Wednesday, November 13, 2013

ከዚህ መከራ እና ስቃይ እንዴት እንላቀቅ?

ዛሬ ላይ ስለ ስቃይ፣ መከራ፣ችግር እና እንግልት በቃላት መግለጽ አስፈላጊ አይመስለኝም። ምክንያቱም በእራሳችን ላይ ቀን በቀን በተግባር እየተፈጸመብን ነውና። ከተግባር በላይ አድን ነገር ሊገልጸው የሚችል ነገር የለም አይኖርምም። ምን አልባት አንዳንድ ሰዎች ችግሩ በቀጥታ ከእኔ አልደረሰም ልንል እንችል ይሆናል “አንተ በሰላም እንድተኛ ከፈለክ ጎረቤትህ ሰላም ይሁን” ይባል የለ በአገራችን ብሂል፤ ምናልባት ለጥቂት የዘመኑ እድለኞች ችግሩ በቀጥታ ባይደርሳቸውም ጎረቤት፣ ወገን ዘመድ ስቃይና እንግልት በዝቶበት ከሚችለው በላይ ሲሆን ሕይወትን በችግር ሲገፉ ማየት ለሰብአዊ ፍጡር እንቅልፍ የማያስተኛ ትልቅ በሽታ ነው። ይህን እያየ  አንድ ሰው ራስ ደና ካለ እሱ ከሰባዊ መደብ ወጥቷል ማለት ነው። እኛ ኢትዮጵያውያን ትናት እና ከትናት በስተያ የነበረን ልዩ  መለያ ጠባያችን መተሳሰብ፣ መረዳዳት፣ የጎረቤት ችግር  ችግሬ፣ ጭንቀቱ ጭንቀቴ፣ አገሬ ህይዎቴ እያልን የኖርን ህዝቦች ነበርን። በተለይ ደግሞ  የአገርና የዜግነት ክብር ምን እንደሆነ በተግባር ያየን፣ ለአለምም ያሳየን ህዝቦች ነበርን።
በዘርፉ ያሉ ባለሙያዎች እንደሚናገሩት አንድ አገር አገር ለመባል ሦስት መሰረታዊ ነገሮች ያስፈልጓታል። ከእነዚህ መሰረታዊ ነገሮች መካከል አንዱ ከተነካ ሉዐላዊት አገር የሚለው ይቀርና ሌላ ስም ይሰጣታል። እነዚህ ሦስቱም ተደጋግፈውና አንዱ የአንዱን ሉዐላዊነት መጠበቅ፣ ማስጠበቅ ይኖርበታል። አንዱ አንዱን ካጣ ምዕሉ ሊሆን አይችልምና። የአንድ አገር ሦስቱ መሰረታዊ ነገሮች የሚባሉት ግዛት፣ ህዝብና መንግስት ናቸው።
  1. ግዛት፦ የአንድ አገር ግዛት ማለት ወሰኗ፣ ድንበሯ፣ የቆዷ ስፋቷ፣ በውስጧ የየያዘዛቸው ወንዝ፣ ተራራ፣ሸለቆ፣ ባጠቃላይ ሙሉ ካርታዋ ማለት ነው። የኢትዮጵያ ግዛት ስንል በምስራቅ፣ በሰሜን፣ በደቡብና በምዕራብ ከሚያዋስኗት ግዛቶች የምትለይበት ቦታ፣ ድንበር ወይም ክልል ጀምሮ  በውስጧ የየያዘዛቸው ወንዝ፣ ተራራ፣ሸለቆ ወዘተ ሙሉ የቆዳ ስፋቷን ያዋስናል። ከዚህ የቆዷ ስፋቷ ትንሽ ከተነካ ግን የነበራት ሙሉ ግዛት አይኖራትም። ይህን ግዛቷን ለማስጠበቅ መንግሥት በማስተባበር ህዝብ በመተባበርና በመጠበቅ ሁሉም የድርሻውን መወጣት አለበት። ዛሬ ላይ የምናያቸው ነገሮች ግን ከዚህ የራቁ ናቸው። መንግሥት ለግዛቷ ሲጨነቅ አናይም፣ ህዝብም በተመሳሳይ። እንደ ጥሬ እቃ ግዛቷን ሲሸጥም፣ ሲደራደርባትም እናያለን። የጽሕፌ ዓላማ ይህን ማንሳት ስላልሆነ እዚህ ውስጥ መግባት አልፈልግም።
  2. ሕዝብ፦ ከሁሉም በላይ ክብርና ሥልጣን ሊሰጠው የሚገባ ነው። ሕዝብ ከሌለ የምንላቸው ነገሮች የሉም። ህዝብ ከሌለ ለግዛት ስም ጠርቶ፣ ወሰን ወስኖ ሊያስቀምጥ የሚችል አካል የለም። ስለዚህ ሕዝም ውድ ዋጋ ያለው ነው። በሌላም በኩል ፈጣሪ አክብሮና ባለ አዕይምሮ አድርጎ የፈጠረው መተኪያ የለለው ፍጡር ነው። ስለዚህ ግዛት በሕዝም ይከበራል፤ መንግሥት ደግሞ  በሕዝብ ይከብራል/ይነግሣል። ላከበረው፣ ላነገሠው ሕዝብ መንግሥት ዋጋ ሊከፍልለት ይገባል። ከዚያ ውጭ ግን(የዜግነት ክብር በኢትዮጵያችን ፀንቶ፣ ታየ ህዝባዊነት ዳር እስከዳር በርቶ)እያልን የአገር መለያ፣ የማንነታችን መገለጫ የሆነውን ባንዲራ እያውለበለብን የምንዘምረው የህዝብ መዝሙር ከንቱና ዋጋ አልባ ሆኗል ማለት ነው። ባንዲራ ደግሞ ጨርቅ አይደለም ልዩ መለያ ማንነታችን ነው። ይህን የማንነት ጉዳይ ሊያስከብረው የሚችል ደግሞ  ህዝብ ነው። ሕዝብ ማለት ደግሞ እያንዳንዳችን ስብስብ/ድምር ውጤት ነው።                                                                      ዛሬ ላይ እየተፈጸመ ያለው ችግር፣ ስቃይና እንግልት እንዲሁም ሞት የጥቂቶች ብቻ ሳይሆን የሕዝብን ክብርና የማንነታችንን መገለጫ ባዲራን ክብር የሚነካና ለዘላለም የማይጠፋ ጥቁር ጠባሳ ነው። ይህ ሲፈጸም ዝም ብሎ  ማየት ግን ከውርደትም በላይ ውርደት ከአረመኔነትም በላይ አረመኔነት ነው። የአረብ ሃገራት እኮ በሕዝባችን ላይ በደልና ግፍ የሚፈጽሙት አረመኔነት ቢሆንም ቅሉ አገራቸውንና የሕዝባቸውን የኑሮ ሁኔታ እንዳይነካባቸው ስለሚፈልጉ ጭምርም ነው።  ታዲያ እኛ ወገናችን የዜግነታችንን መገለጫ የሆነውን ባንዲራ ከራሱ ላይ ጠምጥሞ ሲሞት ስናይ እንዴት አስቻለን? አዎ እውነት ነው በስሜት ብዙዎቻችን በእጅጉ ተጎድተናል፣ ተረብሸናልም፣ ምግብ መመገብ አቅቶናል። ፊታችን በእንባ ታጥቧል። ግን መፍትሔ ሊሆን አልቻለም። ይህ አዲስ ክስተትም አይደለም፤ አስር፣ አስራ ዓመታትን አስቆጥሯል። ችግሩ፣ ስቃዩ  እየባሰ፣ እየጎላ መጣ እንጂ። በአገር ውስጥም በውጭም ችግሩ ያው ነው ልይነቱ የውጭው በመገናኛ ብዙኃን ጎልቶ  መታየቱ እንጂ ብዙዎች አገር ውስጥም እየተሰቃዩ፣ መከራ በዝቶባቸው የሚኖሩት በርካታ ናቸው። ወደ ሦስተኛው መሰረታዊ ነገር ልግባ መፍትሔውን በኋላ እንመለስበታለን።
  3. መንግሥት፦ መንግሥት ማለት በጥሬ ትርጉሙ በአንድ አገር  ውስጥ ሕጎችን ለማውጣትና ለማስፈጸም፣ ሕዝብን ለማስተባበርና ደኅንነቱን ለማስጠበቅ፣ አገርን ለማስከበር  ስልጣንና ኃላፊነት ያለው አካል ማለት ነው። እንዲሁም በምርጫም ይሁን በሌላ መንገድ በሕዝብ ድጋፍ ስልጣን ላይ የወጣ አካል ነው። ስለዚህ ይህ በሕዝብ ድጋፍ ሥልጣንን የያዘ አካል ከስሙና ከትክክለኛ ትርጉሙ አንፃር ለህዝብና ለአገሪቱ ግዛት ከማንም በላይ የሚጨነቅ፣ የሚያስብና የሚቆረቆር አካል ነው ማለት ነው። ምክንያቱም ሕዝብ ከሌለ መንግሥት የለም፤ ግዛትም ከሌለ እንዲሁ። ከምንም በላይ ለመንግሥት መኖር ሁለቱም ወሳኝ ጉዳዮች ናቸው። የየትኛም አገር መንግሥት ይህን ተገንዝቦ ለሁለቱም የሚገባውን እንክብካቤና ክብር መስጠት ካልቻለ የመኖር ዋስትናው ጥያቄ ውስጥ ይገባል። አወዳደቁም በእጅጉ የከፋ ይሆናል። 
ከዚህ አንፃር የአገራችን መንግሥት የቱ ጋር ነው ያለው ብሎ መጠየቁ መሰረታዊና አስፈላጊ ጥያቄ ነው። ያለበትን ደረጃም በተገቢው መንገድ ማሳየት ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል። ስንተቻች/ስንነታረክ ብዙ ዓመታትን አሳልፈናል። አሁን ጊዜው የተግባር ነው። ተግባራዊ ሥራ ለመስራት ወኔ ሰንቀን መነሳት ይኖርብናል። የጦርነት ወኔ አይደም የሰላም፣ የአገር ፍቅር፣ የዜግነት ክብር ወኔ፣ የማንነት ወኔ እንጂ። 
ሰሞኑን የዓለምን ዓይንና ጀሮ የሳበ ትልቁ ክስተት በሳዑዲ አረቢያ ለማየትም ሆነ ለመስማት ዘግናኝና አሰቃቂ በሰው ልጆች ላይ እየተፈጸመ ያለው ድርጊት ነው። በተለይ ደግሞ በኢትዮጵያውያን እህት ወንድሞቻችን ላይ እየደረሰ ያለው ግፍና መከራ ነው። የክብራችን መገለጫ ባንዲራችን ሳይቀር በደም ታጠበ። ወንድሞቻችንም ሰማዕትነትን ተቀበሉ፤ ባንዲራችንም ተጨምራ በድንጋይ ተወገረች። አሁን ችግሩን ማዉራት መደጋገም መፍትሔ አይሆንም። ስለመከራው፣ ስቃዩ፣ እንግልቱና ችግሩ የመገናኛ ብዙኃኖች አወሩልን፣ እኛም ብዙ አወራን፣እያወራንም ነው። 
የሁላችንም ውሳጣዊ ጥያቄ ከዚህ አስከፊ መከራና ስቃይ እንዴት እንላቀቅ?እንዴት ነጻነታችንን እንጎናፀፍ?እንዴት ወደነበርንበት ክብር እንመለስ?የሚለው ስለሆነ በዚህ ዙርያ ለመደርደርያ ያክል ጥቂት ነጥቦችን ላንሳ።
  •  አንድነት መፍጠር፦ ችግር ለመፍታትም ሆነ መፍትሔ ለመፈለግ እኛ አንድ መሆን ይኖርብናል። መግባባት፣ መነጋገር፣ መወያየት በምንችልባቸው ነገሮች ላይ አንድ መሆን አለብን። እኛ በሃሳብ በአመለካከት ከተለያየን እንዴት ችግር ልንፈታ  እንችላለን። ከላይ ባነሳናቸው መሰረታዊ ነገሮች ላይ የጋራ መግባባት ሊኖረን ይገባል። ለአንድ አገር ግዛት፣ ሕዝብና መንግሥት እንደማስፈልግ መግባባት አለብን። በአንድ አገር ውስጥ የተለያየ ቋንቋ፣ ባህል፣እምነት ያለው ህዝብ በአገሪቱ ግዛት አንድ መሆን መቻል አለብን። ይህንን ሊያስተባብርና ሊመራ እንዲሁም አንድ ሊያደርገን የሚችል መንግሥት ሊኖረን ይገባል። ከዚያ ውጭ በቋንቋ፣ በባህል፣ በእምነት እንደተለያየን ሁሉ አንድ ሊያደርገን የሚችል የጋራ የሆነ ነገር ከለሌን ችግሩን በህብረት መቅረፍም ሆነ መቀነስ አንችልም። ስለዚህ መንግሥትም ይህን ተረድቶ ለመለያየት ምክንያት የሆኑ ነገሮችን፣ አንድነታችንን ሊያከስም የሚችሉ ነገሮችን ሊያስወግድልን ይገባል። ብሔር፣ ጎሳ፣ ቋንቋ፣ እምነት እያለ ሊከፋፍለን፣ ሊለያየን አይገባም። ይህን ድርጊት የፖለቲካ ድርጅቶች፣ የሀይማኖት ተቋማት፣ የግል/ሰባዊ መብት ድርጅቶችና ሕዝብ ሁላችንም አግባብ ባለው መልኩ ማውገዝና ማስቆም ይኖርብናል። አንድነት፣ ህብረት ከሌለ ምንም ማድረግ የማንችል ባዶዎች ነንና። የቀደሙት አባቶቻችን በአንድነታቸው ያስመዘገቧቸውን ድል መመልከት እኛ ዛሬ አንድነት እንድንፈጥር ትልቅ ትምህርት ይሆኑናልና። ስለዚህ ዛሬ ላይ እየደረሰ ያለውን አሰቃቂ ድርጊት ለማስቆም  አንድነት ፈጥረን መወያየት፣ መነጋገርና መፍትሔ መፈለግ ትልቁ ሥራችን ሊሆን ይገባል። 
  • አገራዊ ስሜት መፍጠር፦ ሁላችንም በእየአለንበት አንድነት መፍጠር ስላልቻልን አገራዊ ስሜታችንም በእጅጉ ወርዶብናል ማለት ይቻላል። ወጣቱ ስለአካባቢው እንጂ እንደ አገር ማውራት አቁመናል። ስለ ኢትዮጵያ ሲወራ እንደ ሁለተኛ ሦስተኛ ዜጋ ሁነን ቁመን የምንሰማ በርካቶች ሁነናል። ኢትዮጵያዊነት ምን ማለት እንደሆነ ትርጉሙም ስሜቱም ጠፍቶብናል። ወጣቱም ብሔርን፣ ቋንቋን ይሰብካል። የፖለቲካ ድርጅቶችም ይህንኑ ያስተጋባሉ። ለአገር ሳይሆን ለብሔር ብቻ የቆሙ ናቸው። መንግሥትም ለስልጣን ማራዘሚያ ሲል አገራዊ ስሜት እንዲጠፋ ምክንያት ሁኗል። ይህን ከባድ ችግር አሶግደን አገራዊ ስሜት ሰንቀን ኢትዮጵያዊነት ምን ማለት እንደሆነ ከተረዳን አሁን በኢትዮጵያውያን ላይ የሚደርሰውን ችግር ማስቆም እንችላለን። አገር ወዳዶች ከሆን በቀላሉ ከአገር አንወጣም። አገራዊ ስሜት በውስጣችን ከነገሰ ለአገር፣ ለወገንና ለክብራችን ዘብ እንሆናለን።  በዚህ መልኩ ችግሩን ከአምላክ ጋር ማስዎገድ ይቻላል።
  • ዜጎች ሕጋዊና አግባብ ባለው መንገድ እንዲወጡ ማድረግ፦ እኛ ሁላችንም ማለት ይቻላል አገራዊ ስሜት ስለሌለንና ዜጋ ማለት ምን ማለት እንደሆነ ስለማይገባን ከመንግሥት ጀምሮ ሰዎችን ወደ ውጭ ማስወጣት እንደ አንድ የገቢ ማስገኛ መንገድ አድርገነዋል። ዜጎች ሕጋዊ ሁነው እንዲወጡ ሳይሆን ገንዘብ ከፍለው በተሳሳተ መንገድ ሲሄዱ ይመለከተኛል የሚል አካል ባለመኖሩ ችግሩ እንዲባባስ አድርጎቷል። ኤጄንሲ ነን ባዮች ለሚያገኟት ሽርፍራፊ ሳንቲም እንጂ የዜጎች መከራና ስቃይ አይገዳቸውም። ይህን ችግር ለመቅረፍ ማንኛውም ሰው ከአገር ሲወጣ በሕጋዊ መንገድ እንዲወጣ ቢደረግ አማራጭ መፍትሄ ነው። ይሁን እንጂ በሕጋዊም ሆነ በሌላ መንገድ ከአገር የወጣን ሰው እንደ ዜጋ ሰባዊ መብቱ ሊከበርለት የሚችልበትን መንገድ ማመቻቸት ይኖርብናል። ኤጄንሲዎችም ገንዘብ ላይ ብቻ ሳይሆን ለሚልኳቸው ሰዎች ደኅንነትና ክብር እንዲያስቡ ማድረግ። ይህን ጉዳይ የሚመለከተው ሁሉ በኃላፊነት ይዞ ቢቀሳቀስ ችግሩን በመጠኑም ቢሆን መቀነስ ይቻላል።
  • ኤምባሲዎች/ቁንስላዎች የዜጎችን መብት እንዲያስከብሩ ማድረግ፦ መቼም በየአገራቱ የተሰየሙት ኤምባሲዎች/ቁንሰላዎች ፓስፖርትና መታወቂ ለማደስና መሰል ጉዳዮችን ለማስተናገድ ብቻ አይመስለኝም። ይልቁንም በቅርበት ሁነው የዜጎችን መብት ማስከበር እንደ አንድ ትልቅ ኃላፊነት ይወስዱም ዘንድ እንጂ። ስለዚህ እነዚህ አካላት በዋናነት በሕጋዊም ሆነ በሌላ መንገድ የገቡትን ዜጎች መብት ከሚኖሩበት ሕግ አንጻር ማስከበር ተቀዳሚ ተግባር ማድረግ አለባቸው። የአሰሪና ሰራተኛ የስምምነት ውሉንም በሚገባ ማየትና ማስፈጸም ይኖርባቸዋል። ከክፍያ መጠን ጀምሮ ማየትና ከመግሥት ጋር ወጥ የሆነ የውል ስምምነት እንዲኖር መወያየት አለበት። አንድም ሰው ቢሆን ዜጋ ነውና መብቱ ሊከበርለት ይገባል። ይህን ማድረግ የሚችሉ የኢምባሲ/ቁንስላና ዲፕሎማት ሰራተኞ ያስፈልጋሉ። ይህን ማድረግ ከተቻለ ችግሩን በቀላሉ መቅረፍ ይቻላል። ሌሎች የሲቪክ ማህበራትም ሆነ የፖለቲካ ድርጅቶችም ይህን ይፈጽሙ ዘንድ ትችት ብቻም ሳይሆን እገዛ ማድረግ አስፈላጊ ነው ብየ አምናለሁ። ከዚያ ውጪ ግን ልቅሶ፣ዋይታ፣ መከራና እንግልት የዘወትር ተግባራችን እንደሆነ ይቀጥላል ማለት ነው።
  • በዜጎቻችን ላይ ኢ_ሰባዊ ድርጊት ፈጻሚዎችን በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት መጠየቅ፦ ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን እንዲሉ...አገሪቱንና መንግሥትን ቢንቁ እንጂ በዚህ በ21ኛ ክፍለ ዘመን ማን የማነን ዜጋ ከሕግ ውጭ ይነካል። ሕጋዊ ባይሆንና ወንጀል እንኳ ቢሰራ በሕግ አግባብ ይቀጡታል እንጂ እንደ አሸባሪ በአገኙበት ቦታ ደሙን አያፈሱም፣ አካልን አያጎሉም። ምክንያቱም የሰባዊ መብት፣ የዓለም አቀፍ ሕግ አይፈቅድላቸውምና። እኛን ግን ተቆርቋሪና መንገሥት እንደሌለን ካለ ሕግ በአደባባይ ገደሉን፣ ወገሩን፣ ደፈሩን። እንደ እንስሳ ውሻ እየተባልን ክብራችን ይዋረዳል። የማንነታችን መገለጫ የሆነው ባንዲራችን በደም ታጠበ። በዚህ በሰለጠነ ዘመን ሴት እህቶቻችን በየመንገዱ እንዲወልዱ ተደረገ፤ ተደፈሩም። ስለዚህ ይህን ዘግናኝና አሰቃቂ ድርጊት ፈጻሚዎችንና የአገሪቱ መንግሥትን በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት መጠየቅና ለተባበሩት መንግሥታት አቤት ማለት። ይህን ደግሞ ከአገራችን መንግሥት ስለማንጠብቅ ሙያዊና ተሰሚነት እንዲሁም አቅሙ ያላቸውን ሰዎች በጊዛዊ ኮሚቴ አቋቁሞ ክስ መመስረትና ጉዳዩን መከታተል ከተቻለ ለዘላቂም መፍትሔ ትልቅ አስትዋጾ ያደርጋል፤ ለተጎዱ ወገኖቻችንም በዚህ መልኩ አለን ልንላቸው ይገባል። 
  • ጸሎት ወደ ፈጣሪያችን ማቅረብ እና በሰላማዊ መንገድ ድምጻችንን ለዓለም ሁሉ ማሰማቱ እንደተጠበቀ ሁኖ........

No comments:

Post a Comment