Saturday, May 25, 2013

መነኰሳትን አይቻለሁ

 ከእለታት አንድ ቀን ጻድቁ አባታችን አባ መቃርዮስ ከግብጽ አስቄጥስ ወደ ኒጥርያ ተራራ አባ ፖምቦን ፈልጎ ሄደ። አባ ፖምብም "አባታችን እስኪ ለመነኰሳቱ የሆነ ቃል በላቸው" አለው። አባ መቃርዮስም "እኔ ራሴ ገና መነኩሴ አልሆንኩም ነገር ግን መነኰሳትን አይቻለው" አለ። ያየውንም እንዲህ በማለት ነገራቸው፦ "ብቻዬን በበኣቴ ውስጥ ተቀምጨ እያለሁ ባለሁበት በርሃ ውስጥ ማን እንዳለ ለማወቅ በማሰብ ወደ በርሃ እንድሄድ ሃሳቤ አስቸገረኝ። እኔም ይህ ሃሳብ ከአጋንንት የመጣ ጸብአ ፍልሰት/ከብኣቴ ሊያስወጣኝ/ እንዳይሆን ብዬ በመስጋት ለአምስት ዓመት ያህል ከዚያ ከሚያስቸግረኝ ሃሳብ ጋር ስታገል ቆየሁ። ነገር ግንነገሩ ከእግዚአብሔር እንደሆነ ስረዳ ወደ ውስጠኛው በርሃ ለመሄድ ከበኣቴ ወጣሁ። አርባ ቀናት ተጉዤ ወደውስጠኛው በርሃ ደርሼ ጸሎት ካደረስኩ በኋላ ስኳዝ ከአንድ ወንዝ አጠገብ ደረስኩ።
ከዚያም ከመካከሉ ደሴት አለውና ጥቂት ውኃ አገኘሁ። የበርሃ አራዊቱም ወደዚያ በመምጣት ይጠጣሉ። ውኃ ሊጠጡ ከሚመጡት አራዊት መካከልም ሁለት እርቃናቸውን የሆኑ፣ ሰውነታቸው በጣም የከሳና ፀጉራቸው የረዘመ፣ የእጅና የእግር ጥፍራቸው እንደ እንስሳት በጣም የረዘመ ሰዎች አየሁና ታላቅ ፍርሃትን ፈራሁ፤ ሰውነቴም ተንቀጠቀጠ፣ እነርሱ መናፍስት ናቸው ብዬ ነበርና። ነገር ግን እኔን ባዩኝ ጊዜ ተንቀሳቀሱ፣ እነርሱም በስሜ ጠርተው እንዲህም አሉኝ።
  • "መቃሪ ሆይ! አትፍራ እኛም እንደ አንተ ሰዎች ነን። ወደዚህ እንዴት መጣህ? ከዚህስ ምን ትሰራለህ?" አሉኝ።
  • እኔም የፈለግኩትን ከእኔ ያላራቀ እግዚአብሔር እውነተኛ ቅዱሳን የሆናችሁትን አያችሁ ዘንድ ፈቀደልኝ። በረከታቸው ትድረሰኝ አልኩና ቀርቤ ዳሰስኳቸው፣ መንፈስ እንዳይሆኑ ብዬ ሰግቼ ነበርና። እኔም በበርሃ የሚኖሩ ቅዱሳንእንደሆኑ ባወቅሁ ጊዜ ወደ እርሳቸው ቀርቤ እጅ ነሣኋቸው፣ እነርሱም ባረኩኝ፣ ብዙ ነገርም ነገሩኝ። በዚህ በርሃ ከመጣን ጀምሮ ከአንተ በቀር ከአንድም ሰው ጋር ተገናኝተን አናውቅም አሉኝ። 
  • እኔም "ከየት መጣችሁ? ከዚህ በርሃስ እንዴት መጣችሁ?" አልኳቸው።
  • እነርሱም እንዲህ አሉኝ፦ የመጣነው ከገዳም ነው፣ ሁለታችንም ተስማምተን ከዚህ ከመጣን አርባ አመታችን ነው። አንዳችን ግብጻዊ ስንሆን ሌላችን ሊቢያዊ ነን" አሉኝ። " ዓለም እንዴት ናት?? ዝናብ በወቅቱ ይዘንባልን ብለው ጠየቁኝ።
  • እኔም የጠየቁኝን መለስኩላቸውና እንዴት መነኩሴ መሆን እችላለሁ? ብዬ ጠየቅኋቸው።
  • እነርሱም "በዓለም ያሉትን ነገሮች በሙሉ ካላቆምክ መነኩሴ መሆን አትችልም" አሉኝ።
  • እኔም እኔ ደካማ ነኝ፣ እናንተ እንደምትሠሩት ልሰራ አልችልም አልኳቸው።
  • እነርሱም "እንደኛ መሆን ካልቻልክ በበኣትህ ተቀመጥና ስለ ኃጢያትህ  አልቅስ" አሉኝ።
  • እኔም ክረምት ሲመጣ አይበርዳችሁምን? በጋስ ሲሆን ሙቀቱ ሰውነታችሁን አያቃጥለውምን? አልኳቸው። 
  • እነርሱም "ይህን ዓይነት አኗኗር እግዚአብሔር ለእኛ አዘጋጀልን፣ ክረምት ሲመጣ አይበርደንም፣ በጋ ሲሆንም ሙቀቱ አይ ጎዳንም" አሉኝ።
ከዚህም የተነሣ አባ መቃርዮስ "እኔ መነኰሴ አይቼ መጣሁ እንጂ ገና መነኰሴ አልሆንኩም" አለ። ዛሬ ስንቶች ናቸው የአባታችን የአባ መቃርስ ትህትና፣ ትዕግስት፣ ማስተዋል፣ ራስን መግዛትና ጸጋቸውን መለየት ተስኗቸው/ረስተው ያልሆኑትንና ያልነበሩበትን ሲሰብኩና ሲናገሩ የምንሰማቸው? ስንቶች ናቸው የተቀደሰውን ገዳማዊ ሕይወት ሲያራክሱ የምንሰማቸው? የቀደሙት አባቶቻችን ግን የመንፈስ ፍሬን ገንዘብ አድርገው፣ የሆኑትን እንኳ በትህትና እራሳቸውን ዝቅ አድርገው እኛ ኃጢያተኛ ነን፣ አልበቃንም፣ መንፈስን መለየት ይገባናል እያሉ ነበር ይችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያስረከቡን። እኛም ዛሬ እንደ አባታችን አይቻለሁ እንጂ እኔ አይደለሁም እያልን ለመሆን ትጋቱንና ብርታቱን ያድለን ዘንድ አምላከ ቅዱስ መቃርስን  በጸሎት እንማጸነው።

የጻድቁ አባታችን ጸሎቱ፣ ረድኤቱና አማላጅነቱ አይለየን፡ አሜን።

1 comment:

  1. Hey! Would you mind if I share your blog with my facebook group?
    There's a lot of people that I think would really enjoy your content.
    Please let me know. Cheers

    Also visit my web site; cicexpo.org ()

    ReplyDelete