Tuesday, September 3, 2013

የሃማኖት ተቋማት ጉባኤ ሰላማዊ ሰልፍ ጥሪ አስፈላጊ ነበር???

ይህ ጉባኤ በዋናነት የተቋቋመው ለአገር ሰላምና በእምነት ተቋማቸው ለሚያስተዳድሩት ህብረተሰብ(የእምነት ተቋም) ደህንነት እንጂ ለመንግሥት ወይም ለአንድ የፖለቲካ ድርጅት አይደለም። በተለይ ደግሞ ይህ ጉባኤ በእምነት ተቋማት መካከል አለመግባባት እንዳይፈጠር እና ወደ አልተፈለገ ግጭት/እሰጣ ገባ/ ውስጥ እንዳይገባ ሁሉም የየራሱን የሃይማኖት አስተምሮ በመቻቻል እንዲሁም ሰላምና ፍቅር በተሞላበት መንገድ እንዲያካሂዱ ለማድረግ የተቋቋመ ይመስለኛል።
በትናትናው እሁድ ማለትም በ26/12/2005 ዓም የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ግን ከዓላማው በእጅጉ የራቀ እና ሁኔታዎችን ያላገናዘበ መስሎ ይታያል። እርግጥ ነው ይህ ጉባኤ አገራዊ ሰላም ሊያደፈርሱ ይችላሉ ብሎ ያመነባቸውን ጉዳዮች ለህዝብ ይፋ ማድረጉ የሚበረታታና ለወደፊትም ሊቀጠልበት የሚገባ ተግባር ነው። ነገር ግን ይፋ ከማድረጉ በፊት የሃይማኖት ኮሚቴ እንደመሆኑ መጠን በርካታ ቅድመ ስራዎች ሊኖሩት ይገባል። የህብረተሰቡን ነባራዊ ሁኔታ፣ የእምነት ተቋማት አመለካከትና የፖለቲካ አቅጣጫን በሚገባ ማጤን ከዚህ ትልቅ ከሚቴ ቀርቶ ከአንድ ግለሰብ ሊሰወር የማይገባ ነገር ነው።
የህብረተሰቡን ነባራዊ ሁኔታ በትክክል መገንዘብ ያስፈልጋል ሲባል የተፈጠረውን ችግር ህብረተሰቡ በምን መልኩ ነው የተረዳዉ፣ ሰላማዊ ሰልፍ ሊያስወጣ በሚችል መልኩ ነው? ውይስ የግንዛቤ እጥረት አለበት? ወይስ በሌላ አቅጣጫ ነው የተረዳው? የሰላማዊ ሰልፍ አስፈላጊነት? እና መሰል ጥያቄዎችን በማንሳት ህብረተሰቡ ያላበትን የግንዛቤ ደረጃ መለካት፣ ማጤንና መመልከት ይገባል። እንዲሁም ህብረተሰቡን ግንዛቤ ከማስጨበጥ አንጻርም ይህ ኮሚቴ ትልቅ ኃላፊነት አለበት። ሰላማዊ ሰልፍ ወይም ውሳኔ ከመወሰኑ በፊት የችግሩን አሳሳቢነት ማለትም በአገርና በሃይማኖት ተቋማት ላይ ሊያመጣ የሚችለውን ችግር በሚገባ በተለያየ መልኩ ማስረዳትና ማሳወቅ፣ መግለጽና ማስተላለፍ ይኖርበታል። ምናልባት ኮሚቴው ይህን አድርጊያለሁ ቢልም በቂ ነው ብዬ አላምንም። በዚህ መልኩ ህብረተሰቡን ማንቃትና ወደ አንድ የግንዛቤ መንፈስ እንዲመጣ ሳያደርጉ ውሳኔ መወሰን ይባስ ብሎ አገራዊ ሰላማዊ ሰልፍ መጥራት ከጥቅሙ ጉዳቱ እጅግ የከፋ ይሆናል።
የእምነት ተቋማት አመለካከት ምን ይመስላል የሚለውንም በሚገባ መረዳት የኮሚቴው ተቀዳሚ ተግባር ነው። የዚህን ኮሚቴ የእያንዳንዱ አባል የወከለው የእምነት ተቋሙ ነው። ስለዚህ ከእምነት ተቋሙ ጋር መነጋገር፣ መወያየት፣ የችግሩን አመጣጥና ሁኔታ፣ በተቋሙ ላይ ሊያስከትለው የሚችለውን ችግር በሚገባ ማየትና ተደጋጋሚ ውይይቶች ያስፈልጋሉ። ችግሩ ተፈጠረ ከተባለበት ተቋም ወይም ቦታ ድረስ በመሄድ ችግሩን በውውይት ለመፍታት መሞከር ይኖርበታል። በእኔ አመለካከት የሃይማኖት ተቋማት ከመንግሥትም በላይ ለሰላምና ለህብረተሰቡ ደህንነት የሚቆሙ ናቸው። ስለዚህ ችግሩን በውይይት፣ በትምህርትና በተግሳጽ ለመፍታት መጣር ያስፈልጋል። ኮሚቴው እንደኮሚቴ ከመወሰኑ በፊት ከወከለው የእምነት ተቋም ጋር ግልጽ ውይይት አድርጎ ችግሩን ሊፈታ በሚችል መልኩ አንድ አቋም መያዝ ይኖርበታል። በእውነት የትናቱ ሰላማዊ ሰልፍ ግን የተፈጠረውን ችግር ሊፈታ ይችል ነበር??? መልሱን ለእናንተ ትቸዋለሁ።
ይህ ኮሚቴ ከፖለቲካ ነጻ እንደመሆኑ መጠን / በወረቀት ደረጃ ማለቴ ነው/ አንድ ውሳኔ በሚወስንበት ጊዜ የፖለቲካ አቅጣጫውን መመልከት ያስፈልገዋል። ምንም እንኳ ሃይማኖትና መንግሥት የተለያዩ ናቸው ቢባልም መንግሥት ከሃይማኖት ነጻ ሁኖ ስለማያውቅ አቅጣጫውን እና ሂደቱን ከውሳኔ በፊት መረጃዎችን መሰብሰብና መፈተሽ ያስፈልጋል። የህብረተሰቡ የፖለቲካ አመለካከት ምን ይመስላል? የገዢው ፓርቲ ያለበት ደረጃ? የተቀዋሚ የፖለቲካ እንቅስቃሴና ሌሎችንም ተያያዝ ነገሮችን መፈተሽ ይኖርበታል። እነዚህ ሁኔታወችን ሳይገነዘብ ወደ ውሳኔ ከገባ ግን በአንድ ተጽዕኖ ውስጥ ሊገባ ይችላል፤ ይኸው ገባም። የሃይማኖት ተቋም የሰላም ኮሚቴ ተብሎ በአንድ ተጽዕኖ ውስጥ ዥው ብሎ መግባት ግን ችግሩ እንዲበባስ ያደርገዋል፤ በተጫማሪም ሌላ ችግር ይፈጥራል እንጂ መፍትሔ ሊያመጣ አይችልም።
ጉባኤው መመልከት ያልቻላቸው ግልጽ ነገሮች፦
1. ችግሩን፦ ጉባኤው በአዲስ አበባ በ10 ክፍለ ከተሞችና በ116 ወረዳዎች በተካሄደው ህዝባዊ የሰላም ኮንፈረንስ እንዲሁም ከፍትህ ቢሮ ጋር በመተባበር ከነሐሴ 15-16 በተካሄደው የሰላም ኮንፈረንስ ላይ የሃይማኖት መሪዎችና ተከታዮቻቸው «ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በከተማችን እየታየ ያለው የአክራሪነትና የፅንፈኝነት እንቅስቃሴ የሀገራችንን ሰላምና ልማት የሚያውክ፣ በሰላም አብሮ የመኖር እሴቶቻችንን የሚያናጋና የሃይማኖት መልክ የሌለው የጥፋት እንቅስቃሴ ከመሆኑም በላይ በህገ መንግሥታችን የተደነገገውን የሃይማኖት እኩልነትና የእምነት ነፃነት የሚፃረር ስለሆነ በሰላማዊ ሰልፍ ተቃውሟችንን ማሰማት እንፈልጋለን» ተብሎ በአቋም መግለጫ የተላለፈውን መሰረት በማድረግ ሰልፉ እንደተዘጋጀ በጋዜጣዊ መግለጫ ስለሰልፉ አስፈላጊነትም በማብራራት ሰላማዊ ሰልፉ በመጪው እሁድ ከንጋቱ 12 ሰዓት በመስቀል አደባባይ የሚካሄድ ሲሆን፤ በከተማው ውስጥ ያሉ የሃይማኖት ተቋማት በሙሉ በጋራ በመሆን ለሰላም፣ ለልማት፣ ለመቻቻልና ለአብሮነት ያላቸውን ቁርጠኝነት የሚገልጹበት የሰላም መድረክ ነው//፤ በማለት የጉባኤው ኮሚቴ በገለጸልን መልኩ ችግሩን ሙሉ በሙሉ እንውሰደው ብንል እንኳ የሃይማኖት አክራሪነት ከመቼ ወዲህ ነው በሰላማዊ ሰልፍ ሊገታ የሚችለው። ኃያላን አገራት እንኳ በተደራጀና ዘመናዊ ስልትን በመጠቀም አክራሪነትን ማቆም ሳይችሉ እኛ እንዴት ነው በሰላማዊ ሰልፍ ልናቆመው የምንችለው። እንደ አገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ሰላማዊ ሰልፍ ለሰላማዊ ትግልም ልንጠቀምበት አልታደልንም። ስለዚህ ጉባኤው የሃይማኖት አክራሪነትን በሰላማዊ ሰልፍ ለመግታት መሞከሩ የችግሩን ምንነት አለመረዳት ነው። ችግሩን በሚገባ ሳይረዱ ደግሞ ውሳኔ መወሰኑ ከመፍትሔው ይልቅ ጉዳቱ እንደሚያመዝን ብዙ መናገር የሚያስፈልግ አይመስለኝም። ችግሩም መቶ ፐርሰንት/100%/ አክራሪነት ነው ብሎ ለመፈረጅ ማስረጃ የሚያጥር ይመስለኛል። በግሌ አክራሪነት የለም፣ አይኖርም የሚል አመለካከትና ግንዛቤ የለኝም። ቢሆንም ግን በሰላማዊ ሰልፍ ከችግሩ እንወጣለን የሚል እምነት ፍጽሞ አይኖረኝም።
2. ስዓት፦ ሰላማዊ ሰልፉ እንዲጀመር የተደረገበትን ስዓት እንኳን ስንመለከተው ጉባኤው ከወከለዉ የእምነት ተቋም ጋር ጥብቅ ውይይት አለማድረጉን በቀላሉ መመልከት እንችላለን። በተለይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ያን እና ሌሎችም ማለት ይቻላል በየሳምንቱ እሁድ ጥዋት የአምልኮት ስርዓታቸውን የሚፈጽሙበት ስዓት ነው። ስለዚህ ስዓቱን እንኳ ያገናዘበ ሰላማዊ ሰልፍ አለመጥራት የግደለሽነት ያስመስላል። ወይም በሌላ ተጽዕኖ ውስጥ መሆኑን በግልጽ ለመረዳት አያዳግትም። በተጽዕኖዎችና በግደለሽነት የሚደረጉ ማንኛውም ነገሮች ደግሞ ችግርፈጣሪ እንጂ ችግር ፈቺ መቸውንም አይሆኑም።
3. ቀን፦ በሰላማዊ ሰልፉ አስፈላጊነት ጉባኤው ካመነ በቀላሉ ሊመለከተው የሚገባው ነገር የሚደረግበትን ቀን ነው። በዚያ ቀን ምን ተያያዥ ነገር አለ? ቀኑ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል፣ ለእምነት ተቋማትና ለፖለቲካ ፓርቲዎች ምቹ ነው? የሚለውን ጥያቄ ጉባኤው ከመወሰኑ በፊት መመልከት ይኖርበት ነበር። ጉባኤው ግን በተቃራኒው የተጓዘ ይመስላል። ይህ ቀን ማለትም 26/12/2005 ዓ.ም ግን ሰማያዊ ፓርቲ የአገር ሰላም እንዲሰፍን፣ ሰባአዊ መብት እንዲከበር፣ ዲሞክራሲ እንዲሰፍን፣ ከአላግባብ የታሰሩ ዜጎች እንዲፈቱ፣ እኩልነት እንዲረጋገጥ፣ ሙስናና አገርን ወደ ኋላ ሊጎትቱ የሚችሉ ችግሮችን ለመቅረፍና ለህብረተሰቡ ግንዛቤ ለመፍጠር ከመንግሥት እንኳ ሳይቀር ፍቃድ ጠይቆ ለ2ተኛ ጊዜ ሰላማዊ ሰልፍ የጠራበት ቀን ነበር። ጉባኤው ግን ይህን ሳያገናዝብ በመጥራቱ ለፓርቲው አባላት እስራት፣ እንግልትና ድብደባ ምክንያት ሁኗል። ፓርቲው የጠራው ሰላማዊ ሰልፍም በእስራትና በድብደባ እንዲቀየር አድርጎታል። ሙሉ በሙሉ ጥፋቱ የመንግሥት ቢሆንም የጉባኤው አባላት ለዚህ ተግባር ተባባሪ በመሆናቸው ተጥያቂ አድርጓቸዋል። ሌሎችን እናተ ጨምሩበት.......
በአጠቃላይ የጉባኤው ሰላማዊ ሰልፍ ጥሪ አስፈላጊ ነበር የሚለውን ሁላችንም በራሳችን አስተያየት እንስጥበት እና እንማርበት። አስፈላጊ አልነበረም ለምንል ሰዎች ወደፊት እንዲህ አይነት ተያያዥ ክስተቶች እንዳይፈጠሩ ምን እናድርግ ለማለት ሃሳብ መለዋወጡ መልካም ስለሚሆን ለመነሻ ያክል የግሌን ሃሳብ አቅርቢያለሁ።

No comments:

Post a Comment