Friday, May 31, 2013

ስለአባይ ምን ተባለ?

                                                                                           በከበደ ካሳ
https://blogger.googleusercontent.com/img/b/R29vZ2xl/AVvXsEj9wbVH3TqueRjGM3LyUpt3jQf2OavsAU0D0Unns3zubiU2JSQAzNnDMH0mM4myVrtf8LneYC6FurAXKUKjLG4p75zsxhM65wMVlYJG8O811fYb03HLA5tmNM3QcQQJE6Y1VbZwOJgJBNY/s1600/%E1%8A%95%E1%8C%8C.jpg
ኢትዮጵያ ግንቦት 20/2005 የአባይ ወንዝን የተፈጥሮ አቅጣጫ መቀየሯ የአለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃንና ጉዳዩ የሚመለከታቸዉ ሀገራት መነጋገሪያ አጀንዳ ሆኗል፡፡ ዋናው ጉዳይ ምሽት ላይ አልጀዚራ በኢንሳይድ ስቶሪ /inside story/ ፕሮግራሙ ከኢትዮጵያ አቶ በረከት ስምዖንን፤ ከግብፅ ላማ ኤል ሃሎንና ከእንግሊዝ ሊዮ ፓስካልን በማስገባት ዉይይት ያደረገበት ነው፡፡ በዚህ ላይ በኋላ እመለስበታለሁ፡፡ አሁን ግን መገናኛ ብዙሃን፤ ግብፅና ሱዳን ምን አሉ የሚለዉን እንመልከት፡፡

በጉዳዩ ላይ ሰፊ ዘገባ የሰጠው አህራም የተባለዉ የግብፅ ድረ-ገፅ ነው፡፡ ቢቢሲ፤ አልጀዚራና ዋሽንግተን ፖስትም እንዲሁ፡፡ ሁሉም ታዋቂ መገናኛ ብዙሃን በተለያየ መጠን ለጉዳዩ ሽፋን ሰጥተውታል ማለት ይቻላል፡፡ ከብዛታቸውና ከምንጫቸው ተመሳሳይነት አንፃር የያንዳንዱን ዘገባ አቅጣጫ ከማየት ይልቅ በዚህ ጉዳይ ላይ በስፋት አስተያየታቸውን ወደሰጡት ግለሰቦች አትኩሬአለሁ፡፡
ከላይ ከቁንጮው እንነሳ፡፡ ማለቴ ከግብፅ መንግስት አቋም፡፡ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ፅ/ቤት ያወጣው መግለጫ አሁን በአባይ ወንዝ ላይ እየተካሄደ ያለው ግንባታ በውሃ መጠኑ ላይ መቀነስን ሊያስከትል የሚችል እንዳልሆነ የሚገልፅ ነው፡፡ በአባይ ላይ የሚገነባ ማንኛውም ፕሮጀክት ከመጀመሩ በፊት የወንዙን አቅጣጫ በማስቀየር ቦታውን ለግንባታ ምቹ ማድረግን ይጠይቃል ብሏል መግለጫው፡፡ ስለሆነም ከተለመደው ውጭ የሆነ አዲስ ነገር የለም የሚል ይመስላል፡፡
የግብፅ ካቢኔም በጉዳዩ ላይ ትናንት በዝግ ከመከረ በኋላ ባወጣት ቁራጭ መግለጫ የግድቡ ግንባታ ተጀመረ ማለት ግብፅ እውቅና ሰጥታዋለች ማለት አይደለም ብሏል፡፡ ያም ሆኖ የግብፅና ሱዳን የውሃ ድርሻን የማይቀንስ እስከሆነ ድረስ ማንኛዉንም የልማት ፕሮጀክት እደግፋለሁ ብሏል ካቢኔው፡፡ ካቢኔው ጨምሮ እንደገለፀው ለማንኛውም የሶስትዮሽ ኮሚቴውን የጥናት ሪፖርት ይፋ መሆን እንደሚጠብቅ ገልጧል፡፡ ሪፖርቱን ተከትሎ የሚይዛቸዉን አቋሞች /የሚወስዳቸዉን እርምጃዎች/ ከወዲሁ እንዳዘጋጀም ካቢኔው ጠቁሟል፡፡ ምን እንደሆኑ ፍንጭ ከመስጠት ቢቆጠብም፡፡ በዝች መግለጫ መጨረሻ የገባችዉ አረፍተ ነገር ደግሞ “ግብፅና ሱዳን በአንድ ልብ ሆነን በጉዳዩ ላይ ተባብረን እየሰራን ነዉ” ትላለች፡፡ ሱዳን ወደ ኢትዮጵያ እያደላች ነው የሚለዉን ዘገባ ለማጣጣል የገባች አረፍተ ነገር ሳትሆን አትቀርም፡፡
አሁን ዘግይቶ እንደተረዳሁት ደግሞ ዛሬ ግንቦት 22/2005 ፕሬዝዳንት ሙርሲ ከተመረጡ ሚንስትሮች ጋር በዚሁ ጉዳይ ላይ ለመምከር ቀጠሮ ይዘዋል፡፡
የሃገሪቱ የሹራ ምክር ቤት ደግሞ በመጭው እሁድ በዚሁ ጉዳይ ላይ ለመምከር የአስቸኳይ ስብሰባ ቀን ቆርጧል፡፡ በስብሰባው የውጭ ጉዳይና የደህንነት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴዎችን ጨምሮ 6 ኮሚቴዎች እንደሚሳተፉ ይጠበቃል፡፡
እኔ እንዳገኘሁት መረጃ ከሆነ የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በሃገሪቱ ያሉትን የኢትዮጵያ አምባሳደር ሞሃሙድ ድሪርን አስጠርቶ በጉዳዩ ላይ ቃላቸዉን ተቀብሏቸዋል፡፡ ምስኪን! ምን ብለዉ ይሆን? የሚኒስቴሩ የስራ ሃላፊዎች ከበው በጥያቄ ሲያዋክቧቸው፡፡ እንደ መረጃው ሰዎቹ በኢትዮጵያ ዉሳኔ መከፋታቸዉን ለአምባሳደሩ ገልፀውላቸዋል፡፡
ከአባይ ወንዝ የፍሰት አቅጣጫ ማስቀየር ጋር በተያያዘ ስማቸው በተደጋጋሚ የተነሳዉ የግብፅ ውሃና መስኖ ልማት ሚንስትሩ ሞሃመድ ባሃ ኢልዲን ናቸው፡፡ እሳቸዉ የንግግራቸው መጀመሪያ ያደረጉት ግብፅ በጥቅሟ ላይ የሚመጣን ማንኛውንም አይነት ፕሮጀክት እንደማትደግፍ መግለፅ ነው፡፡ ይህ አቋማቸው እንዳለ ሆኖ የወንዙ የፍሰት አቅጣጫ መቀየሩ ግን ለግብፅ ምንም ጉዳት እንደሌለው ለጋዜጠኞች አረጋግጠዋል፡፡ “የተለመደ የግንባታ ሂደት መገለጫ ብቻ ነዉ” ብለውታል፡፡

የአንድ ሃገር ሚኒስትር ከዚህ በላይ ሊሉት የሚችሉት በጎ ነገር ሊኖር አይችልም፡፡ የሃራቸውን ጥቅም የሚጎዳ ነገር ካለ እሱን መቃወም አለባቸው፤ ከሚጠቅማቸው ጋር ደግሞ መተባበር፡፡ እሳቸው ያሉትም ይህንኑ ነው፡፡ አሁን በግብፅ ላይ የተደቀነ አደጋ የለም፤ የጋራ ኮሚቴው ሪፖርት እስከሚወጣ እንጠብቃለን ነው ያሉት፡፡
እኝህ ሰው በቅርቡ በሃገሪቱ በተደረገው የስልጣን ሽግሽግ ባሉበት እንዲቆዩ ሲደረጉ እንኳን ደስ አለዎት በማለቴ የተረቡኝ እንደነበሩ አስታውሳለሁ፡፡ ሰውየው ምንም ያህል ትችት ቢሰነዘርባቸውም ስለኢትዮጵያ ያላቸውን በጎ እይታ በአደባባይ ከመግለፅ ያልተቆጠቡ ናቸው፡፡
ሌላዉ በዚህ ጉዳይ በንቃት የተሳተፉት በኢትዮጵያ የግብፅ አምባሳደር ሞሃመድ እድሪስ ናቸው፡፡ የህዳሴው ግድብ ግብፅ የግዷንም ቢሆን ልትቀበለው የሚገባ የማይቀር ክስተት /reality/ ነው ብለዋል፡፡ የግብፅ የድርድር ግብ መሆን ያለበትም ግድቡን ማስቆም ሳይሆን ሁለቱም ወገኖች ተጠቃሚ በሚሆኑበት መንገድ ላይ ሊሆን እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡ “የአስዋን ግድብ ለኛ አንደሚያስፈልገን ሁሉ የህዳሴዉ ግድብም ለኢትዮጵያውያን ብሄራዊ ሃብታቸው ነዉ” ሲሉ ነው እዉነታውን ፊት ለፊት ለመጋፈጥ የቆረጡት፡፡ አምባሳደሩ አሁን ኢትዮጵያ ያደረገችው ነገር ዱብ እዳ ሳይሆን ካለፈው ህዳር ጀምሮ የምናውቀው ነው ብለዋል፡፡
በሁሉም መድረኮቻችን ኢትዮጵያ በኛ ላይ ጉዳት እንደማታስከትል ደጋግማ አረጋግጣልናለች፤ እኛም ይህንኑ አምነን ተቀብለናል ያሉት አምባሳደሩ ግብፅ ሶስቱም ወገኖች ተጠቃሚ የሚሆኑበትን አሰራር እየፈለገች መሆኗን ተናግረዋል፡፡

እኔ የነዚህን ባለስልጣናት ንግግር በአወንታዊ መልኩ ነው ያየሁት፡፡ ምክንያቱም ቢያንስ ኢትዮጵያ እነሱን የመጉዳት ሃሳብ እንደሌላት መረዳታቸዉን ገልፀውልናል፡፡ የጋራ ተጠቃሚነት መርህ ቀስ በቀስ ቅቡል እየሆነ መምጣቱን አመላካች አስተያየት ነው፡፡
ሆኖም የሀገሪቱና የአለምአቀፍ መገናኛ ብዙሃን ዘገባ አሉታዊ ነው፡፡ መገናኛ ብዙሃኑ ከግድቡ ጋር ያሉ አወንታዊ ጎኖችን ዘወር ብለዉ እንኳን ሳያዩ ሊያስከትል ይችላል ብለዉ ባሰቡት ተፅዕኖ ላይ ብቻ ነዉ ያተኮሩት፡፡
ባለስልጣኖቹ ከተናገሩት ውስጥ ሲመርጡ እንኳን ይህንኑ ፍላጎታቸውን የሚያሟላላቸዉን ንግግር ብቻ እንጅ በመቻቻልና በጋራ ተጠቃሚነት ላይ ያተኮሩትን አገላለፆች በተደጋጋሚ ዘለዋቸዋል፡፡ ለምሳሌ ያክል ሞሃመድ ባሃ ኢልዲን ግብፅ በጥቅሟ ላይ የሚመጣን ማንኛውንም አይነት ፕሮጀክት እንደማትደግፍ መግለፃቸውን ሲያራግቡ በግብፅ ላይ የተደቀነ አደጋ የለም ማለታቸውን ግን ብዙዎቹ አድበስብሰውት አልፈዋል፡፡
ሌላው የሚጠበቅ ግን ቢሆንም መታወቅ ያለበት የግብፅ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አቋም ነዉ፡፡ ፓርቲዎቹ ይህንን ጉዳይ ለፖለቲካ ጥቅም ማግኛ ሲጠቀሙበት ተስተውለዋል፡፡ እነሱ እንደ ጠንካራና ለግብፅ ህዝብ የቆሙ፤ ሙስሊም ብራዘርሁድ የሚመራው መንግስት ደግሞ እንደ ልፍስፍስና የህዝቡን ጥቅም አሳልፎ የሰጠ አድርገው አሳይተዋል፡፡ የናሽናል ሳልቬሽን ፍሮንቱ ኤል ባራዲ በቅርብ ሰዓት በግል ቲዊቱ የሲና በረሃና ኢትዮጵያ መተላለቅን የሚያስከትሉ አደገኛ የቀውስ ምንጭ እንደሆኑ ተንብየዋል፡፡ ይችን ነገር ከኛ ሃገር ተቃዋሚዎች የኮረጇት ሳትሆን አትቀርም፡፡ በነገራችን ላይ የኛዎቹ እስካሁን ድምፃቸዉ አልተሰማም፡፡ የአባይ መንገዱን መቀየር አልሞቃቸውም፤ አልበረዳቸውም፡፡
ይህ በንዲህ እንዳለ የሱዳኑ የውሃ ሃብትና ኤሌክትሪክ ሚኒስትር ሞሃመድ ሃሰን በጉዳይ ላይ ለመምከር ወደ ካይሮ ሄደዋል፡፡ እዛ እንደደረሱም ከግብፁ አቻቸው ጋር ተመካክረዋል፡፡ ምን እንደዶለቱ ግን እስካሁን ወሬ አላገኘሁም፡፡ ወደ ሱዳን ከገባሁ አይቀር በዚሁ የሱዳን ሁኔታ እንመልከት፡፡
በግብፅ የሱዳኑ አምባሳደር ከማል ሃሰን የአባይ ወንዝ አቅጣጫ የመቀየር ዜና አስደንጋጭ እንደሆነና ሱዳንና ግብፅ የአረብ ሊግን ጣልቃ ገብነት ሊጠይቁ እንደሚችሉ ተናግረዋል በሚል ትናንት በርካታ መገናኛ ብዙሃን ተቀባብለውት ነበር፡፡ ሆኖም ከምሽት ጀምሮ በአንዳንድ የግብፅ ጋዜጦችና በሱዳኑ ሱዳን ትሪቡን ድረ ገፅ የወጣ ዘገባ አምባሳደሩ ይህንን ማለታቸውን የሚያስተባብል ነው፡፡

የሱዳን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ እኛ እንዲህ አይነት ንግግር ካፋችን አልወጣም ብሏል፡፡ ኢትዮጵያ እያደረገች ያለችው ነገር በሱዳን ላይ ምንም ጉዳት እንደሌለው አረጋግጠናል፤ በዚህ ጉዳይ ላይ ሁላችንም ተጠቃሚ በምንሆንበት ነገር ላይ ከኢትዮጵያም ሆነ ግብፅ ጋር ለመተባበር ዝግጁ ነን ሲል አቋሙን አሳውቋል፡፡
እስኪ አሁን ደግሞ ትናንት ምሽት በአልጀዚራ ስለተላለፈዉ ፕሮግራም ላንሳ፡፡ በኢንሳይድ ስቶሪ ፕሮግራም ላይ ከአዲስ አበባ የመንግስት ኮሚዪንኬሽን ሚኒስትሩ አቶ በረከት ስምዖን፤ ከካይሮ የአካባቢ ጥበቃ ባለሙያዋ ላማ ኤል ሃሎና ከለንደን ደግሞ ደራሲዋ ሊዮ ፓስካል ቀርበዋል፡፡
የፕሮግራሙ አዘጋጅ ገና ሲጀምር የህዳሴውን ግድብ በግብፅ ህልውና ላይ የተደቀነ አደጋ አድርጎ ነው ያቀረበው፡፡ የግብፅ ህዝብ በ2050 /በነሱ አቆጣጠር/ 150 ሚሊዮን ስለሚደርስ ግብፅ ተጨማሪ 21 ቢሊዮን ኪዉቢክ ሜትር ውሃ ያስፈልጋታል፤ ግድቡ ግን እንኳን ይህን እድል ሊሰጣት 18 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውሃ ያሳጣታል ሲል በመደምደም ይነሳል፡፡ የሃይል ማመንጨት አቅሟንና የግብርና ምርት መጠኗንም ይቀንሰዋል፤ በዚህም ሚሊዮኖች ለረሃብ ይጋለጣሉ ይላል ጋዜጠኛዉ፡፡

አቶ በረከት በሰጡት ምላሽ ታዲያ እንደማስበው የኢትዮጵያ ፍላጎት በግብፅም ሆነ ሱዳን ላይ ይህን ያህል ጭንቅ መፍጠር ሳይሆን የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጨት ነው አሉ፡፡
ጋዜጠኛዉ “ፍላጎታችሁ ጉዳት ማድረስ ላይሆን ይችላል ግን ሂደቱ ይህን ጣጣ ሊያመጣ ይችላል” ሲል አቋረጣቸው፡፡ በረከትም ሂደቱ የሚያስከትለዉ እንደውም የተሻለ የዉሃ መጠን ነዉ፡፡ ምክንያቱም እኛ በአካባቢያችን የምናከናውነው የተፈጥሮ ሃብት እንክብካቤ ስራ የከርሰ ምድር ዉሃ መጠንን የሚያሳድግ ነው ሲሉ ተከራክረዋል፡፡
በዚህ ግዜ ጋዜጠኛው ሊዎ ፓስካልን ግብፅ የሱዳንን መሬት ተጠቅማ በኢትዮጵያ ላይ የሃይል እርምጃ ልትወስድ የምትችልበት እድል እንዳለ ጠየቃት፡፡ እርሷም ስትመልስ ግብፅ ይህን ስልት ቀድማም ትጠቀምበት እንደነበር አስታውሳለች፡፡ በተለይም ሶማሊያንና ኤርትራን በመጠቀም ኢትዮጵያን የማዳከም ስልት ትከትል እንደነበር አውስታለች፡፡ አሁን ግን የኢትዮጵያ ጡንቻ በአካባቢው እየፈረጠመ መሆኑን ታነሳና የጦርነት አማራጭ ለግብፅ አዋጭ እንዳልሆነ በተዘዋዋሪ አስረድታለች፡፡
ጋዜጠኛው ውሃን እንደጦር መሳሪያ አድርጎ ማየቱ ያላስደሰታቸዉ አቶ በረከት “እኛ ዉሃ ያጣላናል ብለን አናስብም፡፡ ይህ አንተ የምትለዉም ግዜ ያለፈበት ተረት ነዉ” ብለውታል፡፡ እንደ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ ወጭውን ብቻዋን ትሸፍነው እንጅ ጥቅሙ የሁሉም ሀገሮች ነው፡፡ ግብፅም ሆነች ሱዳን በበጋ ወራት ሳይቀር ወጥነትና ብዛት ያለው ዉሃ ሊያገኙ እንደሚችሉ የተከዜው ግድብ ለሰሜን ምስራቅ የሱዳን አካባቢዎች ያስገኘዉን ጥቅም በአብነት በማንሳት አብራርተዋል፡፡
በቅኝ ግዛት ወቅት የተፈረሙ ስምምነቶች ኢትዮጵያን ያገለሉ እንደሆኑና ይህንን በመቀየር ኢትዮጵያም ሆነች ሌሎቹ ሃገራት በጋራ ተጠቃሚ የሚሆኑበትን አሰራር መዘርጋት እንደሚገባ ተከራካሪዎቹ አንስተዋል፡፡ ፓስካ “ኢትዮጵያ የድርሻዋን ካልተጠቀመችማ ለውሃው /ለወንዙ/ ደህንነት ለምን ትጨነቃለች?” ስትል መልሳ ጠይቃለች፡፡ ኤል ሃሎ በበኩሏ የቀድሞው ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ ንግግርን በማስታወስ ግድቡ የኢትዮጵያ ብቻ ሣይሆን የአካባቢው ሃብት እንደሆነ አሳይታለች፡፡
በአጠቃላይ ሲታይ ውይይቱ መግባባት የሰፈነበት ነበር፡፡ ሆኖም ከኢትዮጵያው ሚኒስትር በስተቀር ሌሎቹ ጉዳዩ በቀጥታ የማይመለከታቸውና የመወሰን ስልጣን የሌላቸዉ መሆኑ የውይይቱን ፋይዳ ያሳንሰዋል፡፡ ውይይቱ በሶስቱ ሃገራት ከፍተኛ ባለስልጣኖች መካከል ቢሆን ይሻል ነበር፡፡ ነገር ግን ሱዳንና ግብፅ በአሁኑ ሰዓት /ቢያንስ የገምጋሚው ቡድን ሪፖርት ይፋ እስኪሆን/ ለመነጋገር ዝግጁ የሆኑ አይመስልም፡፡

No comments:

Post a Comment