Saturday, September 14, 2013

ሰው እና ሕገ ሕሊና/ተፈጥሯዊ ሕግ

ሰው ማነው? ብሎ ለጠየቀ “ሰው ንግግሩን ይመስላል” እንዳትለኝ ንግግሩ እምነቱንና ሃሳቡን ሙሉ በሙሉ የሚያመለክት ዕውቀት አይሆነውምና ነው፡፡ በተለይ ከዘመኑ ድርጊታችን ስንመለከተው ንግግራችን እና ድርጊታችን ፍጹም ተቃራኒ ሁኖ እናገኘዋለን። ለሰው ባሕርያዊ ተፈጥሮና ዕውቀት ምስክሩ ውስጣዊ የአዕምሮ አቋምና የሕሊና ሕግ ነው ብለንም አንደመድምም፡፡ ሰው እንዲያውቅ የተመደበለት የሕግ ተፈጥሮ ዕውቀት መጀመሪያ ክፍል መልካምን ማወቅ፡፡ ሁለተኛ ክፋትን ንቆ መልካምን ገንዘብ ማድረግ፡፡ ሦስተኛ መልካምን በግብር መግለጽ ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቱያን ሊቃውንት ይሁዳን ሲገልጹ “በአፍ አምኖ በልቡ የካደ” ይሉታል፡፡ ባህላችን “አፈ ቅቤ፤ ሆደ ጩቤ” እንዲል፡፡ ይሁዳ በጊዜያዊ ጥቅም ተታሎ ለሕሊናው መገዛት ስላልቻለ አምላክን ያህል ጌታ ለሞትና ለስቅላት አሳልፎ ሸጠ። ከሐዋርያት ማኅበርም በእራሱ ድርጊት ተለየ።
የክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር መሠረት ሕገ ልቦና/ሕሊና ስንል ያለ ትምህረት በተፈጥሮ የሚሰጥ ሲሆን ይህም ሕገ ልቦና፤ ሕገ ህሊና፤ ሕገ ተፈጥሮ ወይንም ሕገ ጠብዓያዊ በመባል ይታወቃል፡፡ ሕገ ኦሪትና ሕገ ወንጌል፤ ሕገ ሕሊናን ይተረጉማሉ፡፡ ለአብነት ብንጠቅስ አዳምና ሔዋን ቅዱስ ዳዊትትን፣ ቅዱስ ጴጥሮስንና ይሁዳን፤ ከመጸጸት ክፉዎችን ከማዘን የምታደርሳቸው የሕሊና ኮሽታ ነች፡፡ በኑሮ ሂደት ሀዘን፣ ጸጸት ርትዕ በምናደርግበት ጊዜ ልዩ መንፈሳዊ ጥበብ አልያም ዕውቀት በመታደል ሳይሆን ሰው በመሆናችን በሕሊና ውስጥ የተቀረጸ በህሊና ሚዛን የሚሰጥ ፍርድ በመኖሩ ነው፡፡ ለምሳሌ አብርሃምን ስንመለከት ምንም የተጻፈ ሕግ፣ ሰባኪና መምህር ባልነበረበት ወቅት በሕገ ልቦና/ሕሊና ተመርቶና ተመራምሮ ከእግዚአብሔር ጋር ለመነጋገር ችሏል። አባቱ ታራ ይከተለው የነበረው መንገድ እጅግ ስህተት መሆኑን ተረዳ። ለከዚህም በተጨማሪ ሕገ ሕሊና በጽሑፍ ከተሰጡን ሕግጋት /ሕገ ኦሪት፣ ሕገ ወንጌል፣ ማሕበራዊ ሕግ/ በላይ ሰማያዊና ምስጢርን ለመጠበቅ ሲያገለግል እናገኘዋለን፡፡ የቤተ ክርስቲያን የሀገር የግል ምስጢር ይጠበቅ ዘንድ መንፈሳዊ ሕግና ማህበረሰባዊ ሕግ ይደነግጋል፡፡ የአምላክ እናት ድንግል ማርያም ያለ ምድራዊ ሕግ አስገዳጅነት በሕገ ልቦና ዳኝነት ለሰማያዊ ምስጢር የታመነች ነበረች “እናቱ ማርያም በልቧ ትጠብቀው ነበር” እንዲል፡፡ /ሉቃ.2÷19/፡፡
“ሰው ራሱ መጽሐፍ ነው” የሚለው የአነጋገር ስልት የሚያስተላልፈው ሰው ይነበባል፤ ይጠናል፤ ይተነተናል፤ ይጸድቃል፤ ይሻራል ለማለት ነው፡፡ ከሌሎች ሥነ ፍጥረታት በላይም አስተማሪና ሚስጢራዊ ነው። እነዚህን ተግባራት ለሌሎችም ሆነ ለራሳችን ለድርጊታችን ብያኔ ፍርድ ለመስጠት ረቂቅ የሕሊና ልጓም እንደ መሠረት ሆኖ ያገለግላል፡፡ ሰው በውስጡ የሚያረጋግጣት እውነት በክበበ አዕምሮ በሚጨበጥ ሕገ ባሕርይ ከመገለፅ እምቢ አትልም፡፡ እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት እምነት በቅድሚያ እንዲገኝ ግድ ቢሆንም በተግባር ወይንም በድርጊት ካልተዋሃደ ክርስቲያናዊ ሕይወታችን ፍሬ ቢስ፤ ረብ የሌለው ከንቱ ድካም ይሆናል፡፡ ለመሆኑ እምነታችን ከድርጊታችን ለምን ተዛነፈ? በጽናት የምናምነውን እምነት አጥቦ የመውሰድ ብቃት ያለው ሃይል ይኖር ይሆን? በዕለት ተዕለት ማኅበራዊ መስተጋብር የምንወስናቸው መጠነ ሰፊ ጥቃቅን ውሳኔዎች ውህደ ሃይማኖት ምግባር የታሹ ወይስ የስሜት ውጤቶች ናቸው? እርግጥ ነው ስሜት አልባ ሰብአዊ ፍጡር ሊሆን አይችልም፡፡ 
ነገር ግን ነፍስን ደስ የሚያሰኝ ሰማያዊ እውነት ከስሜት በላይ ነው፡፡ እውነት ደግሞ በሕገ ሕሊና ያለ አምላካዊ ሕግ ነው። ሕጉን ያለመፈጸም እንጂ መካድ አይቻልም ምክንያቱም ተፈጥሮአዊ ሕግ ነውና። ሰው ድርጊቱን ምክንያታዊ ቢያደርገውም እውነቱን ግን በትክክል ሕሊናው ይነግረዋል። ከሰው ሊሰወር ይችላል ከሕሊናው ግን መሰወር አይችልም። ብዙ ሰዎች ትክክል ያልሆነ ድርጊት ለመፈጸም ከአሰቡበት ጊዜ ጀምሮ ከራሳቸው ጋር ይሟገታሉ፤ ልፈጽመው ወይስ ይቅርብኝ በማለት። እውነቱንና ትክክለኛውን መንገድ ግን ሕሊናቸው በተለያየ መንገድ ያሳውቃቸዋል። ቅዱስ ጳውሎ እንደተናገረው "እነርሱም ሕሊናቸው ሲመሰክርላቸው፥ አሳባቸውም እርስ በርሳቸው ሲካሰስ ወይም ሲያመካኝ በልባቸው የተጻፈውን የሕግ ሥራ ያሳያሉ።"(ሮሜ 2፥15)
በገሃዱ ዓለም በብዙዎቻችን ሕይወት የሚታየው ውሳኔዎቻችን በድካም ባካበትነው ዕውቀት፤ መንፈሳዊ አስተምህሮ፤ ዓለማዊ ጥበብ፤ የቅዱሳን ሕይወት ሳይሆን ለስሜት ያጋደለ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ለሁለት ጌታ መገዛት አይቻልም የሚለውን ኃይለ ቃል ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተማረው ይሁዳ ለ30 ብር ሸጦታል ለምን ትለኝ እንደሆን ሰው ክፉን ነገር እስኪሰራ ሰው ልበ ሙሉ ይሆናልና ነው፡፡ ሁለተኛው የህሊና ዓይን ከነፍስ ባይለይም በኃጢአት ምክንያት ይጨልማል ይደክማልና ነው፡፡ በአጭር አገላለጽ ድርጊታችንን የሚቆጣጠረው በዕለቱ ስሜታችንን ያቀጣጠለው ኃይል እንጂ በጥረት ያካበትነው ትምህርት ወይም ዕውቀት ሆኖ አይታይም፡፡
ሰው በሕገ ሕሊና፣ በሕገ ኦሪት፣ በሕገ ወንጌልና በሕገ ማህበራዊ መገዛቱን ትቶ በጊዜአዊ ስሜት ለጥቅምና ለስልጣን፣ ለክብርና ለእይታ ማደር ከጀመረ ለአገርም፣ ለቤተሰቡም ለራሱም ሳይሆን በቅዠትና በሰላም እጦት ሕይወቱ እንዲሁ ያልፋል። ሰው ሆይ ከምንም በላይ ለተፈጥሮአዊ ሕግ ተገዢ ሁን፤ ሕሊናህ ይዳኝህ፤ ለመልካም ነገር ትጋ፤ እምነትና በጎ ሕሊና ይኑርህ!!!  

ምንጭ፦ ማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ (ሚያዝያ 26፣2003ዓ.ም)

No comments:

Post a Comment