Tuesday, September 10, 2013

አዲስ ዓመት፣ አዲስ ዕቅድ

በየአመቱ አዲስ ዓመት በመጣ ቁጥር ከእንኳን አደረሳችሁ የመልካም ምኞት ቀጥለን በአዲስ ዓመት ዕቅድህ/ሽ ምንድን ነው? የሚለው የተለመደ ጥያቄ ነው። መልሳችንም እንደ ሥራ መስካችንና አመለካከታችን የተለየ መልክና ይዘት ይኖረዋል። በአዲስ ዓመት በት/ት ገበታ ላይ የሚገኙ ሁሉ ጥሩ ውጤት ማስመስገብን፣ አርሶ አደሮች ጥሩ ምርት ማምረትን፣ በንግዱ ዓለም የሚገኙ ትርፋማነትን፣ ማኅበርተኞች የማኅበራቸውን ዓላማና ግብ መሳካትን፣ ፖለቲከኞች መልካም አስተዳደርንና የተቀናቃኛቸውን ክስረት፣ መንግሥት የስልጣን ዘመን ማራዘሚያ መንገዶችን እና ሰራተኞች የደሞዝ ጭማሪን/ትምህርትን  በአጽንኦት ይሻሉ ይመኛሉ።
አሁን  በአለንበት ዘመን  ምኞታችንን  ሁሉ እውን  ለማድረግ በእጅጉ ከባድ ነው። ሆኖም ግን ልናተኩርባቸው  የሚገቡ ነገሮችን ለይቶ  ለስኬት የሚያበቃንን መንገድ መከተል  ብልህነት ነው። በአጭር ከዚህ በታች ልናተኩርባቸው የሚገቡ ነገሮችን ለመነሻ ያክል ጥቂት ልበል።

እንደ  ክርስቲያን በአዲሱ ዓመት ልናተኩርባቸው የሚገቡ፦
  • ከበፊቱ በበለጠ ከጠላታችን ዲያቢሎስ ጋር የምንዋጋበትን እቃ ጦር ለመልበስ ታጥቀን የምንነሳበት፣ 
  • ቤተ ክርስቲያንን ከበፊቱ በበለጠ ልናገለግልና ልንገለገልባት በጽዕኑ ዓላማ ቆርጠን የምንነሳበት፣
  • ቤተ ክርስቲያን የሁከት፣ ፀረ ሰላም፣ ፀረ ልማት እንዳይደለችና የሰላም፣ የፍቅር፣ የአንድነት ት/ቤት እንደሆነች በኩራት የምንመሰክርበትና የምንገልጽበት፣ 
  • ቤተ ክርስቲያን አክራሪነትን የምትቃወም እንጂ አክራሪነት የሚለው ቃል ፈጽሞ ሊሰጣት እንደማይገባ በድፍረት የምንመሰክርበት፣ 
  • ከሰዎች ጋር መታረቅና ፍቅርን በስጦታ መልክ መለገስ፣
  • ሰውነታችንን በንስሃ ታጥበን በአምላክ ቅዱስ ሥጋና ክብር ደም ታትመን አዲስ ሕይወትና አዲስ መንፈስ የምንይዝበት ዘምን እንዲሆን ይፈለጋል።
እንደ  መንግሥት በአዲስ ዓመት፦
  • መልካም አስተዳደር ለማስፈን መጣር፣
  • ሕግን ከወረቀት ባለፈ በተግባር ማዋል፣
  • የህዝቡን ብሶት ሰምቶ ለችግሩ ደራሽ መሆን፣
  • አገራዊ ስሜትን ለህብረተሰቡ ማስገንዘብ፣
  • ለዲሞክራሲ ግንባታና ለአገራዊ እድገት የሚጥሩ ተቀናቃኝ/ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ማበረታታት፣
  • በሃይማኖት ጣልቃ ገብነትን ማቆም፣
  • ለሰባዊ መብት ተቆርቋሪ መሆን፣
  • ከአላግባብ የታሰሩ እስረኞችን መፍታት፣
  • ትክክለኛ መረጃ ሳይኖር ሰዎችን፣ድርጅቶችንና ተቋማትን  ያልሆነ ስም ሰጥቶ ማሸማቀቅን ማቆም፣
  • ስልጣን የህዝብ መሆኑን በተግባር ማሳየት እና መሰል ተግባሮችን የሚተገብርበት ዘምን እንዲሆን ይፈለጋል። 
እንደ ሰራተኛ በአዲስ ዓመት፦
  • ለሌላ ሁለተኛ ወይም ሦስተኛ አካል ሳይሆን ለህሊና መስራት፣
  • በማነኛውም የሥራ መስክ ህዝብን እንደምናገለግል  በሚገባ መገንዘብ፣
  • ለሕገ መንግሥት ብቻ ሳይሆን ለሕገ አምላክም መገዛት፣
  • ማጭበርበር፣ ሙስና እና ጥቅመኝነትን አምርሮ  መጥላትና ማጋለጥ፣
  • ፍቅርን  በስጦታ መልክ ለሰዎች መለገስ፣
  • በማነኛውም መልኩ ለእውነት ለመስራት እራስን ዝግጁ ማድረግ ይገባል።
እንደ መንግሥት ተቃዋሚ ፓርቲ በአዲሱ ዓመት፦
  • ለህዝብና ለሃገር መቆማችሁን በትክክል ሊያስረዳ  በሚችል መልኩ ዓላማችሁን መግለጽ፣
  • የመንግሥት አካላትን በፖሊሲና በዓላማ እንጂ  በማንነታቸው አለመተቸት፣
  • ማንኛውንም ድርጅት ወይም ተቋም ለፖለቲካ ቅስቀሳ አለመጠቀም፣
  • ስድብንና ዛቻን ትቶ ሙህራዊ የአነጋገር ዘይቤ መጠቀም፣
  • ድርጅታችሁ ከብሔር ይልቅ  አገራዊ እንዲሆን  ማድረግ፣
  • የመንግሥትን  መልካም ሥራዎች ካሉ ማበረታታትና መደገፍ፣
  • ለዲሞክራሲ፣ ለሰላምና ለአድነት ቆርጦ መነሳት ከእናተ በአዲስ ዓመት ይጠበቃል
ሁላችንም 2006 ዓምን እነዚህንና ሌሎች አስፈላጊ ተግባራትን ለመተግበር አቅደን አዲሱን ዓመት መቀበል ይገባናል።   

ዘመነ ማርቆስ/2006 ዓም የሰላም፣ የፍቅር፣ የደስታ፣ የአንድነት፣ የሕይወት ብልጽግና   እንዲሆንልን አምላከ ቅዱሳን በቸርነቱ  ይርዳን፡አሜን!።

No comments:

Post a Comment