Monday, November 11, 2013

ነጻነት ወይስ ቅኝ ግዛት/ባርነት

ቅኝ ግዛት ማለት የአንድ ሃገር ህዝቦች የሌላውን ሃገር ህዝቦች በቁጥጥር ስር በማዋል የሚደረግ ግዛትን የማስፋፋት ስርዓት ነው። በዋናነት ቅኝ ግዛት የሚገልጸው ከ15ኛው እስከ 20ኛ ክ/ዘመን ያለውን የአውሮፓ ሀገሮች የአፍሪካን፣ ሰሜን አሜሪካን እና የእስያ ሃገሮችን የተቆጣጠሩበትን ዘመን ነው። በዚያ ዘመን ቅኝ ገዥዎች በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ኢትዮጵያን የራሳቸው ግዛት ለማድረግ መጠነ ሰፊ ሙከራ አድርገዋል። ለምሳሌ፦
ከ1521_1535 ግራኝ መሐመድ በቱርኮች እገዛ ያደረገው ጦርነት
ከ1824_1832 የግብጦች ተደጋጋሚ ወረራ /በባሕረ ነጋሽ እንዲሁም በ1867_68 ጉንዳጉንዲትና ጉራዕ ላይ
በ1877 ከደርቡሾች ጋር በተካሄደው እልህ አስጨራሽ ጦርነት ኢትዮጵያውያን አርበኞች ድል ነስተው ሰንደቃላማ ከፍ አድርገው አውለብልበዋል።
እንዲሁም ምዕራባውያን የውርደት ካባ የተከናነቡበትን የ1896 የአድዋ፣ የ1928_1935 የነበረውን የኢጣሊያ ጦርነት በቃላት መግለጽ ከምንችለው በላይ ጀግኖች አባቶቻችን ደማቸውን አፍስሰው፣ አጥንታቸውን ከስክሰው በአሸናፊነት ከእነሙሉ ክብሯ አገራቸውን ለትውልድ ማስተላለፋቸው ኢትዮጵያ አገራችን ለአፍሪካውያን የነጻነት ምሳሌ ለምዕራባውያን ደግሞ የውርደት ካባ ያከናነበች መሆኗን በታሪክ ትጠቀሳለች። በዚህ ምክንያት ዛሬ እኛም ስለ አገራችን መናገር ስንጀምር በቅኝ ግዛት ያልወደቀች ብቸኛ አፍርካዊት አገር ብለን ለንግግራችን መግቢያ እናደርገዋለን። በመቀጠልም የራሷ ያልተከለሰ ቋንቋ፣ ባህል፣ እምነትና ታሪክ ያላት ብለን አፋችንን ሞልተን እንናገራለን።
የጽሁፌ መነሻ ግን በተለያየ መልኩ ስለምናውቀው የቅኝ ግዛት ታሪክ መተረክ አይደለም። በዚህ ዙርያ በርካታ የታሪክ ሙህራን በስፋት መዝግበው አስቀምጠውልናል። ነገር ግን ዛሬ ላይ ማየት ያለብን ትልቁ ነገር ትናት በአባቶቻችን ጀግንነት በቅኝ ግዛት ያልተደፈረች አገር ዛሬ ምን ደረጃ ላይ አለች? ህዝቧ በነጻነት እየኖረ ነው? ዛሬም ከግዞት ነጻ ናት? ወይስ ታሪክ ብቻ የሚለውን በአጭሩ የራሴን እይታ ለማስቀመጥ ነው።
በመጀመርያ ነጻነት ማለት ምን ማለት ነው? ነጻነት የሚለውን ቃል ሰዎች የተለያየ አተረጓጎም ሊሰጡት ይችላሉ፡፡ ሆኖም ግን ነጻነት ማለት ከግዞት መውጣት፤ ከሌሎች ተጽኖዎች መውጣት፤ በራስ መወሰን ማለት ነው፡፡ ይህ ማለት ማንም ሌላ ሰው ሳያስገድደን እና የማንንም መብት ሳንነፍግ በነገሮች ላይ በራስ ወይም በጋራ መወሰን መቻል ነው፡፡ ደሞክራሲ ሊባልም ይችላል፡፡ ነጻነት አለ ካልን ሃሳባችን ወይም ተሳትፏችን ተሰሚነትና ተቀባይነት አለው ማለት ነው፡፡ በእርግጥ ይህንን በተግባር ለመተርጎም እኛ መብታችንን ማወቅ ግዴታችንን ደግሞ መወጣት ይኖርብናል፡፡
ይህንን ጥሬ ትርጉም ይዘን በኢትዮጵያ ላይ ያለውን ሁኔታ ስንመለከት "ነጻነት" የሚለውን ቃል እንኳ ለመጠቀም አስቸጋሪ ነው ብዬ አምናለሁ። በእርግጥ ትናት አይካድም ቅኝ ግዛት አልተገዛንም፤ የማንነት ችግር አልነበረብንም፤ በሌሎች ዜጎች ዘንድ ከበሬታና መፈራት ነበረን፤ ይህን ያክል የጎላ የምጣኔ ሃብት ችግር አልነበረብንም፤ ተስፈኞችና ሰላማውያን ነበርን፤ ለታሪክ፣ ለሃገር፣ ለወገንና ለማንነቱ የሚጨነቅና የሚቆረቆር ትውልዶች ነበርን። ዛሬ ግን ይህ ሁሉ ከእኛ ርቋል። አይዞህ ባይ ጠበቃ የሌለው፣ ተስፋው የጨለመ፣ ለሃገሩና ለማንነቱ የማይጨነቅ ተስፋ ቢሶች ሆነናል። በሀገር ውስጥም ሆነ በስደት አንገታችንን ደፍተን ነጻነታችንን አጥተን ሰሚ ያጣን ትውልዶች ሁነናል። ትናንት አባቶቻችን በተለያየ መልኩ በስደት ከሃገር ሲወጡ ዜግነታቸውን ሲጠየቁና ኢትዮጵያዊ ብለው ሲናገሩ ኢትዮጵያ የሚለው ስም የኩራት ስሜትና ክብር ያገኙበት ነበር።
ዛሬ ላይ ግን በተቃራኒው ሁኗል። ኢትዮጵያዊ ነኝ ለማለት የውስጥም የውጭም ችግሮች አጣብቂኝ ሁነውብናል። ግን ለምን? እንዴት? መከበርያ የነበረች ሀገር ዛሬ ህዝቦቿ በሄድንበት ሁሉ ዋይታ፣ ሰቆቃ፣ መከራና ስቃይ ስለምን በዛብን???
"እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ የዋይታና የመራራ ልቅሶ ድምፅ በራማ ተሰማ ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች የሉምና ስለ ልጆችዋ መጽናናትን እንቢ አለች።" (ኤር 31፥15) የተባለው ተፈጸመ። (ማቴ 2፥17) ተብሎ የተነገረው ለኢትዮጵያውያን ይሆን እንዴ እያልኩ አለመሆኑን እያወኩ ግን እራሴን እጠይቃለሁ። ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን እስራኤላውያን በእነ ያዕቆብና በልጁ በዮሴፍ ጊዜ ታላቅ ክብርና ዝና ነበራቸው። ያዕቆብና ዮሴፍን የማያውቅ ጨካኝና አረመኔ ንጉሥ በተነሳ ጊዜ ያ የነበራቸው ክብር፣ ሰላምና ነጻነት አጥተው በተቃራኒው ዋይታና ሰቆቃ ሆነ። ራሔልና መሰሎቿ ከስቃያቸው መብዛት የተነሳ እጅግ አለቀሱ። እግዚአብሔርም ልቅሷቸውን ሰማ ከባርነትም ነጻ ይወጡ ዘንድ ሙሴን፣ እያሱንና ካሌብን አስነሳ፤ ነጻም ወጡ። የእኛም ነገር ዛሬ ይኸው ነው፤ የአባቶቻችን ጀግንነት፣ታሪክ፣ መልካም ሥራ ሁሉ ተረስቶ የፈርዖያውያን መቀለጃና እልህ መውጫ የሆነው። እስራኤላውያን በራሔል ልቅሶ በሙሴ አማካኝነት ነጻ እንደወጡ ሁሉ ለእኛም ሙሴና ራሔል ያስፈልጉናል።

                            ራሔል ራሔል እስኪ አልቅሽ?


አልቅሽ እንጂ ራሔል የምን ዝምታ ነው
ልጆችሽ በስቃይ ነጻነት ናፍቃቸው 
ልጆችሽ በስደት ወሃ እየጣማቸው
እንዲሁም በእስር ቤት ዱላ ቀለባቸው  
ከፊሎች በቤት ውስጥ ስቃይ በዝቶባቸው
ሌሎች ብቸኝነት እያሰቃያቸው 
የሚናገሩበት አንደበት አጥሯቸው 
ጾታዊም ጥቃት ሲደረግባቸው
ዓለም በአንድ ጎራ ሁሉም ሲንቃቸው
አያውቁም! እነሱ ኋላ ቀሮች ናቸው
መጤ ህገ ወጦች....
...እያለ የዓለም ህዝብ በግፍ ሲገፋቸው 
ይኸው የልጆች ተደፋ አንገታቸው
ቀና ብሎ መሄድ እኮ ተሳናቸው
 ራሔል እስኪ አልቅሽ ይህንን ለውጭው። 

አይ ራሔል እንዳልሰማሽ ዝም አልሽ
አጣሽ እንዴ ይህን ታሪክ የሚነግርሽ 
የልጆችሽን የበደል ፅዋ የሚያዋይሽ
ጠፋ እንዴ ደግ ሰው የሚነግርሽ
ነው አንቺም እንደሌሎች ዝም አልሽ?
 ራሔል በዛብን መከራ ከልብ አልቅሽ።

አምላክ ሆይ እባክህ ሰው አስነሳ 
ለሀገር ለወገን የሚያስብ የሚሳሳ
ጀግና ጎበዝ እንደ ሳምሶን አንበሳ
ለወገኖቹ የሚቆም ዘብ አለኝታ 
እንደ ሙሴ የሚሆን መከታ 
ፈጣሪ እባክህ ሰው አስነሳ 
የራሔል እንባማ አለቀና ሳሳ።
ካለእሱ አይሆንም ሙሴን ላክላቸው
አረመኔዎችን ጸጥ እንዲያስላቸው
ለያሱም ለካሌብ ሙሴ አለ በላቸው
ለራሔልም ልጆች እሱ ነው ኃይላቸው።

በሉ የራሔል ልጆች ተዘጋጁ
ሁሉም ያለውን ይያዝ በእጁ
ስደት መከራ ይብቃ ነጻነትን አውጁ።

ራሔል ሆይ አቤት በይ እንጂ ኢትዮጵያ
የልጆሽ ደራሽ የጭንቀት ማረፊያ
አለሁ በይን እንጂ አንቺ የኛ መግቢያ
 ራሔል እስኪ አልቅሽ ለእምዬ ኢትዮጵያ
ለእናት ሀገራችን ለእኛ መከበርያ።


በእውነት ዛሬ በእጅጉ የራሔል ልቅሶና ሙሴ ያስፈልገናል። ለዚህ ደግሞ ኢትዮጵያውያን በአረብ ሃገራት በተለይ ደግሞ የሰሞኑ በሳውድ አረቢያ የሚደርስባቸው ግፍና መከራ፣ እንግልት፣ ስቃይና ሞት ከበቂ በላይ ማስረጃ ነው። ኢትዮጵያ ለዜጎቿ የሚቆረቆር መሪ ባለመኖሩ ዜጎቿ ያለምህረት በፖሊስና በህዝቡ እየታረዱና አካላቸው እስኪጎድል ደማቸው እንደጎርፍ እስኪወርድ ድረስ እየተደበደቡ ነው።
 ማን ሃይ ይበልላት? ማን ያልቅስላት? ማን ይጩህላት? መሪ ነን ባዮች ራሳቸው ችግሩ የጎላ እንዳልሆነ ለአለም መንግሥታት በመገናኛ ቢዙኃናቸው አዋጅ እየተናገሩ በየት በኩል ዓለም ይረዳን።
የቀደሙ ነገስታት ግን ለአገራቸው፣ ለዜጋቸው ሲሉ ራሳቸውን አሳልፈው እስከ መስጠት ደርሰው ነበር፤ ሰጥተዋልም። ዛሬ ላይ ያለው መሪ፣ መንግሥት ነኝ ባዩ ግን ለወጣቱ የስደት፣ ለቀሩት ደግሞ የሃዘን፣ የስቃይና የችግር ምክንያት ሆኗል።

በአጭሩ እኛ ምን እናድርግ???
  1. ከመንግሥት፦ ከኢትዮጵያ መንግሥት ምንም መፍትሔ ስለማልጠብቅ ብዙ ባልል ደስ ይለኛል። ከኢትዮጵያ መንግሥት ይልቅ መንግሥት አልባዋ የሶማሊ ዜጎች ተከብረው ይኖራሉ። እኛ ግን አንቱ የተባለ መንግሥት እያለን ( አንቱታው በእነርሱ አነጋገር/ በእየ ክፍለ ዓለማቱ በእንግልትና በስቃይ ውስጥ እየኖርን ነው። በእየ ሀገሩ ያሉት ኢምፓሲዎች፣ ዲፕሎማቶችና አምባሳደሮች ለገቢ ማሰባሰቢያ እንጂ የዜጎች ችግርና መከራ ቅጣት ታክል አይገዳቸውም። በዚህ ሁኔታ መፍትሔ ከመንግሥት መጠበቅ የዋህና ቂል ያስመስላል። ከቻለ እና ቅንነቱ ካለ ለስደት ምክንያት መሆኑን ተረድቶ ራሱን
    ማስተካከልና መፈተሽ ቢችል ትልቁ መፍትሔ ከእርሱ ጋር መሆኑን መረዳት ይችላል።
  2. ከቤተ እምነቶች፦ ከእነርሱ የሚጠበቀው በተለያየ ስቃይና መከራ ውስጥ ላለው ህዝብ የ ራሔልን እንባ የተቀበለ አምላክ የእኛንም ልቅሶና ጩኸት ይቀበል ሰንድ ወደ ፈጣሪ በጸሎት ማሳሰብ።
  3. ከታዋቂና ተሰሚነት ካላቸው ሰዎች፦ ምንም እንኳ በተለያየ ጊዜ ለዓለም መንግሥታትና በቀጥታ ጉዳዩ ለሚመለከታቸው አካላት ችግሮችን ማሰማቱን ባታቆሙም ዛሬም ያለመሰልቸት ተደጋጋሚ ግፊት ማድረግና ችግሩን ማሳዎቅ።
  4.  ከእኛ ከሁላችን፦ ነግ በእኔ ብለን በጸሎት ወደ ፈጣሪ፣ እንዲሁም ባለንበት ቦታ ሁሉ በሰላማዊ መንገድ ድርጊቱ ኢ_ሰባዊ እንደሆነ ለዓለም መንግሥታትና ህዝብ ጩኸታችንን ማሰማት።
በአጠቃላይ በኢትዮጵያውያን ላይ በአገር ውስጥ የአገር ውስጥ ቅኝ ገዥዎች፣ በውጭ የእነርሱ ቢጤዎች በዜጎቿ ላይ የመከራ ሸክም እየጫኑብን፤ ሰሚ በማጣታችን ተስፋ ቆርጠን እንገኛለን። ማንም እንደለለን ተረድተን ችግሩን ተቋቁመን ዘላቂ መፍትሔ ለማምጣት ቆርጠን መነሳት ይኖርብናል።ነጻነታችንን የምንጎናጸፈው እንዴት? መቼ? በምን መልኩ? የሚለውን ጥያቄ ሁላችንም እንወያይበት,,,,,,,,,,,,,

No comments:

Post a Comment