Monday, November 25, 2013

ቅኔአዊ ግጥም የሳዑዲን ግፍና በደል አስመልክቶ

          (በሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው)saudi and ethiopians

እንዲህ እንዲያ ብለው አሙን ፤ ተጠይቀው ሲመልሱ
የወገኖቻችንን ደም ፤ በእብደት ግፍ ያፈሰሱ
የኢትዮጵያ ስደተኞች ፤ ባሕላችንን ተቃረኑ
ንጽሐችንን አረከሱ ፤ ነፍሳችንን አስኮነኑ
መጠጥ በማዘዋወር ፤ በስርቆት ወንጀል በምኑ
አንተ አረመኔ እንስሳ ፤ ምኑን ብየ ላውጣልህ ስም
መጠጥ ምንህ ነውና ፤ ስካርህ የአንተ በሰው ደም
አስገድዳ አልደፈረችህ ፤ ደፈርካት እንጅ በማደም
መድፈርህ ሳያንስ ሳይበቃ ፤ አርደህ በላሃት ርጉም
አንተ ውሉደ አጋንንት ፤ አረመኔ ዘረ ሰዶም ፡፡
    ሌቦች ነበረ ያልካቸው ? እሰይ እንኳንም ሰረቁ
    ፈልገውት እንዳይመስልህ ፤ ምንም ነገር አይደል ድንቁ
    እባክህ ለከት ይኑርህ ፤ በዚህ አይታማም ወገኔ
    ነቢይህ ያውራህ ታሪኩን ፤ ያበሻን ማንነት ብያኔ
    የፍትሕ ደግነት ባለቤት ፤ ሕዝብ እንደሆነ መናኔ
    ነገር ግን እንዲያ ማድረጉ ፤ ሲያደርግ ባላይም በዓይኔ
    የሚነግርህ ስለነበረ ፤ መንገሩ ነበር በቅኔ
    በቋንቋው ጸጋ በዘይቤ ፤ በሰምና ወርቅ ምጣኔ ፡፡
ሐበሻ እንደዚህ ማስኖ ፤ የመከራ ዓይነት ለመጋቱ
ሞት በመንገዱ እየበላው ፤ አሁንም ለስደት መትጋቱ
ውዲቷ ሀገሩን እንደጠላ ፤ እየጣለለት መውጣቱ
ቅድስቲቱን እናት ሀገር ፤ ያረገብንን ያሳር ጓዳ
ለዜጎች ሲዖል ገሃነም ፤ ምቾት የሞላት ለእንግዳ
ሀገር ወገንን አውድሞ ፤ ተግቶ የሚሠራ ለባዳ
ይሄንን ቅጥረኛ መንግሥት ፤ ለጠላት ያደረን ባንዳ
ወልዳቹህ በማሳደግም ፤ ለዚህ ያበቃቹህት ይሁዳ
እናንተው ስለሆናቹህ ፤ የታሪኩ ሀሁ ሠሌዳ
ምሰሶው ወራጅ ማገሩ ፤ መሠረቱና ግድግዳ
ለችግራችን ተጠያቂ ፤ የምስቅልቅሉ ባለዕዳ
እናንተው መሆናቹህን ፤ ሊጠቁምና ሊያስረዳ
ያለንበትን ስንክ አሳር ፤ አውጥቶ ሊያሳይ ከሜዳ
ለማድረግ ነበረ እንጅ ፤ ከቶም አልነበር ሊጎዳ
መናኛ ነገርን ወስዶ ፤ ሊጠቀም ሊሆነው ጋዳ
እናንት በምቾት በቅንጦት ፤ እየኖራቹህ በተድላ
በሠራቹህት ሸር ክፋት ፤ እሱ መዋጡን ባሜኬላ
የስሕተታቹህን ርቀት ፤ የክብደቱንም ልክ ጣራ
ትኩረታቹህን በማግኘት ፤ ሊያሳውቅ እንጅ ያን ዳራ
አነፃፅራቹህ እንድታዩት ፤ በግብረገባዊ ተዋስኦ
በእምነታቹህ ሚዛን ልክ ፤ እንድትለኩት ያለ አድልኦ
ለማድረግ ነበረ እንጅ ፤ ከቶም አይደለም የአመል
የእውነት ምስክር አለን ፤ ከፈላስፋ እስከ አምላክ ቃል ፡፡
    የልቅ ማሰብ ያለባቹህ ፤ ለዚህ ለዚያ ሁሉ ሴራ
    ሀገራችንን ለማፍረስ ፤ ላረጋቹህት ስርሠራ
    ብትከፍሉ የማትጨርሱት ፤ አለባቹህና ብዙ ዕዳ
    ከቶ እንዴት ትሆናላቹህ ፤ አስቡበት አለው ፍዳ
    ይብላኝ ለእናንተ እንጅ ፤ እኔስ አለኝ ሀገር የእርሻ
   ጊዜአዊ ነው የኔ ችግር ፤ ለነገ አለኝ መፈወሻ
   መግቢያ አላጣም እኔ እንዳንተ ፤ አልነቀል መጨረሻ ፡፡
አርቃቹህ ብታስቡ ፤ መኖሪያቹህ ምድረበዳ
እህል ዘርቶ የማያበቅል ፤ የማያቆም አገዳ
አሁን ነገ ላይ ተሟጦ ፤ በሚያልቀው ዘይት ታብዮ
እንዲህ በግፍ ላይ መጫወት ፤ ፍርጃህ ነው የልቅ በል ወዮ
ሐምሳ ዓመታት ለማይቆየው ፤ አቤት ስንቱ ተደረገ
ደጅህ ላይ አለ ጠብቀው ፤ ይነቅልሀል ስደት ነገ
ዘይትህን ሲጨርስ መሬቱ ፤ ሌላ የለው የተነፈገ
ወዴት ይሆን መሰደጃህ ፤ ጎረቤትህ ከመሸገ
ጠላት አርገህ ካቆየኸው ፤ ፊትህን ማየት ካልፈለገ ፡፡
ላለው ሆኖልህ ነገሩ ፤ ዛሬ ላንተ ያደገደገ
ነገ አጠገብህ አይኖርም ፤ በሩን ይዘጋል እያሸገ
ያው በተራህ ትቆጥራለህ ፤ በየዓይነቱ ግፍ ወፍዳ
የዘሩትን ማጨድ አይቀር ፤ አጥቶ መውጫ ቀዳዳ
ወገን ንቃ ይግባህ ሴራው ፤ እኛን ማጥፋት የፈለጉት
እርስ በርስህ እያፋጁ ፤ አስቀምጠው ባንዳ መንግሥት
ሀገርህን ለመውረስ ነው ፤ ሲነጥፍባቸው ሲሳይ ሀብት ፡፡
    ብዙ ነው ሴራው ትብትቡ ፤  ምኞታቸውን ለማስመር
    እግዜርን ይዘህ ታገለው ፤ ሳትከፋፈል በብሔር
    ወጥመዱ ይከሽፋል ሴራው ፤ ይወድቁበታል ለአሳር
    የአንተ ቀን ደግሞ ይመጣል ፤ ይኖርህማል አኩሪ ሀገር ፡፡

No comments:

Post a Comment