Sunday, May 5, 2013

ሁለቱን በጣምራ/በአንድነት ማስኬድ አይቻልም?

በሁሉም ማለት ይቻላል የሃይማኖት አስተምሮ ሥጋዊና መንፈሳዊ ሥራዎችን ሁለቱን በጣምራ ማስኬድ እንደሚቻል በሚያስተምሩት የአስተምሮ ዘይቢያቸው ይሰብካሉ። በተለይ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ እንደ ቀደምትነቷ ለዚህ በር ከፋችም አይነተኛ ምሳሌም ናት። "ሥጋ ካለነፍስ፡ ነፍስ ካለ ሥጋ አትቆምም"፤ ሁለቱ ተያያዥና ተደጋጋፊ ናቸው፤ አንዱ ካለአንዱ መቆምና ሥራቸውን ማከናወን እንደማይችሉ አስፍታና አሙልታ ታስተምራላች።
ምንም እንኳ መንፈሳዊነቱ ጥያቄ ውስጥ ቢገባም ብዙ አገሮች ይህንን መርህ ተከትለው ተግባራዊ ሲያደርጉ ይታያሉ፤ለስኬትም በቅተዋል። ይህንንም አብነት አድርገው የበለጸጉ አገሮችም ሆነ በማደግ ላይ ያሉ አገሮች ተያያዥ ነገሮችን ዛሬም በጣምራ/በአንድነት ለማስኬድ ሲሞክሩ ይታያሉ። በሙከራቸውም እድገትን፣ ብልጽግናን፣ ሰባዊ ርኅራሄንና እኩልነትን በመጠኑም ቢሆን ህዝባቸው ተጠቃሚ እንዲሆን አድርገዋል።
ወደ አገራችን ኢትዮጵያ ስንመለከት ግን ሌሎች በርካታ ነገሮችን ትተን እጅግ ለሰው ልጅ መሰረታዊ የሆኑ ነገሮችን እንኳ በአንድነት ለማስኬድ አልተቻለም፤ ለማድረግም ሙካራ ሲደረግ ጎልቶ አይታይም። ለዚህ ችግር ሁላችንም በትንሹም ቢሆን ከተጠያቂነት ባናመልጥም በዋናነት ግን አገሪቱን እያስተዳደረ ያለው መንግሥት ትልቁን ድርሻ ይወስዳል።

የአገራችን መንግሥት ልማታዊና ዲሞክራሲያዊ መንግሥት ነኝ ብሎ ከነገረን አመታትን አስቆጥሯል። በእውነት ሁኖ ከተገኘና ለመሆን ጥረት የሚያደርግ ከሆነ በእርግጥም መልካምና የሚደገፍ ሃሳብ ነው። በእርግጥ አቶ መለስ በህይወት በነበሩበት ጊዜ ልማትና ዲሞክራሲ ምንም ግንኙነት እንደሌላቸው ተናግረው ነበር። ፓርቲያቸውም የእርሳቸውን ቃል ተግባራዊ ለማድረግ ሌት ተቀን እየሰራ እንደሆነ ምስክር መሆን ይቻላል። በልማት ስም ነጻነት ሲገፈፍ፣ በልማት ስም የእምነት ተቋማት ሲፈርሱ፣ በልማት ስም ታሪካዊ ቦታዎች ታሪካቸው ሲጠፋ፣ በልማት ስም ሰዎች ከቦታቸው ከንብረታቸ  ሲፈናቀሉ እያየን እየተመለከትን ነው። እኔ የዝወትር ጥያቄዬ ግን  ሁለቱን በጣምራ ማስኬድ አይቻልም? የሚለው ነው። ዶ/ር ዘላለም ተክሉ፡ አቶ መለስ"ዲሞ ክራሲና ልማት ምንም ግንኙነት የላቸውም" ብለው በተናገሩት ላይ ትችታቸውን በጥናታዊ ጽሁፍ እንዲ አቅርበዋል።
የዲሞክራሲ ጥንታዊ ትርጉም “ የህዝብ ሃይል” ወይም “ የህዝብ አስተዳደር” ሲሆን መሰረቱም ሁለት የግሪክ ቃላቶች ዴሞስ(demos)  “ህዝብ” እና ክራቶስ (kratos) “ሃይል” ውህደት ነው:: የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት በነበሩት አብረሃም ሊንከን አተረጓጐምም መሰረት ደግሞ ዲሞክራሲ ማለት በህዝብ የተመረጠና ለህዝብ የቆመ የህዝብ መንግስት ማለት ነው:: በዚህ ዓይነት ስርዓት ውስጥ የተመረጡ መሪዎች ቀጥተኛ ተጠሪነታቸው (accountability) ለህዝቡ ሲሆን የሚሰጡት አገልግሎትም በህዝቡ ፍላጎት ላይ የተመሰረተ ብቻ እንደሆነ ይገለጻል:: ዘመናዊው የዲሞክራሲ ምንነት በቀደምቶቹ ትርጉሞች ላይ የዳበረ ሲሆን የሰው ልጅ መሰረታዊና ፖለቲካዊ መብቶች የማክበር፣ በህዝቦች መካከል የሰፈነ እኩልነት፣ ነጻና ፍትሃዊ የመምረጥና የመመረጥ መብት ያለው፣ ሃሳብን በነጻነት መግለጽ የሚፈቅድ፣ እንዲሁም ከማንኛውም ተጽዕኖ ነጻ የሆነ የፍትህ ሥርዓትንና ነጻ ፕሬስ ያካተተ ተቋምም እንደሆነ ይታወቃል::

የኢኮኖሚ ልማትም በጣም የሰፋ፣ ከጊዜ ጊዜ ተለዋዋጭና አከረካሪ ትርጓሜ የያዘ ንድፈ ሃሳብ ነው:: ልማት ቀደም ባሉ ጊዜያት ሲተረጎም የሰው ልጅ ያለውን የጉልበት፣ የካፒታልና የዕውቀት አቅም አሻሽሎ ምርታማነትን በማሳደግ በሚያገኘው የተሻለ የነፍስ ወከፍ ገቢ ከድህነት የተላቀቀና የተመቻቸ ኑሮ መኖር መቻል ነበር:: የኖቤል ተሸላሚው ኢኮኖሚስት አማርቲያ ሴን እንደሚያስረዳው ደግሞ በ1980ዎቹና 90ዎቹ በኋላ የልማት ትርጉም እየሰፋ መጥቶ ከኢኮኖሚ ጠቀሜታ በተጨማሪ የሰብዓዊና የፖለቲካ ነጻነት መብቶችን፣ ስፋት ያላቸው ማህበራዊ ዕድሎችን፣ የአመራር ግልጽነትና የደህንነት ዋስትና እንዲያካትት ተደርጎ እንዲሰራበት ተደርጓል:: የሰብዓዊ ተሟጋች ድርጅቶች ደግሞ የልማት ትርጓሜ ከላይ ከተዘረዘሩት በተጨማሪ የሰፋ የህብረተሰብ ተሳትፎና የመሪዎች ግልጽነት (transparency) መያዝ እንዳለበት አበክረው ያሳስባሉ:: ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በስፋት ተቀባይነት ያገኘውና በብዙ ሃገራት፣ ዓለም አቀፍ የልማትና የፋይናንስ ተቋማት እየተሰራበት ያለው ደግሞ የሌላውን የኖቤል ተሸላሚ ኢኮኖሚስት ጆሴፍ ስቲግሊትዝ ትንታኔን መሰረት በማድረግ የጎለበተው አስተሳሰብ ሲሆን በዚህ ትርጓሜ መሰረት ልማት ማለት ከኢኮኖሚ ዕድገት ባሻገር የሰው ልጅ ከማህይምነት የሚላቀቅበት፣ ለረጅም ዕድሜ ሊኖር የሚችልበትና ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል የሚጎናጸፍበት ደረጃ እንደሆነ ታምኖበታል::

ስለዚህ የሃገራችን መንግሥትም በስም ከመነገድና ህብረተሰቡን ግራ ከማጋባት ይልቅ እነዚህ ሁለቱን በጥምረት ማስኬድ ይችል ነበር። እርግጥ ነው በአንድ ጊዜ ተግባራዊ ማድረግ ከማሰብ በላይ እጅግ አዳጋች ነው፤ ሆኖም ግን በሂደት መድረስ የማንችልበት ምንም ምክንያት የለም። ምክንያቱም ይህን በጥምረት ከሚያስኬዱ ሃገራት በአቅምም በሰው ኃይልም የተሻልን እንጂ ያነስን አይደለንምና።
ዲሞክራሲንና ልማትን፤ ነጻነትንና ልማትን፣ እኩልነትንና ልማትን፣ ሰላም ፍቅርንና ልማትን፣ የህብረተሰቡን ፍላጎትና ልማትን፣ የእምነት ተቋማት ሳያፈርሱ ልማትን በጣምራ ማስኬድ አይቻልም? መልሱ ይቻላል ነው። ብዙዎች እንደሚስማሙት ነጻነት ካለ ልማት አለ፣እድገት አለ፣ ብልጽግና አለ፣ መከባበርና ግልጽ ውይይት በህብረተሰቡ ዘንድ ይኖራል። ስለዚህ ከሁሉም በፊት ለነጻነትና ለዲሞክራሲ ቅድሚያ በመስጠት ሁለቱን በጣምራ ብናስኬዳቸው መልካም ይሆናል የሚል ሃሳብ አለኝ።
የእያንዳንዳችን ድርሻ፦ በጉልበታችን፣በገንዘባችን፣በሃሳባችን/በእውቀታችን እና በአገኘነው አጋጣሚ ተጠቅመን ከዘረኝነት ርቀን መንግሥት መልካም ነገሮችን በጥምረት እንዲያስኬድ ድጋፍና አቅጣጫ ማሳየቱ የውዴታ ግዴታችን መሆኑን አውቀን ብንሰራ ለውጥ ልናመጣ እንችላለን።

መልካም የትንሣኤ በዓል!
የዘወትር ምኞቴ የነጻነት ትንሣኤ ለኢትዮጵያ.................

No comments:

Post a Comment