራይ፣ ለመኪና፣ ለሰራተኛ፣ለህክምና ሌሎች ጥቅማ ጥቅሞችን ጨምሮ ከፍተኛ ገንዘብ በወር ወጪ ታደርጋለች ማለት ነው። ይህን ጉዳይ መንግሥት ለአገራችን በምን ያክል መጠን እንደሚያስብ በጥልቀት ለመረዳት በጎ አጋጣሚ ፈጥሮልናል።
በዚህ ዙርያ የእኔ ሃሳብ ይህን ያክል የአገሪቱን ገንዘብ ወጪ ከማድረግ ይልቅ መንግሥት ከኃላፊነት ለሚለቁ ከፍተኛ ኃላፊዎች የሚሆን ቤት ቢያስገነባ የተሻለ ይሆናል። ምክንያቱም የሚገነባዉ ቤት ለወደፊት የአገሪቱ ቋሚ ንብረት ይሆናል፤ ከዚያም በላይ ለኪራይ በየወሩ የሚወጣውን ከፍተኛ ገንዘብ ይቀንሳል።



No comments:

Post a Comment